Saturday, 21 May 2016 16:03

የግንቦት 20 ትርፍና ኪሳራ - ባለፉት 25 ዓመታት

Written by 
Rate this item
(5 votes)

ፖለቲከኞች ምን ይላሉ?

የግንቦት 20 በዓል 25ኛ ዓመት የብር ኢዮቤልዩ በተለያዩ ዝግጅቶች እንደሚከበር መንግስት አስታውቋል፡፡ ግማሽ ክፍለ ዘመን
ባስቆጠረው የኢህአዴግ መራሹ መንግስት የተመዘገቡት ስኬቶችና ውድቀቶች እንዴት ይገመገማሉ? የግንቦት 20 ትርፍና ኪሳራ
እንዴት ይገለጻል? የተለያዩ የፓርቲ አመራሮችና ፖለቲከኞች አስተያየታቸውን ሰንዝረዋል፡፡ የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ አለማየሁ
አንበሴ የሁሉንም ሃሳብና አተያይ እንደሚከተለው አጠናቅሮታል፡፡

“ለኔ ግንቦት 20፣ እንደ ማንኛውም ሰኞና ማክሰኞ ነው”    አቶ ግርማ ሠይፉ - የቀድሞ የፓርላማ አባል)

  ግንቦት 1983 ላይ ምናልባት የ23 አመት ወጣት ነበርኩ፡፡ እውነቱን ለመናገር የመንግስት ለውጡ ሲመጣ ምንም የተለየ ነገር አልጠበኩም ነበር፡፡ እነዚህ ሰዎች ሲመጡ አገር መምራት ይችላሉ ወይም ይመራሉ የሚል ግምት አልነበረኝም፡፡ ከራሳቸው አስተሳሰብ እንኳ ስንነሣ የቀድሞ ጠቅላይ ሚኒስትር በወቅቱ እየተጠላ የመጣውን ሶሻሊዝም ያውም የአልባኒያ ሶሻሊዝም ተከታይና ይሄንኑ ይሰብኩ የነበሩ ሰው ናቸው፡፡ ስለዚህ እነዚህ ሰዎች ለዚህች ሃገር ይጠቅማሉ ወይም ይህቺን ሃገር ይመራሉ የሚል እምነት አልነበረኝም፡፡ ሆኖም በራሳቸው ባይችሉም እንኳን ሌሎች ኢትዮጵያውያንን በማሳተፍ አገሪቷን ወደተሻለ አቅጣጫ ሊመሯት ይችላሉ የሚል ተስፋ ነበረኝ፡፡ አቅምም ስለሌላቸው ሌላውን ያሳትፋሉ የሚል ግምት ነበረኝ፡፡
በሽግግር ቻርተሩ ጊዜ ነፃ ሚዲያ፣ ሳንሱር ቀርቷል የሚሉ ቃላት የተጨመሩበት ስለነበር ጥሩ ነገር ሊመጣ ይችላል የሚል ተስፋ ነበረኝ፡፡
መጨረሻ ላይ ግን ሁሉንም ያሳተፈ ነው በሚል የራሳቸውን ኮንፈረንስ ሲያካሂዱ በዚያኑ ወቅት አንዱ ከሣሽ አንዱ ተከሳሽ ሆኖ የሚቀርብ ሣይሆን ሀገራዊ እርቅ የሚወርድበት ሁኔታን ስለአሸናፊነት ስነልቦና ወርደው ቢያመቻቹ ኖሮ ወደምንፈልገው ምዕራፍ የምንሸጋገርበት እድል ነበር ብዬ አምናለሁ፡፡
ከዚያ በኋላም ይሻሻላሉ ተብለው ሲጠበቁ ብሶባቸው በ1993 ዓ.ም የኢትዮጵያ ህዝብ እስኪንገሸገሽባቸው ድረስ ደርሰዋል፡፡ እኔ እንደሚመስለኝ ያኔ ያዳናቸው በወቅቱ የተከሰተው የኢትዮ-ኤርትራ ጦርነት ነው፡፡ ጦርነቱ ለእድሜያቸው መራዘም መልካም እድል የፈጠረላቸው ይመስለኛል፡፡ ጦርነቱ ተከስቶ ኢትዮጵያውያን አንድ የሚያደርግ ነገር ባይፈጠር ኖሮ  ይገጥማቸው የነበረውን ችግር መቋቋም አይችሉም ነበር፡፡ ያ ለእነሱ አንድ እድል ነው ብዬ አስባለሁ፡፡ በአለማቀፍ ደረጃም ለመጀመርና ዘልቆ ለመግባባት ጦርነቱ እድል የከፈተላቸውም ይመስለኛል፡፡
ሌላኛው በኢህአዴግ የ25 አመት ጉዞ ውስጥ በጉልህ የሚጠቀሰው የ1997 ምርጫ ነው፡፡
በወቅቱ ከህዝቡ የቀረበባቸውን ተቃውሞ ሊቋቋሙ አልቻሉም ነበር፡፡ አጋጣሚውን ለበጎ መጠቀም ሲችሉ አልተጠቀሙበትም፡፡
 ከዚያ በኋላም “ስልጣናችን የሚያበቃው በመቃብራችን ላይ ነው” ብለው ቆርጠው ተነስተው ይኸው እስከዛሬ አሉ፡፡
የግንቦት 20 ፍሬዎች
ስኬታቸው ይሄ በመሠረተ ልማት አገኘን የሚሉንን ከሆነ እኔ አልስማማም፡፡ ስኬት በቁስ ብቻ ሳይሆን በሰው ልጅ ሰብዕና እና ነፃነት ላይ የሚመሰረት ነው የሚል ዕምነት አለኝ፡፡ ከተማ ውስጥ ከምናያቸው አስፓልቶች በላይ ከ25 አመት በኋላም 20 ሚሊዮን ህዝብ በእለት ደራሽ እርዳታና በሴፍቲኔት የሚረዳ ህዝብ መኖሩን ነው የማስበው፡፡ ይሄን ሁሉ ጉድ ይዘን ተሣክቶልናል የምንል ከሆነ፣ እንደ ባህላችን ያው “ተመስገን” ብለን መኖር አለብን ማለት ነው፡፡
ከዚህ መለስ ብለን ማየት አለብን ብዬ የማስበው ጦርነት ባይኖር ኖሮ ደርግስ መሠረተ ልማት የሚባለውን መስራት አይችልም ወይ? የሚለውን ነው፡፡ በሚገባ ይሠራ ነበር፡፡ ከዚህች ድሃ ሀገር በየአመቱ በቢሊዮን የሚቆጠር ገንዘብ ባይሸሽ ደግሞ ምን ሊሠራ እንደሚችል ማሠብ ያስፈልጋል፡፡ አንዳንዴ በሚኒልክ ጊዜ ስልክ አልነበረም፤ዛሬ ሞባይል አምጥተናል ሲሉ ይገርመኛል፤ ሞባይልን እነሱ ባያመጡትም ማንም ሊያመጣው የሚችል ነው፡፡ ዘመኑ የፈቀደው የቴክኖሎጂ ውጤት ነው፡፡ የኢህአዴግ መንግስት ባይኖርም ሞባይል ይኖር ነበር፡፡ መንገድ ሠርተናል የሚለውም ቢሆን ጣሊያንም በሚገባ መንገድ ሠርቷል፡፡ በ5 አመቱ ብዙ መንገድ ሠርቷል፡፡ ስለዚህ ጣሊያን ይሻለን ነበር ልንል ነው?
መንግሥት ሲቀየር የነበርዎት ተስፋ ምን ነበር? ተስፋዎት ከ25 ዓመት በኋላ ተሟልቶ አግንተውታል?
እኔ እዚህ ሀገር የምኖረው በየዓመቱ ተስፋ ስላለኝ ነው፡፡ እኔ ተስፋ አልቆርጥም፤ በአገሪቱ ውስጥ ነገሮች እንዲሻሻሉ የራሴን አስተዋጽኦ ማበርከት አለብኝ ብዬም አምናለሁ፤ በግሌም ከመሰሎቼ ጋር ሆኜም፡፡ የኔ ልጆች፤ “ይህቺን ሃገር እንዲህ አድርገው ያስረከቡን አባቶቻችን ናቸው” ብለው እንዲወቅሱኝ አልፈልግም፡፡ እንዲለወጥና እንዲሻሻል ጥረት አደርጋለሁ፡፡ መለወጥና ማሻሻል ባልችል እንኳ ልጆቼ፣ “አባቴ ዝም ብሎ ቁጭ ብሎ ነው እንደዚህ አይነት ሀገር ያስረከበኝ” እንዳይሉኝ በግሌ ሙከራ አደርጋለሁ፡፡ እኔ እያንዳንዱ ሰው የሚያደርገው እንቅስቃሴ ለለውጥ የራሱ ድርሻ አለው የሚል ጠንካራ እምነት አለኝ፡፡ ግን ብንተባበር ለውጡን እናፋጥናለን፡፡
ለኔ ግንቦት 20 እንደ ማንኛውም ሠኞና ማክሰኞ ነው፡፡ በትግል ለውጥ ለማምጣት ግንቦት 20ን መጠበቅ አያስፈልገኝም፡፡ አንድ ሴትዮ ምን አሉኝ መሰለህ? “ኢህአዴግ ያመጣልን ለውጥ ሴት ልጆቻችን በቪዛ ውጭ ሀገር እንዲሄዱ ማድረግ ብቻ ነው፡፡” እኔም እሱ ባይመጣ ኖሮ ይቀርብን ነበር የምለው ዛሬ ላይ ያለ አንድም ነገር የለም፡፡ አሁን ያሉት ነገሮች ሁሉ እሱ ባይመጣም ምናልባትም በተሻለ መጠን የሚመጡና የሚፈጠሩ ነገሮች ናቸው፡፡ እንደውም የተሻሉ ብዙ ነገሮች ይኖሩ ነበር፡፡ ሞባይልም፣ ቴሌቭዥንም ሌላውም እነሱ ቢኖሩም ባይኖሩም ይመጣሉ፡፡ እኔ የሚቆጨኝ ያልመጡ ብዙ ነገሮችን ሳስብና የተበላሸውን ነገር ሳስተውል ነው፡፡
ዛሬ አንድ ሚኒስትር ሲሾም ስሙን ለመስማትና በዘር ለመፈረጅ እንድንጣደፍ ያደረጉን እነሱ ናቸው፡፡ መታወቂያችን ላይ ብሄር የፃፉልን እነሱ ናቸው፡፡ በየእለቱ ስለ ብሄር እንድናስብ አድርገውናል፤ እነዚህ ሁሉ ጥሩ አይደሉም፡፡

========================================

“አገሪቱ የባህር በር ያጣችው ከግንቦት 20 በኋላ ነው”     አቶ ልደቱ አያሌው፤ ፖለቲከኛ)

የመንግስት ለውጡ ሲመጣ የተለያዩ ጭንቀቶች ነበሩ፡፡ ይህቺ ሀገር ወደ ሁከት ሜዳ ትሸጋገራለች የሚል ፍርሃት ነበር፡፡ ኢህአዴግ ከሚያራምዳቸው አንዳንድ አቋሞች በመነሳት ደግሞ ሀገሪቱ ትበታተናለች የሚል ስጋትም ነበር፡፡ እኔም እንደ ማንኛውም የወቅቱ ወጣት በነዚህ ሀሳቦች መሃል ነበርኩ፡፡
በመጀመሪያ ግንቦት 20 ደርግ ወድቆ ኢህአዴግ የተተካበት ነው፡፡ በአንፃራዊነት በሃገሪቱ ውስጥ ለረዥም አመታት በርካታ ወጣቶችን የጨረሰው ጦርነት የቆመበት ጊዜ ነው፡፡ እሱ በራሱ ስኬት ነው፡፡ ሁለተኛው ውጤት በሀገሪቱ ውስጥ ለመጀመሪያ ጊዜ በአለማቀፍ ደረጃ እውቅና ያገኙ የሰብአዊ መብት ድንጋጌዎች ተቀባይነት ያገኙበት ጊዜ ነበር፡፡ የነፃ ፕሬስ፣ የብዙሃን ፓርቲ አሰራር ቢያንስ በህግ ደረጃ እውቅና አግኝተዋል፡፡ ቆይቶ ቢሆንም የኢኮኖሚ እድገትም የታየው ከግንቦት 20 በኋላ ነው ማለት ይቻላል፡፡
 ያሳጣን ብዬ የማነሳው አንዱና ዋነኛው የኢትዮጵያና የኤርትራ ህዝብ የተነጣጠለው በግንቦት 20 አማካኝነት መሆኑ ነው፡፡ በታሪኳ የባህር በር ያጣችውም ከግንቦት 20 በኋላ ነው፡፡ የአንድነት ስሜት ጥያቄ ውስጥ ገብቶ ከመቼውም ጊዜ በበለጠ የአካባቢያዊ ስሜት የበለጠ ቦታ ያገኘበት ጊዜ የመጣው በግንቦት 20 ነው፡፡ የሀገሪቱ አንድነት ጥያቄ ውስጥ ገብቶ እስካሁን ዘልቋል፡፡ በየጊዜው አዳዲስ ቅራኔዎችና ግጭቶች እየተፈጠሩ ነው፡፡ በሂደትም ደግሞ ስልጣን በአንድ ፓርቲ የበላይነትና ሁለንተናዊ ቁጥጥር ውስጥ የወደቀበት ሁኔታ ነው የተፈጠረው፡፡ ከዚያ በኋላ ያሉት ነገሮች ሁሉ የህብረተሰቡ አመለካከቶች ነፀብራቅ ሳይሆን የአንድ ፓርቲ ነፀብራቅ ነው በአጠቃላይ የህዝቡን ህይወት እየወሰነ ያለው፡፡ በህገ መንግስቱ የሰፈሩና በጎ ናቸው ያልናቸው ነገሮች በተግባር ላይ የውሃ ሽታ የሆኑበት አጋጣሚም በሂደት ተፈጥሯል፡፡
 አንፃራዊ ሠላም መገኘቱ በሌላ ጎኑ በበጎ የሚታይ ነው፡፡ ይሄን ስል ጦርነት የለም ማለቴ አይደለም፡፡ ግንቦት 20 ማክበር ከጀመርን 25 ዓመት ሆኖናል፡፡
በዚህ መሃል በኢኮኖሚው፣ በፖለቲካው፣ በማህበረሰብ እድገት፣ በፍትህ … ዘርፍ ያሉ ጉዳዮች በሰፊው መገምገም አለባቸው፡፡ ከሁሉም በላይ ግን የሚያሳስበው የሀገሪቱ አንድነት አደጋ ላይ መሆኑ ነው፡፡

==================================


“ድርጅታችን ለስርአቱ አደጋ የሆኑትን በተሃድሶ አጥርቷል”     (አቶ ሴኩቱሬ ጌታቸው፤ የቀድሞ ታጋይ)
በእነኚህ 25 ዓመታት ውስጥ በርካታ ፖለቲካዊ ማህበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊ ድሎች ተመዝግበዋል፡፡ እንደሚታወቀው የስርአት ለውጥ ነው የተደረገው፡፡ ያለፉት መንግስታት ህዝቦችን በተለያየ መልኩ የሚጨቁኑ ነበሩ፡፡ ያንን የጭቆና ስርአት የገረሰሰ ድል ነው፡፡ የኢትዮጵያ ህዝቦች ለመጀመሪያ ጊዜ የሰብአዊና ዲሞክራሲዊ እድሎቻቸውን እንዲጠቀሙ፣ የራሳቸውን እድል በራሳቸው መወሰን የሚችሉበት፣ የግልም ሆነ የቡድን መብቶቻቸው እንዲከበር ያደረገ ነው፡፡
በዚያው መጠን ሀገራችን ከድህነት አረንቋ እንድትወጣ እያደረገ ያለ ድል ነው፡፡ በድህነትና በኋላ ቀርነት የምትታወቀውን ሀገራችንን በልማት እንድትታወቅ አድርጓል፡፡ የልማት አቅጣጫን በመቀየስ በሀገሪቱ ልማት የሚፋጠንበትና ህዝቡ በየደረጃው ተጠቃሚ የሚሆንበት ምቹ ሁኔታ ለመፍጠር የሚያስችል መሰረት የተጣለበት ቀን ነው፡፡ በማህበራዊ መስኩም እንደዚሁ ዜጎች የሀገሪቱ አቅም በፈጠረው መጠን ከትምህርት፣ ከጤና፣ ተጠቃሚ የሚሆኑበት፣ ሰራተኞች የላባቸው ተጠቃሚ የሚሆኑበት፣ ጥቅማቸው እንዲከበር መሰረት የተጣለበት ቀን ነው፡ በጨቋኝ ስርአት ስር የነበረን ህዝብ ወደ ተሻለ ምዕራፍ ያሻገረ ቀን ነው፡፡
የሽግግር መንግስቱ ቻርተር የሀገሪቱን ብሄር ብሄረሰቦች ያሳተፈ ነበር፡፡ አለማቀፍ ደረጃውን የጠበቀ የፕሬስ ነፃነት የታወጀበት እለት ነው፡፡ ኢኮኖሚውም ቢሆን ግብርና መር የሆነ ፖሊሲ ወጥቶ ሀገሪቱን ከውድቀት ታድጓል፡፡ ወደ እድገት ሊያመራ፣ የሠለጠነ የሰው ሃብት ሊያፈራ የሚችል ህገ መንግስት መሰረት የተጣለበት ቀን ነበር፡፡ በነዚህ አመታት አብዛኛውን ህዝብ ከድህነት ያወጣ፣ መሰረተ ሰፊ የሆነ የኢኮኖሚ እድገት መመዝገቡን ማንም የሚክደው አይደለም፡፡ በጋራ የፌደራል ስርአት ተፈጥሮ፣ ዜጎች በእኩልነት የሚኖሩበት ምቹ ሁኔታ ተፈጥሯል፡፡ የቡድን መብት ተከብሯል፡፡
በዚያው ልክ ባለፉት 25 ዓመታት ያጋጠሙ ፈተናዎችም አሉ፡፡ የህዝቡ ተጠቃሚነት እየሰፋ በሄደ ቁጥር በጣም ብዙ ፍላጎቶች ይፈጠራሉ፡፡ ጠያቂና ሞጋች የሆነ ህብረተሰብ እየተፈጠረ ነው ያለው፡፡
የመንግስት መዋቅርን አለ አግባብ ለመጠቀም የተደረጉ ሙከራዎች ታይተዋል፡፡ ድርጅታችንም ለስርአቱ አደጋ የሆኑትን በተሃድሶ አጥርቷል፡፡ አሁንም በመልካም አስተዳደርና በኪራይ ሰብሳቢነት የሚታዩ ችግሮች የስርአቱ ፈተናዎች ናቸው፡፡ ኢኮኖሚው ባደገ ቁጥር በዚያው ልክ ፈተናዎቹ ውስብስብ እየሆኑ ነው የሄዱት፡፡ 25 ዓመቱን ሙሉ እንዲህ በቀላሉ አልዘለቅንም፡፡ እየታገልን ነው፡፡ ከዚህ በኋላም ትግላችን ቀጥሎ እቺን ሀገገር ወደ ተሻለ ምዕራፍ የማሸጋገር ስራ ይሰራል፡፡ ሀገራችን ከኋላቀርነት ወጥታ የእድገት ማማ ላይ የምትደርስበትን አቅጣጫ ስለያዘች ደስተኞች ነን፡፡ በቀጣይ ጉዟችን ፈተናዎችን እያለፍን የታፈረች፣ የተከበረችና ህዝቦቿ በነፃነት የሚኖሩባት ሀገር እንገነባለን፡፡ በዚህ መንፈስ ነው የምናከብረው፡፡

=================================

“ኢህአዴግ በ25 ዓመት ወደ ቅቡልነት አልተሸጋገረም”      (ዶ/ር ዳኛቸው አሰፋ፤የፍልስፍና ምሁር

የግንቦት 20 በአል 25ኛ ዓመት ሲታሰብ፣ ያለፉትን 25 ዓመታት በሶስት ዘርፎች መገምገም ያስፈልጋል፡፡ አንደኛ ከዲሞክራሲ አንጻር፣ በነዚህ 25 ዓመታት ውስጥ ስርአቱ የዲሞክራሲ ጅማሮ ላይ ነው ቢባልም ከጉልበት ወደ ቅቡልነት ሲሸጋገር አላየንም፡፡ አልተሸጋገርንም፡፡
ይልቁንም ወደ ፈላጭ ቆራጭነት (አውቶሪቶሪያን) የበለጠ ተሸጋግሯል፡፡ ሁለተኛ በፌደራሊዝም ዙሪያ ጅማሮው በጎ የሚባል ነበር፤ኋላ ላይ ግን ፌደራሊዝሙ ቀርቶ ወደ ብሄረሰብ ተኮር አሃዳዊነት (ethnic totalitarianism) ተሸጋግሯል፡፡
የተወሰኑ ክልሎች አሉ፤በአሃዳዊ ስርአት የሚተዳደሩ፡፡ ሶስተኛ ኢኮኖሚውን በተመለከተ ጅምሩ ጥሩ ነበር፤ኋላ ላይ የሙሰኛው ሲሳይ ሆነ እንጂ፡፡ ሙሰኛው እየበላው ነው ያለው፡፡ ሙሰኛው የደረሰበት ደረጃ ከፍተኛ ከመሆኑ የተነሳ ዝም ቢባልም  ጠንክረው እናሻሽል ቢሉም ስርአቱን የሚያፈርስ ሆኗል፡፡ በአጠቃላይ የፖለቲካ አዙሪት ውስጥ ገብቷል ብለን ልንደመድም እንችላለን፡፡ያሉትን ማህበረ-ፖለቲካዊ  ቅራኔዎች ከባድ የሚያደርጋቸው ከኋላ የወረሳቸው ሳይሆን ራሱ የፈጠራቸው ችግሮች ፈጠው ሲመጡ አደጋው የከፋ መሆኑ ነው፡፡ ኢህአዴግ እንደሚያወራው ቢሰራ ኖሮ ከየአቅጣጫው ጥያቄ ባልተነሳ ነበር፡፡   

Read 7473 times