Saturday, 11 June 2016 13:47

ተመድ የኤርትራ ባለስልጣናት በአለም አቀፍ ፍ/ ቤት እንዲቀርቡ ጠየቀ

Written by 
Rate this item
(3 votes)

የኤርትራ መንግስት የተመድን ሪፖርት አጣጥሎታል

የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የሰብዓዊ መብቶች ምርመራ ኮሚሽን፣ የኤርትራ መንግስት ባለስልጣናት በዜጎቻቸው ላይ ለሩብ ክፍለ ዘመን በፈጸሙት የማሰር፣ የማሰቃየት፣ የመግደል፣ የአስገድዶ መድፈርና የመሳሰሉ ኢ-ሰብዓዊ የወንጀል ድርጊቶች በአለማቀፉ የወንጀለኞች ፍርድ ቤት ቀርበው ሊጠየቁ ይገባል ማለቱንና፤ የጸጥታው ምክር ቤትም በአገሪቱ ላይ ማዕቀብ እንዲጥል መጠየቁን ሮይተርስ ዘገበ፡፡
የኤርትራ መንግስት በበኩሉ፤ የተመድን ሪፖርት ፖለቲካዊና መሰረት የለሽ ነው ሲል በመተቸት፣ መሰል ውንጀላዎች በኤርትራ ላይ ብቻ ሳይሆን በመላ አፍሪካ ላይ የሚቃጡ ጥቃቶች ናቸው ብሏል።
አገሪቱ ነጻነቷን ከተጎናጸፈችበት ጊዜ አንስቶ መሪዎቿ በዜጎች ላይ ኢ-ሰብአዊ ድርጊቶችን መፈጸማቸውን ባለፈው ረቡዕ የገለጸው ኮሚሽኑ፣ የአገሪቱ ከፍተኛ ባለስልጣናት ለፈጸሙት ወንጀል ተጠያቂ መሆን እንዳለባቸው ጠቁሞ፣ በምርመራው ያገኘውን ውጤት ለአለማቀፉ ፍርድ ቤት ማስተላለፉንም አስታውቋል፡፡ ባለፉት 25 አመታት 400 ሺህ ያህል የአገሪቱ ዜጎች በወታደራዊ ግዳጅና በመሳሰሉት የግዳጅ ተልዕኮዎች የባርነት ህይወትን ሲገፉ ቆይተዋል ያለው መርማሪ ቡድኑ፣ በአገዛዙ ተማርረው ከአገሪቱ ለመውጣት የሚሞክሩ በርካታ ዜጎችም በአገሪቱ መንግስት የድንበር ጠባቂዎች እንደሚገደሉ አስታውቋል፡፡
በየወሩ በአማካይ 5 ሺህ ኤርትራውያን በአገዛዙ ተማርረው አገራቸውን ጥለው ይሰደዳሉ ያለው ኮሚሽኑ፤ዜጎችን በኢ-ሰብዓዊ መንገድ የሚያሰቃዩት እነዚህ ከፍተኛ ባለስልጣናት አለማቀፍ ህጎችን በመጣስ በሰሩት ከፍተኛ የወንጀል ድርጊት ተገቢውን ቅጣት ማግኘት እንዳለባቸው ጠቁሞ፣ በአገሪቱ ላይ ማዕቀብ እንዲጣል ጠይቋል፡፡
የኤርትራ ፕሬዝዳንት አማካሪ አቶ የማነ ገብረአብ ረቡዕ ዕለት በሰጡት መግለጫ፣ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የሰብዓዊ መብቶች ምርመራ ኮሚሽን ያወጣው ሪፖርት መሰረተ ቢስና ምንም አይነት ማስረጃ የሌለው መሆኑን በመጥቀስ፣ መንግስታቸው ሪፖርቱን እንደሚያወግዘው አስታውቀዋል፡፡
ኮሚሽኑ በኤርትራ ላይ አደረግሁት የሚለው የጥናት ሪፖርት፣  የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የጥናት መርሆችን ያላከበረና ሙያዊነት የጎደለው ነው ያሉት አቶ የማነ፤አገሪቱ ነጻነቷን ከተጎናጸፈችበት ጊዜ አንስቶ የተመዘገቡ መልካም ለውጦችን ለማካተት ያልደፈረና ሚዛናዊነት የጎደለው ነው ብለዋል፡፡

Read 2340 times