Monday, 19 September 2016 07:30

በሳምንቱ ከ11 ሺህ በላይ የደቡብ ሱዳን ስደተኞች ኢትዮጵያ ገብተዋል

Written by 
Rate this item
(10 votes)

ከ292 ሺህ በላይ የአገሪቱ ስደተኞች በኢትዮጵያ ይገኛሉ

      ባለፈው ሳምንት ብቻ ከ11 ሺህ በላይ የሚሆኑ ደቡብ ሱዳናውያን ስደተኞች በጋምቤላ ክልል በኩል ወደ ኢትዮጵያ እንደገቡ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የስደተኞች ኮሚሽን ትናንት ባወጣው መግለጫ አስታወቀ፡፡
በአገሪቱ እየተባባሰ የመጣው ግጭትና ውጥረት በርካታ ዜጎች አገራቸውን ለቀው ወደ ጎረቤት አገራት እንዲሰደዱ እያስገደዳቸው ነው ያለው ኮሚሽኑ፤ ባለፈው ሳምንት በስደት ወደ ኢትዮጵያ የገቡት ከ11 ሺህ በላይ ደቡብ ሱዳናውያን በኢትዮጵያ የሚገኙ የአገሪቱ ስደተኞችን ቁጥር ከ292 ሺህ በላይ እንዳደረሱት አስታውቋል፡፡
አብዛኞቹ ስደተኞች ናስር፣ ማባን፣ ማቲያንግና ማዩት በተባሉት የደቡብ ሱዳን አካባቢዎች የተጠናከረ ወታደራዊ እንቅስቃሴ በማየታቸውና አዲስ ግጭት ይከሰታል ብለው በመስጋት ስደትን የመረጡ ደቡብ ሱዳናውያን እንደሆኑም አስረድቷል፡፡
ባለፈው ሳምንት በጋምቤላ ክልል ድንበር አቋርጠው ወደ ኢትዮጵያ ከገቡት ደቡብ ሱዳናውያን ስደተኞች፤ አብዛኞቹ ሴቶችና ህጻናት ናቸው ያለው ኮሚሽኑ፣ ብዙዎቹም የኑዌር ጎሳ ተወላጆች እንደሆኑና 500 ያህሉ ስደተኞች ያለ ወላጅ ብቻቸውን ስደት የወጡ ህጻናት እንደሆኑ ገልጧል፡፡
በደቡብ ሱዳን የእርስ በእርስ ግጭት ሳቢያ ወደ ጎረቤት አገራት የተሰደዱ የአገሪቱ ዜጎች ቁጥር ከአንድ ሚሊዮን በላይ መድረሱን ያስታወቀው ተቋሙ፤ ከእነዚህም መካከል ከ185 ሺህ በላይ የሚሆኑት ካለፈው ሃምሌ ወር ወዲህ ስደት የወጡ እንደሆኑ አክሎ ገልጿል፡፡

Read 2580 times