Saturday, 11 June 2016 13:49

አንጌላ መርኬል ለ6ኛ ጊዜ የዓለማችን ሃያል ሴት ተብለዋል

Written by 
Rate this item
(3 votes)

አሜሪካ በርካታ ሃያላን ሴቶችን በማስመዝገብ ከአለማችን ቀዳሚ ሆናለች


በየተሰማሩበት መስክ የላቀ ተሰሚነትን ያገኙ የአለማችንን 100 ሃያላን ሴቶች ዝርዝር በየአመቱ ይፋ የሚያደርገው ታዋቂው ፎርብስ መጽሄት፣ ሰሞኑን ባወጣው የ2016 ሃያላን ሴቶች ዝርዝር ውስጥ የጀርመን መራሄ መንግስት አንጌላ መርኬልን ለስድስተኛ ጊዜ በቀዳሚነት አስቀምጧል፡፡
በፎርብስ አመታዊ ዝርዝር ውስጥ ላለፉት አምስት አመታት የዓለማችን ሃያል ሴት ሆነው የዘለቁትን አንጌላ መርኬልን በመከተል እንደ አምናው ሁሉ ዘንድሮም በሁለተኛ ደረጃ ላይ የተቀመጡት፣ በዘንድሮው የአሜሪካ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ ፉክክር ላይ የሚገኙት ሂላሪ ክሊንተን ናቸው፡፡
የአሜሪካ የፌደራል ሪዘርቭ ሊቀመንበር ጃኔት ያለን ሶስተኛ ደረጃን ሲይዙ፣ በጎ አድራጊዋ ሚሊንዳ ጌትስና የጄነራል ሞተርስ ዋና ስራ አስፈጻሚ ሜሪ ባራ በአራተኛና አምስተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጠዋል። የአለማቀፉ የገንዘብ ተቋም ማኔጂንግ ዳይሬክተር ክርስቲያን ላጋርድ፣ የፌስቡኳ ሼሪል ሳንበርግ፣ የዩቲዩቧ ዋና ስራ አስፈጻሚ ሱዛን ዎጅኪኪ፣ የኤህፒ ኩባንያ ዋና ስራ አስፈጻሚ ሜግ ዊትማንና ባንኮን ሳንታንደር የተባለው ድርጅት ሊቀመንበር አና ፓትሪሺያ ቦቲን እንደ ቅደም ተከተላቸው እስከ አስረኛ ያለውን ደረጃ ይዘዋል፡፡
በዘንድሮው የፎርብስ 100 የአመቱ የዓለማችን ሀያላን ሴቶች ዝርዝር ውስጥ ከተካተቱት ሴቶች መካከል 26 ያህሉ የፖለቲካ መሪዎች መሆናቸው የታወቀ ሲሆን፣ ከአፍሪካ ፖለቲከኛ ሴቶች መካከልም የላይቤሪያ ፕሬዚዳንት ኤለን ጆንሰን ሰርሊፍና የሞሪሽየስ ፕሬዚደንት አሚና ጉሪብ ፋኪም በዝርዝሩ ተካትተዋል፡፡ በዝርዝሩ ውስጥ የተካተቱት ሌላኛዋ አፍሪካዊት ሴት ናይጀሪያዊቷ ባለሃብት ፎሎሩንሽኮ ኣላኪጃ ናቸው፡፡
አሜሪካ በርካታ ሴቶችን በሃያላኑ ዝርዝር ውስጥ በማስገባት ከአለማችን አገራት ቀዳሚቱን እንደያዘች የታወቀ ሲሆን 100 የተለያዩ አገራት ፖለቲከኞችን፣ የኩባንያ ስራ አመራሮችን፣ በጎ አድራጊዎችን፣ ስራ ፈጣሪዎችንና ሳይንቲስቶችን ባካተተው በዘንድሮው የፎርብስ ሃያላን ሴቶች ዝርዝር ውስጥ የተካተቱት አሜሪካውያን ሴቶች 51 መሆናቸው ተነግሯል፡፡

Read 3552 times