Saturday, 30 July 2016 11:29

ሦስቱን መንግስታት በንጽጽር (ንጉሱ- ደርግ-ኢህአዴግ)

Written by  አሰፋ ጫቦ
Rate this item
(10 votes)

ከአዘጋጁ፡- ለአቶ አሰፋ ጫቦ በቃለ-መጠይቅ መልክ በኢሜይል ከላክንላቸው በርካታ ጥያቄዎች ውስጥ ለአራቱ
የሰጡትን ምላሽ ማቅረባችን ይታወሳል፡፡ ሰሞኑን ደግሞ፡- “ሦስቱን መንግስታት በንጽጽር እንዴት ይገልጹዋቸዋል?” በሚል
ለላክንላቸው ጥያቄ፣ አስፋፍተውና በመጣጥፍ መልክ ምላሽ ሰጥተውናል፡፡ በአንድ ጊዜ ለማስተናገድ ብዙ በመሆኑ በሁለት
ክፍል እናቀርበዋለን፡፡ የመጀመርያው የመልሱን ክፍል እነሆ፡-

“ያለፍክባቸውን ሶስቱን መንግስታት በንጽጽር እንዴት ትገልፃለህ?”
የሚለው በጣም ከባድ ጥያቄ ይመስለኛል። ዘርዘር ባደርገው ጋዜጣው በቂ ቦታ አይኖረው ይሆናል ብዬ ፈራሁ። ሰብሰብ ያደርኩ እንደሁ ደግሞ ከመልስ ይልቅ ተጨማሪ ጥያቄዎች የሚጋብዝ ይሆናል ብዬ ፈራሁ።  እስኪ መጠነኛ፤ መሀል መንገድ ፈልጌ ለማትኮር እሞክራለሁ።
ለዚህም ሁለት አብይትና ገላጭም ናቸው ብዬ የምገምታቸው ነጥቦች ላይ አተኩራለሁ። የመጀመሪያው እነዚህን 3 መንግስታት፤ ማለትም የንጉሰ ነገስቱን፤ የኢትዮጵያ ሕዝባዊት ዲሞክራሲያዊት ሪፐብሊክ (ኢሕድሪ (ደርግ) እና አሁን በስልጣን ላይ ያለውን መንግስት እንደ ሥርዓተ-መንግሥት (System of Government) ምን ይመስላሉ የሚለውን ቀንጭቦ ማየት ይሆናል። ሁለተኛው እነዚህን መንግሥታት በቁልፍነት ሲያሽከረክሩና  አድራጊ ፈጣሪ የነበሩትን  ግለሰቦች፣ ማለትም፣ ኃይለሥላሴን፤ መንግስቱ ኃይለ ማርያምንና መለሰ ዜናዊን ለማየትና ለማሳየት መሞከር ይሆናል። እንደ አጋጣሚ ሆኖ ሶስቱንም በቅርብ የማወቅ፤ አብሮ የመስራት፤ ከዚያም ፈግጠው-ፈግጠው ተባብለን ተለያይተናል። በቅርብ ርቀት (የቅርበት-ርቀቱ መጠን ቢለያይም) ሰብእናቸውንም የማየትና የመታዘብ እድል ነበረኝ። ይህ የዐይን ምስክርነቴ ለምለው ተጨማሪ ምንጭም ሆኖ ያገለግላል የሚል እምነት አለኝ። በፈግጠው ፈግጠው ጉዳይ፣ እኔ ውድ ዋጋ ከፍያለሁ። እየከፍልኩም ነው። ”… ወትሮም መንገደኛ ፊትና ኋላ ነው” የሚሉት ሆኖ እንጅ እነሱም ከፍለዋል። እርግጥ የእጁን ያላገኘው መንግስቱም አለ።

ሕገመንግሥት
የማንኛውም አገር ሥርዓተ-መንግስቱ መግለጫ ሕገመንግስቱ ነው። ሕገመንግሥት ማለት አንድ አገር የሚገነባበት ጽኑ መሠረቱ፤ ጣራውን ተሸካሚ አስተማማኝ ግርግዳውና፤ ደመና ዞር ባለው ቁጥር፣ ብርድ፤ ፀሐይ ብቅ ባለች ቁጥር፣ ሙቀት የማያስገባ፣ የረጋና የተረጋጋ ጣሪያ ያለው ጽኑ አዳራሽ እንደ ማለት ነው። እዚያ ታላቅ አዳራሽ ውስጥ ነው ክፍሎቹ እንደ ቤተሰቡ ዕውነት የሚከፋፈሉትና የሚደላደሉት:: ሕገመንግስትን መሠረታዊ ህግ፤ የሕጎች ሁሉ ምንጭ (እናት) (Basic Law,Fundamental Law) ይሉታል። ነውም! ስለሆነም፤ በሕገመንግስቱ ብንጀምር የሚሻል ይመስለኛል።
በንጉሱ ሕገ መንግስት (1948 ዓ.ም) እንጀምር። ይህም “የተሻሻለው የ1948 ዓ.ም ሕገ መንግስት” ተብሎ የሚጠራው ነው። ይህ ሕገመንግስት አብዛኛው ህዝብ ከማያውቀው ታሪክ፣ ሌላም ታሪክ ከኋላው አለ። ንጉሱ፤ “ለምንወደዉና ለሚወደን ሕዝባችን በራሳችን ፈቃድ ተነሳስተን ሰጠነው” እንደሚሉት አይደለም። የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ውሳኔ የፈደራል አክት (The Federal Act 1952) የሚባል አለ። ይህም ኤርትራን ከኢትዮጵያ ጋር በፌዴሬሽን ለማገናኘት የተባበሩት መንግስታት ውሳኔ ነበር። በአለም አቀፍ የሕግና የፖለቲካ ባለሙያዎች የተዘጋጀ ሕገ መንግስት አለ። ፌዴሬሽኑን ለመቀበል ይህንን የፌዴራል አከት መቀበል እንጅ አማራጭ አልነበረውም። ኢትዮጵያ ያኔ የነበራት የ1923 ዓ.ምቱ፤እጅግ ኋላቀር ሕገ-መንግስት ነበር። የፌዴሬሽኑ ርእሰ ብሔር ደግሞ ንጉሱ ሊሆኑ ነው። ስለዚህም ኤርትራን 25 ዓመት (1948-1923) ወደ ኋላ ከመውሰድ፣ ኢትዮጵያን 25 አመት ወደፊት መጎተት ይሻላል የሚል እርቅ ሃሳብ (Compromise) መሆኑ ይመስለኛል። ሌላው ቢቀር በወረቀት ላይ እንኳን ቢሆን ጎተት እናድርጋት እንደ ማለት ነው።
ቁልፉና ተፈላጊው ነገር ኤርትራን በዚህም ይሁን በዚያ ወደ እናት አገሯ መመለሱ ነበር፡፡ ብዙም ሳይሰነብት ኤርትራን ለዚህ ያበቃው ዘር መዘራት ተጀመረ። ይህ ያልተጣጣመም፤ ፈላጭ ቆራጭ ንጉስ ነገስትና ዘመናይ የሆነው የኤርትራ ሕግ አብሮ አለመሄድ፤ የፌዴሬሽኑ ማፍረስና መፍረስ መነሻ ምክንያቶች ሆኑ። እርግጥ አባባሽ የሆኑ ሌሎችም ምክንያቶች፣ ሰበቦች ሞልተዋል። ከመጀመሪያውም ቢሆን፣ ይሁን-ይሁን ተብሎ እንጅ ሁለንተናው ሲታይ የፌደራል መለኪያዎች አያሟላም ነበር የሚሉ የሕግም የፖለቲካም ምሁራን አሉ።
 ከዚህ፤ 131 አንቀጽ ከነበረው ከ1948 ዓም ሕገመንግስት ውስጥ 35ቱ የንጉሰ ነገስቱን ዝርያና ውርስ፣ ስልጣን የሚናገር ነው። ከዚህ ውስጥ አንዱ አንቀጽ የያዘው፣ ዘውድ በሳባ በኩል ከአይሁዱ ነገሥታት ከዳዊትና ከሰለሞን ሳይቋረጥ የመጣ፣ ኃይለስላሴም የዚያ ዝርያ ስለሆኑ ከእርሳቸው ዝርያ ለዘለዓለም አይወጣም የሚል ነው። እንዲህ ሲያዩት የሚገርም ነው። እኔን ይገርመኛል። መጀመሪያ ለስላሴ ኦሮሞ ናቸውና እዚህ ስለ ንግስት ሳባ ከሚወራው ትንግርት ውስጥ (እውነትነት ቢኖረው እንኳን) የሚያገባቸው ነገር ያለ አይመስለኝም። ከሁሉም በላይ ግን ኃይለስላሴ፤ ይህንን እስከ ወዲያኛው ሊያደርስ የሚችል፤ የሚመኙትን ዘውድ የሚያጓጉዝ አልጋ ወራሽ አልነበራቸውም። አልጋ ወራሽ የተባሉት አንደበታቸው ተይዞ አውሮጳ ለሕክምና ከሔዱ አመታት አልፏል። ንጉሱ መጃጀታቸው ደግሞ የአደባባይ ሚስጥር ነበር። ለሁሉም ለሁሉም በ1966-67 የኃይለ ሥላሴም ሆነ የዝርያቸውም መጨረሻ እስከ ወዲያኛው ሳይሆን ከርቸሌ እንደነበረ ያየነው ወይም የሰማነው ነው።
ያም ሆኖ የዚህ ህገመንግስት ገላጫ ባህርዩ አንዱና ቁልፉ ኢትዮጵያን እንዴት እንደሚያስቀምጥ ነው። “ኢትዮጵያ ማለት ምድሪቱ፤ ባህሩ፤ ደሴቶቹና ከላይ የከበበው ሰማይ ጭምር ነው” ይልና ይህ የማይደፈርና የማይቆራረስ ነው ይላል። ስለዚህም  ኢትዮጵያ  ማን እንደሆነች፤ የት እንደምትገኝ፣ ምኑና ምኑ ተሰባስቦ፣ ወጥና አንድ ኢትዮጵያ እንደሚያሰኛት በማያጠራጥር፤ በማያሻማ ቋንቋ ተጽፎ ተቀመጧል። ይህም አይደፈርም አይገሰስም ይላል።   
የደርግ ሕገመንግሥት፤ኢትዮጵያ የሶሺያሊስት አገር መሆኗን በማያሻማ ቋንቋ አስቀምጧል። ዛሬ ነፋሱን ተከትለንም ሶሺያሊስት፤ ካህኑ፤ አጥማቂው ጭምር የነበርነው ሁሉ “እኔኮ! ነገር ግን…!” ማለት ጀምረናል። እዚያ ውስጥ አልገባም። ከሐዲዎቹ ያላስተዋልነው ነገር ቢኖር አብዛኛው የምዕራብ አውሮጳ አገሮች በተለይም እስካንዲኔቪያ (Scandinevia) የሚባሉት ወይ ሶሺያሊስት ወይም የዚያ ጥምር መሆናቸውን ነው። ለምሳሌ የአሁኑ፤ የዛሬው፤ የፈረንሳይ መንግስት ሶሺያሊስት ነው። ይህ ደግሞ ወደ መቶ ዓመታት የሚጠጋ ታሪክ አለው።
የደርግ መንግስት፤ የኢትዮጵያ ማንነት ልክ የንጉሱ መንግስት ሕገመንግሥት ያለውን በተጠናከረ መልኩ ይደግመዋል። ኢትዮጵያ ነጻ የማትደፈርና የማትከፋፈል ነች ይላል። ሌላው የደርግን ሕገ መንግሥት ለየት የሚያደርገው፣ ይህ መንግስት የተመሠረተው ለነማን፤ በነማን እንደሆነ ይዘረዝራል። ይህም ዝርዝር “የሠርቶ አደሩ፤ የገበሬው፤ የምሁራን፤ የአብዮታዊው ሠራዊት፤ የእጅ ሠራተኞችና የተቀሩት የዲሞክራቲክ ኃይሎች መንግስት ነው !” ይላል። እዚህ ዝርዘር ውስጥ ያልገባ ቢኖር፤ “ሳይሰራ የሚባለው!” ነበር። ማለትም፤ ደርግ በዝባዥና አቆርቋዥ የሚላቸው መሆናቸው ነው። ደርግ ዛሬ ከመቃብሩ ቀና ብሎ ቢያይ “ምነው!?  ስምንተኛው ሽህ ገባ እንዴ!?” ሳይል የሚቀር አይመስለኝም፡፡
አሁን ደግሞ በሥራ ላይ ያለውን የኢህአዴግን ሕገመንግሥት ለማየት እንሞክር። ለመንደርደያ ያክል ይህንን ሕገመንግሥት ያረቀቀው፤ “ዶክተር” ፋሲል ናሆም መሆኑን መግለጹ ጥሩና አስፈላጊም ይመስለኛል። CONSTITUTION FOR A NATION OF NATIONS ,The Ethiopian Prospect የሚል መጽሐፍ ጽፏል። መጀመሪያ ነገር ይህ መጽሐፉ የኢትዮጵያ ሕገመንግሥት አይደለም። ለመንግሥቶች መንግሥት የወጣ ሕገመንግሥት ይለዋል። ትርጉሙ ግልጽ አይደለም። ለኔ ግልጽ አይደለም! ብቻ በዚህ ሕግ መንግስት፤ እንደ ፋሲል ናሆም አባባል፤ አቀራረብ ኢትዮጵያ የመጽሐፉም፤ የሕገመንግሥቱም ዋና ተዋናይና እምብርት አይደለችም እንደ ማለት ነው። ተለጣፊ መሆንዋ ነው። PROSPECTS  የሚለው ቃል ትርጉም ይኸውና፤ prospect,noun ,the possibility or likelihood of some future event occurring.” ምናልባት ሊሳካ ይችላል ማለት ነው። ምናልባት ሊሳካ የሚችለው ምኑ ይሆን? አልነገረንም! የሚጽፈው ስለ ኢትዮጵያ ስለሆነ ኢትዮጵያ፤ እንደ ኢትዮጵያነትዋ ላትሳካ ትችላለች ማለት ይሆን? ይህም የሚያስኬድ ትርጉም ይመስለኛል። ሌላው፤ወያኔ ይህንን የማይመስል ነገር ተግባራዊ ማድረጉ አይሳካለት ይሆናል ለማለት ይሆን? አሁን ምድሪቱ ላይ የምታየውን ዕውነት ልብ ያልን እንደሆነ፣ ይህኛውም ትርጉም የበለጠ የሚመስል ነው።
ፕሮፌሰር ቲዎዶር ቨስታል፤ TheodoreM.Vestal “ETHIOPIA:A Post-Cold War African State” በሚለው መጽሐፋቸው ስለ ፋሲል ኖሆም በሰፊው ጽፈዋል። በገጽ 95-96 ይገልጹታል። በገጽ 102 የግርጌ ማስታወሻም ላይ፣ ፋሲል በ1966 የኃይለ ሥላሴን ሕገመንግሥት፤ በኋላም ትንሽ ቆየት ብሎ የደርግን ህገ መንግስት አርቃቂ መሆኑና አሁን ደግሞ ለሶስተኛ ጊዜ የዚህኛው አርቃቂ መሆኑንም ያመለክታሉ። ሌሎች ምሁራን መፈልፈል እንዲቻል የሲቪል ሰርቪስ ኮሌጅንም ያቋቋመው ፋሲል ናሆም ነው።
የፋሲልን መጽሐፍ አንድ ቀን አበራየዋለሁ፤ ወይም “ገላልጦ ለማየት” እሞክራለሁ የሚል ሐሳብ ስለአለኝ እመለስበታለሁ። የፋሲል መጽሐፉ ሽፋን ሁለት የአኩሱም ሐውልቶችና በመካከሉ አሮጌ የብራና ጽሁፍ የሚመስል ተሸንቅሯል። ወደ ጥንታዊቱ ዘመነ አኩሱም እንመልሳችኋለን ነው መልእክቱ? መቼም ትርጉም አለው! ከሌሎች ነጥቦች ጋር ሲገናዘብ፣ ለዚህም ትርጉም ቦታ አለው።
የዛሬን የኢትዮጵያን ማንነትና ምንነት ለመረዳት፣ የኢህአዴግን  ሕገመንግሥት አንቀጽ 2 ማንበብ ይበጃል። ኢትዮጵያ ማለት የፌዴሬሽኖቹ አባላት ጥርቅም ነው ይልና ዳር ድንበሯ ግን በስምምነት ይወሰናል ይላል። ስለ ምድሩ ስለ ሰማዩ፤ ስለ አየሩ፣ ስለ ባሕሩ የሚያወሳው ነገር የለውም። እርግጥ ስለ ባህሩ የሚያነሳው ነገር የለዉም። ቀይ ባህርን ኢትዮጵያ በቅኝ ገዥነት ያገኘችው ስለሆነ፣ የኢትዮጵያ አካል አይደለችም፣ አልነበረችምም ብሎ መለስ ዜናዊ ለተባበሩት መንግስታት ደብዳቤ ጽፏልና፣ ስለ ባህር ንብረት ሊነሳ አይችልም። ዳር ድንበሯ የተከበረ፤ የማይደፈር፤ የማይቆራረስ ነው አይልም። አንዴ ኤርትራ ተቆርሶ ሔዷልና፣ ከአሁን በኋላ አይቆራረስም ማለቱ ትርጉም የለውም ብለውም ሊሆን ይችላል። በህግ Precedent ይሉታል። አስቀድሞ የተወሰነውን፣ ይህኛውም ይከተላል እንደ ማለት ነው።
በዚህ ላይ አሁን ሲነገር እንደምሰማው፤ (ተጠናቆ እንደሁ አላውቅምና) ለሱዳንም መሬት ይሰጥና ከዚያ በኋላ ይመስለኛል የምዕራቡ ድንበራችን የሚወሰነው። በምስራቅ በኩል ያለው ድንበራችን ጉዳይ በእጃችን ያለ አይመስለኝም። ሶማሌ መፈረካከሷ ብቻ ሳይሆን ሞቃዲሾን ያማከለው የሱማሌ መንግስት የሚሉት፣ እንኳንስ ድንበር ሊካለል፣ ለራሱም ቢሆን ከመንግስት ይልቅ የመንግስት ቅዠት ነው የሚመስለው።
ብቻ ብዙ ማለት ሲቻል ላሳጥረው። በኢህአዴግ ሕገመንግሥት አንቀጽ ሁለት መሠረት፤ ኢትዮጵያ የታወቀ፣ የጸና፣ የማይሸራረፍ፣ የማይቦጨቅ ዳር ድንበር የላትም፡፡

መሪዎቹ
አሁን ደግሞ በሥልጣን ላይ ያለ መንግስት፣ አድራጊ ፈጣሪ የነበሩ መሪዎች፤ ማለትም ኃይለ ሥላሴን፤ መንግስቱ ኃይለማርያምንና መለስ ዜናዊን በጨረፍታ ለማየት እንሞክር።
በኔ አስተያየት፤ አስተያየት ብቻ ሳሆን ከተግባራቸው በመነሳት እነዚህ ሶስት ግለስቦች ከጠበቅነውና ከምንጠብቀው በላይ የሚጋሩት የጋራ ባሕርይ ያላቸው ይመስለኛል። ከእነዚህ የጋራ ባሕርያት ውስጥ  ሰውን የመረዳትና የመመዘን ብቻ ሳይሆን ሰንጥቆ ውስጡን የማየት፤ሰውን ፈጽሞ አለማመን፤ የሰውን ጠንካራና ደካማ ጎኑን ማወቅ፤ ጠንካራ ጎን አለው ብለው የገመቱትን ቢቻል ማራቅ፣ ካልሆነም ማጥፋት፤ በጣም የከረረ ራስ ወዳድነት፤ ርህራሔ (Empathy,Smpathy) የሚባለውን ነገር ጨርሶ አለማወቅ፤ ከዚህም የተነሳ ከወዳጅ ዘመድ፣ ጓደኛ ጀምሮ ይበልጠኛል ብሎ ያመኑትን ሰው ለማጥፋት ወደ ኋላ አለማለት፤ ለድርጊታቸው ተቀባይነት ያለው በአገር ፍቅር የተቀባባ ምክንያት መስጠትና ከራሳቸው በስተቀር ምንንም ማንንም አለመውደድና ያቀረቡ መምሰል እንጅ ሰው አለማቅረብ ----- ገላጮቹ ናቸው። ዋና መመሪያቸው፤ “ጠርጥር ገንፎም ውስጥ አለ ስንጥር!” የሚል አይነት ይመስላል።
የሰውን ልጅ ስነአዕምሮ አጥኝዎች (Psychologists) ይህንን ከአዕምሮ ህመም እንደ አንዱና ለማከምና ለማዳን የማይቻል መሆኑን ይገልጻሉ። ለማከምና ለማዳን የማይቻለው፣ የዚህ አይነት ህመም ያለባቸው ሰዎች በጣም ጠልቀው የሚያዩ ስለሆነ፣ ሐኪሙ ለሚጠይቀው ጥያቄ “የሚፈልገው መልስ ይህ ነው!” ብለው አውቀው፣ ወስነው ስለሚመልሱ፤ በሩን መዝጋት ስለሚችሉ፣ ውስጥ ገብቶ አይቶ መድኅኒትም ሆነ ምክር መስጠት አይቻልም ነው የሚሉት።
ይህን የአዕምሮ ህመም አይነት Sociopath  ይሉታል። በአማርኛ ለመተርጎም ይከብደኛል። ምናልባትም ዕቡይ ማለት ይቻል ይሆናል። ይህንን ለመረዳት M.E Thomas  የምትባል የሕግ ፕሮፌሰር Confessions of a Sociopath: A Life Spent Hiding in Plain Sight: በሚል የጻፈችው ዝነኛ መጽሐፍ አለ። የመጽሐፉ ተጨማሪ ርዕስ፡- A Life Spent Hiding in Plain Sight የሚል መሆኑን ልብ ይሏል! አብረውን ናቸው ግን አንለያቸውም፤ አናውቃቸውምም ለማለት ነው። እንደሌላው በሽታ በአደባባይ የሚገለጥበት መንገድ የለውም ለማለት ነው። ራስዋ የዚህ ሕመምተኛ መሆንዋን አምና፣ በምርጥ የአዕምሮ ሕመም ሐኪሞች (Psychiatrists) ተመርምራ የጻፈችው ነበር።  እኔም ይሕንን መጽሐፍ ካነበብኩ በኋላ አንድ በዚህ ሙያ  25 አመት የሰራና ልምድ ያለው፣በሚያስተምርበት ተመዝግቤ አንድ የሳይኮሎጂ ትምህርት ወሰድኩ። ከዚያ በፊት ዩኒቨርስቲ እንደ መግቢያ የወሰድኩት የሳይኮሎጅይ ትምህርትና በንባብም ያዳበርኩት ተጨምሮ ነው እዚህ ከሙያዬ ውጭ ይህን አስተያየት እንድሰነዝር የገፋፋኝ። አንድ ቀን ክፍል ውስጥ ይህንኑ ፕሮፌሰር፤ “ታዲያ ስለ Sociopath ምን ይሻላል?” አልኩት። “መሆኑን ከለየህ፣ ከቻልክ ከአጠገቡ ሮጠህም ቢሆን አምልጥ!” ያለኝን አስታወስኩና ሳቅሁኝ። ሩጬ አላመለጥኩምና!
ባለሙያዎቹ ይህ የአዕምሮ ሕመም፤ ሁለት ምንጭ አለው ይላሉ። አንዱ በተፈጥሮ (Genetic) ሲሆን ሁለተኛው ከአስተዳደግ ነው ይሉናል። Nature and Narture ይህንን አሁን ባለው ማስረጃ ኃይለ ሥላሴን እንመለከት። የ19ኛው ክፍለ ዘመን ሰው ነበሩ። ይህም ማለት ወጣቱ ምንሊክ ነበሩ ማለት ነው። የገዙት፤ የነዱት ደግሞ በ20ኛው ክፍለ ዘመን ነበር። ይህም ማለት ዘመኑ የርሳቸው ዘመን አልነበረም (anamoly) ለማለት ነው። ቢሆንም ፊደልም ቢሆን ከፈረንጅ ጋር ቆጥረዋል። ሰዉ ማመስገን የማይሆንላቸው ተፈሪ መኮንን፤ “ሕይወቴና የኢትዮጵያ እርምጃ“ በሚለው መጽሐፋቸው፤ የሚያመሰግኑት ይህንኑ ፈረንጅና አንድ ከኦርቶዶክስ የኮተለክ አስተማሪያቸውን ብቻ ነበር። ተፈሪ መኮንን፤ እናት፣ አባት፣ ወንድም፣ እህት የሌላቸው፣ በመጥፎ ሞግዚት ያደጉ ነበሩ። የዘውዴ ረታን፤ “ተፈሪ መኮንን” እና የፈታውራሪ ተክለሐዋሪያትን፤ “ሜሟር” ማንበብ ነው። አባት የላቸውም ያልኩት በሕይወት ሳይሆን ከስራቸው የተነሳ፣ ራስ መኮንን የሚያሳድጉ አባት አልነበሩም ለማለት ነው። ይህ እንግዲህ የኃይለ ሥላሴን ድብቅና ሽምቅ ፍቅር አልባ ነፍስ የቋጠረ ይመስለኛል። ጸጋዬ ገብረመድኅን፤ “በክልስ አባ ልበ እግረኛ” ግጥሙ፤ “..ከራሱ በስተቀር ሌላ ያለው የማይመስለው..” የሚለው አይነት መሆኑ ነው።
ከሌላ እናት የሚወለዱ አንድ ወንድማቸው፤ ደጃዝማች ይልማ፤ ቢኖሩም እሳቸውንም ቢሆን በመጽሐፋቸው ውስጥ ይከሳሉ። ይቀናቀነኝ ነበር! ይላሉ።
(ይቀጥላል)





Read 11851 times