Saturday, 11 June 2016 13:45

ካስትል ወይን አዲስ ምርት ለገበያ አቀረበ

Written by 
Rate this item
(1 Vote)

ከ8 ዓመት በፊት በኢትዮጵያ በወይን ጠመቃ የተሰማራው ካስትል የወይን ጠጅ ፋብሪካ፣ ከነጭና ቀይ ወይን በተጨማሪ “ሮዜ” የተሰኘ አዲስ የወይን ጠጅ ለገበያ አቀረበ፡፡  
በወይን ጠመቃ አለማቀፍ እውቅና ያለው የፈረንሳውያኑ ካስትል ቤተሰቦች ወይን አምራች ኩባንያ በኢትዮጵያ ያለውን የወይን ጠጅ ገበያ ድርሻ እያሰፋ መሆኑን የገለጸ ሲሆን በዓመት ከ1.4 ሚ. ጠርሙስ በላይ ወይን ለገበያ እያቀረበ መሆኑንም አስታውቋል፡፡ አዲሱ “ሮዜ” የተሰኘው ምርቱ በኢትዮጵያ የወይን ወዳጆች በስፋት ከሚታወቁት “ነጭ” እና “ቀይ” ወይን የተለየ አዲስ የፈጠራ ምርት ነው ተብሏል፡፡ ይሄም ፈጠራ ካስትልን ብቸኛ ያደርገዋል፡፡
በተጨማሪም ኩባንያው በቀላል ዋጋ ተጠቃሚዎች ሊያገኟቸው የሚችሉ የካርቶን ወይኖችን  ለገበያ ለማቅረብ በዝግጅት ላይ መሆኑን የኩባንያው የማርኬቲንግና ሽያጭ ማናጀር ወ/ት አለም ፀሐይ በቀለ ገልፀዋል፡፡ የወይን ፋብሪካው አሁን ካለው 162 ሄክታር የወይን እርሻ በተጨማሪ 85 ሄክታር የማስፋፊያ ስራ እየሰራ መሆኑን ወ/ት አለምፀሐይ አስረድተዋል፡፡
የካስትል ወይኖች ለምን ዋጋቸው ተወደደ ተብለው የተጠየቁት ሃላፊዋ ሲመልሱ፤ነጋዴዎች ፋብሪካው ከተመነው ዋጋ በላይ ከ100--200 ፐርሰንት ጭማሪ እያደረጉ ስለሚሸጡ ነው ብለዋል፡፡ ኩባንያው ስለ ወይን ጠጅ አይነቶች ለመስተንግዶ ባለሙያዎች ስልጠና እየሰጠ መሆኑንም ለማወቅ ተችሏል፡፡  

Read 2087 times