Monday, 25 July 2016 07:11

የአተት ወረርሽኝ በቀጣዮቹ ሳምንታት ይባባሳል ተባለ

Written by  መታሰቢያ ካሣዬ
Rate this item
(31 votes)

- በከተማዋ 80 ሆቴሎችና 12 የጤና ተቋማት ታሸጉ
- 10 ሺ ኪሎ ምግብና 1200 ኪሎ ሥጋ ተወገደ

   በአዲስ አበባ ሰኔ 2 ቀን 2008 ዓ.ም መከሰቱ በይፋ በተገለፀው የአተት በሽታ የሚያዙ ነዋሪዎች ቁጥር እየጨመረ መምጣቱ የተገለፀ ሲሆን በሽታው በወረርሽኝ መልክ ሊከሰት እንደሚችልና በቀጣዮቹ ሳምንታት እንደሚባባስ የዩኤን የረድኤት ማስተባበሪያ አስታወቀ፡፡ በሽታው ከጎርፍ መከሰት ጋር ተያይዞ የሚስፋፋ መሆኑን የጠቆመው መረጃው፤ በመጪው ነሀሴ ወር ሊባባስ እንደሚችል አስታውቋል፡፡
በሌላ በኩል በከተማዋ ለህብረተሰቡ ንፅህና የጎደለው አገልግሎት ሲሰጡ ተገኝተዋል የተባሉ ከ80 በላይ ሆቴሎችና ምግብ ቤቶችን ማሸጉን የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የምግብ፣ መድሃኒትና ጤና ክብካቤ ቁጥጥር ባለስልጣን ገልጿል፡፡
ሰሞኑን በመዲናዋ የተለያዩ አካባቢዎች በሚገኙ ሆቴሎችና ምግብ ቤቶች ላይ ድንገተኛ ፍተሻና ቁጥጥር ሲያካሄድ መሰንበቱን የጠቆመው ባለሥልጣን መ/ቤቱ፤ የመመገቢያና የማብሰያ ዕቃዎቻቸው ንፅህና በአግባቡ ያልተያዘ፣ በቆሻሻ አወጋገድ ሥርዓታቸው ላይ ጉድለት የተገኘባቸውና ንፅህናውን የጠበቀ የምግብና መጠጥ አገልግሎት አልሰጡም ያላቸውን ከ80 በላይ ምግብ ቤቶች፤ ሆቴሎችና መጠጥ ቤቶች ማሸጉን አስታውቋል። በፍተሻው ወቅት የተገኙና ከአተት በሽታ ጋር ተያይዞ በህብረተሰቡ ጤና እና ህይወት ላይ አደጋ ሊያስከትሉ ይችላሉ የተባሉ ከ10 ሺ ኪ. በላይ ምግቦች፣ 120ኪ. ስጋና በርካታ አትክልቶች እንዲወገዱ መደረጋቸው ታውቋል፡፡
ይህ በእንዲህ እንዳለ በአተት በሽታ ተይዘው ወደ ተቋሞቻቸው ለሄዱ ህሙማን ተገቢውን የህክምና እርዳታ አልሰጡም የተባሉ 10 ክሊኒኮችና ሁለት ሆስፒታሎችም መታሸጋቸው ተገልጿል፡፡
የግል የጤና ተቋማቱ ለአተት ህሙማን ሊደረግ የሚገባውን የቅብብሎሽ ህክምና በአግባቡ አላከናወኑም በሚል ነው እርምጃው የተወሰደባቸው፡፡

Read 7228 times