Monday, 19 September 2016 07:47

የትግራይ ህዝብ የለውጡ አጋር እንጂ ተጠቂ ሊሆን አይገባም

Written by  መርስዔ ኪዳን ሜኔሶታ፤ ሃገረ አሜሪካ
Rate this item
(4 votes)

     በሃገራችን እየተካሄደ ባለው ህዝባዊ አመፅ ምክኒያት ብዙ የሰው ህይወት መጥፋት፣ የአካል ጉዳትና የንብረት ውድመት እየደረሰ ነው። ይህ ሁኔታ እንዲፈጠር ያበቁ ብዙ ምክኒያቶች ቢኖሩትም አንዱና ዋነኛው ምክኒያት በሃገሪቱ ውስጥ ፍትሃዊ የሆነ የፖለቲካ ስርዓት አለመኖሩ ነው። ኢትዮጵያ ብዙ ብሄሮች ብቻ ሳይሆን ብዙ ፖለቲካዊ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ አመለካከት ያለው ህዝብ የሚኖርባት አገር ነች። ሆኖም ያለው የፖለቲካ ስርአትና በስልጣን ላይ ያለው መንግስት ይህንን ልዩነት ማክበርና ማስተናገድ ባለመቻላቸው ብቻ ሳይሆን ፍላጎትም ባለመኖሩ ለዚህ ችግር ተዳርገናል። ኢህአዴግ የሚመራው መንግስት  የተፈጠረውን ችግር በተመለከተ በቅርቡ ያወጣው መግለጫ የችግሩን መጠን በውሉ ያላጤነና ጭራሽም ዋነኛውን የችግሮቹን ሁሉ መንስኤ ያልተመለከተ ነው። ለሙስናውም፣ ለመልካም አስተዳደር እጦቱም፡ ለብሄር ነክ ጥያቄዎችም፤ ለሌሎች ችግሮችም ምክኒያት የሆኑት ዋነኞቹ መሰረታዊ ችግሮች ህዝብ ያሻውን የሚመርጥበት ዴሞክራሲያዊ ስርአት አለመኖር፣ ህዝብ ሲበደል ብሶቱን የሚገልፅበት ነፃ መድረክ መጥፋት፣ የተለያዩ የፖለቲካ አመለካከቶች የተወከሉበት ፓርላማ አለመኖር፣ የአገሪቱ ህግ አውጪና ህግ አስፈፃሚ አካላት መቶ በመቶ በኢህአዴግ ቁጥጥር ስር መሆን፣ የፍትህ አካላት በነፃነት ለመስራት አለመቻል ናቸው።
በኦሮሞና በአማራ ክልሎች የተነሱት ተቃውሞዎች መነሾዎች የተለያዩ ይሁኑ እንጂ ዋነኛው ምክኒያት ከላይ የዘረዘርኳቸው መሰረታዊ ችግሮች ውስጥ ውስጡን ሲብላሉ ቆይተው በመፈንዳታቸው ነው። የጊዜ ጉዳይ ነው እንጂ ነገሮች ካልተስተካከሉ የትግራይም ሆነ የሌላው ክልል ህዝብ መነሳቱ አይቀርም። እነዚህ ችግሮች ከብሄር ብሄር ሳይለዩ ሁሉንም ያማረሩ መሆናቸው የታወቀ ሆኖ ሳለ፤ አንዳንድ ፅንፈኛ አካላት ሁኔታውን አንዱ ብሄር ተጠቃሚ፣ አንዱ ብሄር ተጎጂ እንደሆነ አድርገው በመቅረፅ ለአገሪቷም ሆነ ለየትኛውም ህዝብ የማይበጅ፣ አንድ ብሄር ላይ ያነጣጠረ ዘመቻ በማካሄድ ላይ ይገኛሉ። በተለይም በኤርትራ መንግስት ባጀት ተበጅቶላቸው የሚንቀሳቀሱ ቡድኖች በግልፅ በአንድ ብሄር ላይ በታሪክና በህግ ተጠያቂ የሚያደርግ አደገኛ ዘመቻ በማካሄድ ላይ ይገኛሉ። እውነት ለኢትዮጵያ ህዝብ ቀና የምንመኝ ሰዎች ይህንን ድርጊት በጋራ ልናወግዘውና ልንቃወመው ይገባል።
በዚህ አጭር ፅሁፍ ትግሬው በዚህ መንግስት በተለየ ተጠቅሟል የሚለው አመለካከት ትክክል እንዳልሆነ፣ በኦሮሞ፣ በአማራና በሌሎችም ክልሎች ያሉ በደሎች በትግራይም እንዳሉ እንደውም የበለጠ አሳሳቢ እንደሆኑ፣ ትግሬዎች በኢትዮጵያ ውስጥ መፈጠር ለሚገባው ፍትሃዊና ዴሞክራሲያዊ ስርአት ዋነኛ ባለድርሻና ተዋናይ መሆን እንደሚገባቸው፣ ይህን ለውጥ ለማምጣት የሚደረገው ትግልም ሰላማዊና ሰላማዊ ብቻ መሆን እንዳለበት ለማስገንዘብ እሞክራለሁ።
ትግሬው በዚህ መንግስት ከሌላው በተለየ ተጠቃሚ ሆኗልን?
ሕወሓት የበላይ የሆነበት የኢትዮጵያ ህዝቦች አብዮታዊ ዴሞክራሲያዊ ግንባር (ኢህአዴግ) ስልጣን በያዘ ማግስት፣ አብዛኛውን ቁልፍ የፌደራል መንግስት ስልጣናት የሕወሓት አባላት እንደያዙ የታወቀ ነው።  በተለይ ደግሞ የመከላከያ ሃይሉ ሙሉ ለሙሉ ሊባል በሚችል ሁኔታ በሕወሓት ሰራዊትና ወታደራዊ አመራር ስር መውደቁ ይታወቃል። በጊዜው አዲስ የተመሰረቱት ክልሎችም ከሕወሓት አማካሪ ተመድቦላቸው እንደነበር የሚታወስ ነው። ይህ ሁኔታ ከጊዜ ወደ ጊዜ በመጠኑም ቢሆን እየተለወጠ የመጣ ቢሆንም ሙሉ በሙሉ ተስተካክሏል ማለት አይቻልም። ታዲያ ባለፉት ሃያ አምስት አመታት የነዚህ የሕወሓት ባለስልጣናትን መብዛት የተመለከቱ የሌላ ብሄር ተወላጆች፣ ትግሬ በተለየ ተጠቃሚ የሆነበት ስርዓት የተፈጠረ እንዲመስላቸው ሆኗል። ሆኖም ትግሬው ከሌላው ብሄር በተለየ ተጠቅሞ እንደሆነ ለመመርመር መመልከት ያለብን እነኚህን ጥቂት ባለስልጣናት ሳይሆን አብዛኛው ትግሬ የሚኖርበትን የትግራይን ክልል ነው።
የትግራይ ክልል ከሌሎች ክልሎች ጋር በኢኮኖሚያዊ፣ ፖለቲካዊና ማህበራዊ መስኩ ሲወዳደር በተለየ ተጠቅሟል የሚያስብል ሁኔታ አንድም የለም። እንደውም ህዝቡ ክልሉን ለማሳደግና ለማልማት ከሚጥረው ጥረት አንፃር ሲታይ፣ ያለው መንግስት አጋዥ ሳይሆን ማነቆ ነው የሆነበት ማለት ይቻላል። ለምሳሌ መላው የትግራይ ህዝብ ክልሉን ለማልማት፣ የትግራይ ልማት ማህበርን አቋቁሞ የበኩሉን ድርሻ ለመወጣት ሲጥር ቆይቷል፤ ሆኖም ሕወሓት የልማት ማህበሩን በነፃ እንዲንቀሳቀስ ሊፈቅድለት ስላልቻለ አብዛኛው የልማት ማህበሩ አባል ራሱን ለማግለል ተገዷል። የትግራይ ልማት ማህበር በመጀመሪያዎቹ አመታት በሚሊዮን የሚቆጠሩ አባላት ያሉት፣ የክልሉ መንግስት ከሚሰራው በላይ ትምህርት ቤቶችንና ጤና ጣቢያዎችን የሚሰራ ማህበር ነበር። አሁን ግን ከህዝቡ ባለቤትነት ወጥቶ በሕወሓት ቁጥጥር ስር በመውደቁ አብዛኛው አባላቱ በየወረዳቸውና አውራጃቸው የየራሳቸውን የልማት ማህበራት በመፍጠር ትተውት ወጥተዋል።
በትግራይ ክልል የሚኖረው ህዝብ የአካባቢውን በረሃማነት ለመለወጥ በዓመት ለሁለት ወራት ነፃ የጉልበት አገልግሎት የሚሰጥ ሲሆን ከክልሉ ውጪ የሚኖረው ህዝብ ደግሞ በየወረዳው ትምህርት ቤቶችንና ጤና ኬላዎችን በመስራት ከፍተኛ ርብርብ ያካሂዳል። ይህ ህዝቡ የሚሰራው ስራ ክልሉን በነዚህ መስኮች የተሻለ ውጤት እንዲያስመዘግብ አስችሎታል። ይህ የህዝቡ ጥረት ባይኖርበት ኖሮ የክልሉ መንግስት ብቻ የሚሰራው ስራ ከሌሎች ክልሎች ያነሰ ይሆን ነበር።
በኢንቨስትመንት ደረጃ ክልሉ ገብቶ ለመስራት ፍላጎት ያለው ብዙ ህዝብ ቢኖርም በክልሉ ያለው የአስተዳደር ብልሹነት አላሰራ ስላላቸው አብዛኞች ነጋዴዎች በአዲስ አበባ ወይም ሌሎች ክልሎች ሄደው ለመስራት ተገደዋል። በክልሉ የሚገኙ የተፈጥሮ ሃብቶች ኤፈርት በመባል በሚታወቀው የሕወሓት የንግድ ድርጅት ስር ካልሆነ በስተቀር ሌሎች የግል ነጋዴዎች እንዲሰሩባቸው የሚጋብዝ ሁኔታ የለም። ኤፈርት የሚባለው የንግድ ድርጅት አትራፊ የሆኑ የንግድ ዘርፎችን በሞኖፖል በመያዝ ሌሎች ነጋዴዎችን ከጨዋታ ውጪ እንዲሆኑ የሚያደርግ ነው። የክልሉ ህዝብ ድርጅቱ በስሙ የተቋቋመ ቢሆንም አንድም ግዜ የአፈፃፀም ሪፖርት ተደርጎለት አያውቅም። የድርጅቱ ትርፋማነት አጠያያቂ ባይሆንም ትርፉ ምን ላይ ዋለ? ትግራይን መልሶ ለማቋቋም ምን ተደረገ? ለሚለው ጥያቄ ምንም ምላሽ የለም። በዚህ ድርጅት ስር የተመዘገቡት ንብረቶች ለባለቤቱ ለትግራይ ህዝብ የሚሸጋገሩበትን መንገድ ብዙዎቻችን ብንጠቁምም ሕወሓት ይህን ጥያቄ ለመመለስ ምንም ፍላጎት አሳይቶ አያውቅም፡፡
በማህበራዊ መስኩ የየክልሎቹን የስራ አፈፃጸም ብቃት ማሳያ ይሆን ዘንድ አንድ ላይ የተጀመሩትን የባህርዳር፣ የመቀሌና የአዋሳ የስፖርት ስቴድየሞች እንመልከት። የመቀሌ ስቴዲየም ከባህርዳሩም ሆነ ከሁለቱም በኋላ ከተጀመረው ከአዋሳ ስቴዲየም እኩል እንኳ ሊጠናቀቅ አልቻለም። ሕወሓት በዓሉን ሊያከብር ሲል በለብ ለብ ከተሰራ በኋላ ለመጨረስ ዞር ብሎ እንኳን ያየው የለም። የመቀሌ ሕዝብ በንፁህ ውሃ እጥረት ሲሰቃይ ይኽው ስንት አመት አስቆጠረ? በጣም የምንኮራባቸውን የእነ አፄ ዮሃንስን፣ እነ አሉላ አባነጋን፣ የአድዋ ድልንና ሌሎች ታሪካዊ እሴቶቻችንን ለመጠበቅና ለመጪው ትውልድ ለማስተላለፍ የተነሱ ቀና ኢትዮጵያውያንን አላሰራ በማለት ህዝቡን አፍኖት ይገኛል። ከላይ የዘረዘርኳቸውን ሁኔታዎች በቅጡ የተረዳ ሰው፣ ትግሬው ከሌላው ኢትዮጵያዊ ወገኑ የበለጠ ተጠቅሟል ሊል አይችልም።
ብዙዎች ታዲያ ይህ ሁሉ ችግር ካለበት ለምን ትግሬውም እንደ ሌላው አይቃወምም? ብለው ይጠይቃሉ። በመጀመሪያ ደረጃ ትግሬው አይቃወምም የሚለው ድፍን ድምዳሜ ትክክል አይደለም። ብዙ የትግራይ ልሂቃንና ፖለቲከኞች ከሌሎች ባልተናነሰ ሁኔታ መንግስት ላይ የሰላ ትችትና ተቃውሞ ያቀርባሉ፡፡ ለዚህም የቀድሞ የድርጅቱ አባል የነበሩት ጄ/ል ፃድቃን ገ/ትንሳይ፣ ጄ/ል አበበ ተክለሃይማኖት፣ ገብሩ አስራት፣ ስዬ ኣብረሃ፣ አስገደ ገ/ስላሴ፣ ፕ/ር ተኮላ ሓጎስ፣ ኣብረሃ በላይ፣ ፕ/ር መድሃኔ ታደሰ፣ አብረሃ ደስታ፣ ፕ/ር ገብሩ ታረቀ፣ ዶ/ር ሃይሉ አርአያ እና ሌሎችንም እንደ ምሳሌ መዘርዘር ይቻላል። ከነዚህም አንዳንዶቹ ልክ እንደ አማራው፣ ኦሮሞውና ሌላው ተቃዋሚ እስር፣ እንግልትና ስደት ደርሶባቸዋል። እነኚህ ግለሰቦች ናቸው፤ አብዛኛው ትግሬ ግን ሕወሓትን ሲቃወም አይታይም የሚለው ክርክር የተወሰነ እውነታ አለው። ግን ደግሞ ምክኒያታዊ ነው። በትጥቅ ትግሉ ወቅት ልጁን፣ ወንድሙን፣ እህቱን፣ ጓደኛውን ያላጣ ትግሬ የለም። በ17 ዓመቱ ትግል ከ60ሺሕ በላይ ወጣቶችን ያጣው ህዝብ፤ በትግሉ ያገኘውን አንፃራዊ ሰላም እንዲህ በቀላሉ ሊያጣው አይፈልግም። ሌሎች በቀላሉ ሕወሓትን ለመቃወም የሚነሳሱትን ያክል ትግሬውም እንዲነሳ መጠበቅ ይከብዳል። ነገር ግን በጊዜ ሂደት በስልጣን ላይ ያሉት የሕወሓት መሪዎች፣ ከ60ሺሕ በላይ ወጣቶቹ የተሰዉበትን ዓላማ ዘንግተው ስልጣናቸውን እንደ ርስት ሲንከባከቡ ሲመለከትና የህዝብ መብት ሲደፈጠጥ ሲመለከት፣ ወንድሞቼና እህቶቼ የሞቱለት መብቴ ተረገጠ የሚል ከፍተኛ ቁጭትና ሃዘን ውስጥ ገብቷል።
ሌላው ትግሬዎች የኢህአዴግን በደል አይቃወሙም የሚለው አስተያየት የሚፈጠረው የትግራይን ህዝብና ሕወሓትን ለይቶ ካለማየት ነው። የትግሬዎችን ጥቅም የሚነካ ነገር ላይ አለመስማማት እንደ ሕወሓት ደጋፊነት የሚያስቆጥርበት ሁኔታ ተፈጥሯል።  አንዳንድ ሰዎች የትግሬ የበላይነት አለ ሲሉ፤ አይ ስህተት ነው ችግሩም በደሉም ሁላችንም የምንጋራው ነው እንጂ ትግሬ በተለየ የተጠቀመበት ሁኔታ የለም ብለን የምንከራከርን ሰዎች፣ ያለውን በደል እንደማንቃወም ተደርጎ ይወሰዳል። የሑመራ፣ ወልቃይትና ፀገደ አከላለል ጉዳይ ጥሩ ምሳሌ ይሆናል። አብዛኛው ትግሬ በሑመራ፣ ቃፍታ፣ ወልቃይትና ፀገደ ወረዳዎች የሚኖሩት ኢትዮጵያውያን ትግሬዎች መሆናቸውን ያውቃል። ስለሆነም ቋንቋን መሰረት ያደረገ የፌደራል ስርዓት ሲፈጠር እነኚህ ወረዳዎች በትግራይ ክልል ውስጥ መመደባቸው ተገቢ ነው ብሎ ያምናል። ታዲያ ወልቃይት በአማራ ክልል ስር ይሁን የሚል ተቃውሞ ሲነሳ አብሮ እንዲነሳ እንዴት ይጠበቃል። ወቅታዊ በመሆኑ የወልቃይትን ጉዳይ በትንሹም ቢሆን ዘርዘር አድርጎ ማየቱ ይበጃል።
በአንድ በኩል የወልቃይት ህዝብ ትግሬ ሳይሆን አማራ ነው፤ ስለሆነም በአማራ ክልል ውስጥ ይታቀፍ የሚል አቋም የያዙ አሉ። ይህ አቋም ከእውነታው ፍፁም የራቀና በውጭ ሚዲያ ተደጋግሞ ስለተነገረ አብዛኛው ሰው እውነት የመሰለው አቋም ነው። በ1987 ዓ.ም. የተደረገው ቆጠራ የሚያሳየው፣ በቦታው የሚኖረው ህዝብ በአመዛኙ ትግሬ መሆኑን ነው።


ይህን መረጃ አንዳንዶች ቆጠራው የተካሄደው በኢህአዴግ ግዜ ስለሆነ አንቀበለውም ይላሉ። ሆኖም በኢህድሪ ወይም ደርግ ግዜ የተሰሩ የብሄር ጥናቶችም የሚያመላክቱት በነኚህ ወረዳዎች የሚኖረው ህዝብ በአመዛኙ ትግሬ መሆኑን ነው። ከዚህ በታች የምትመለከቱተ ካርታ በ1971 ዓ.ም. የተዘጋጀ ሲሆን እንደሚታየው በጊዜው በሰሜን ጎንደር ማለትም ሑመራ፣ ወልቃይት፣ ፀገደና ፀለምቲ ውስጥ የሚኖረው የትግርኛ ተናጋሪው ብሄረሰብ እንደሆነ ያሳያል። የትግራይ ህዝብ ለ17 አመታት ባደረገው ትግልም የወልቃይት ህዝብ ዋና ተሳታፊ ከመሆኑም ባሻገር ወልቃይት የሕወሓት ደጀን የነበረ ቦታ እንደነበር ይታወቃል። ይህ ማለት በነኝህ አከራካሪ ቦታዎች አማራው አይኖርም ነበር ማለት አይደለም። ከቀድሞም ቢሆን ሁለቱ ህዝብ አገው፣ ኩናማና ሌሎች ብሄሮችንም ጨምሮ አብሮ ይኖር እንደነበረ ማወቅ ይገባል። ነገር ግን ከላይ በአሃዙ ማየት እንደሚቻለው በደርግ ጊዜ የነበረው ካርታም እንደሚያሳየው በአካባቢው የሚኖረው ዋነኛ ብሄረሰብ ትግሬው ነው።
ይህን መረጃ የተመለከቱ ሰዎች ታዲያ ለምን ህዝቡ አማራ ነን ብሎ ጠየቀ? ይላሉ። ይሄም ተደጋግሞ ስለተነገረ እውነት የመሰለ ውሸት ነው። በርግጥ በጎንደር የሚኖሩ ጥቂቶቹ በትክክልም ከወልቃይት አካባቢ የሆኑ አብዛኛው ግን የዛው የጎንደር አካባቢ ሰዎች ወልቃይት አማራ ነው ብለው ኮሚቴ አቋቁመው ተንቀሳቅሰዋል። ሆኖም ግን በወልቃይትም ሆነ በሌሎቹ አከራካሪ ቦታዎች እንዲህ አይነት ጥያቄ ከህዝቡ አልተነሳም። አብዛኛው ህዝብ የውጭ ሚዲያ፤ በወልቃይት ህዝቡ አማራ ነኝ ብሎ ጠየቀ እያለ በአርማጭሆ ወረዳ የተካሄደውን ስብሰባ ልክ ወልቃይት ውስጥ እንደተካሄደ አድርጎ በማቅረቡ የተሳሳተ መረጃ ሰለባ ሆኗል።
አንዳንዶች ደግሞ በዘር የሚደረግ መከፋፈል ትክክል አይደለም ስለዚህ በወልቃይት የሚኖሩት ትግሬም ሆኑ አማራ ወደ አማራ ክልል መዛወር አለባቸው የሚል አቋም ያራምዳሉ። በርግጥ ብሄርን ወይም ቋንቋን ብቻ ያደረገ ፌደራሊዝም እንደማይበጅ ብዙው ትግሬም ጭምር የሚስማማበት ነው። ግን ያ ማለት ቀድሞ በአፄ ሃይለስላሴም ሆነ በደርግ ግዜ የነበሩት አከላለሎች ትክክልና ፍትሃዊ ናቸው ማለት አይደለም። ጥያቄው ለምን በቋንቋ ይከፋፈላል ከሆነ፣ ሰሜኑ የቀድሞ የጎንደር ክፍል በትግራይ መካለሉን የምንቃወመውን ያክል ደቡቡ የጎንደር ክፍልም በአማራ ክልል መወሰኑንም መቃወም ይገባል።
ግማሹ የቀድሞ ትግራይ ክፍለሃገር ወደ አፋር ክልል እንዲካለል ተደርጓል። ይህ ወደ አፋር እንዲካለል የተደረገው ክፍል በጣም ሰፊና ብዙ ማዕድናት የታደለ ነው። ሆኖም አፋሮች የሚኖሩበት ስለሆነ፣ በአፋር ክልል ስር መሆኑ አከራካሪ አልሆነም።
ጉዳዩን በጥልቀት ያልተረዱ ሰዎች ደግሞ ለምን በአከራካሪ ቦታዎች ሪፈረንደም አይካሄድም ብለው ይጠይቃሉ። ሪፈረንደም ቢካሄድ ውጤቱ ያለውን ሁኔታ ብዙም እንደማይቀይር ከላይ ከጠቀስኩት ስታቲስቲካዊ መረጃ ማየት ይቻላል። እንዲያም ሆኖ ሪፈረንደም ሊካሄድ የሚችለው ህገመንግስቱ ላይ በተደነገገው መሠረት ነው። አንድ ወረዳ ሪፈረንደም እንዲያካሂድ የወረዳው ምክር ቤት ሁለት ሶስተኛው ሪፈረንደም እንዲካሄድ መወሰን አለበት። አሁን ባለው ሁኔታ ደግሞ የወረዳውን ምክር ቤት ሙሉ በሙሉ የተቆጣጠረው ሕወሓት ነው። ብዙዎች ከሚያስቡት በተቃራኒው፤ ሕወሓት ከትግራይ ጥቅም ይልቅ ለስልጣኑ የበለጠ ቀናኢ ነው። አገሪቱን የባህር ወደብ አልባ ያደረገበትን ሁኔታ፣ በአስር ሺዎች መስዋእት ከሆኑ በኋላ የአልጀርስ ስምምነትን የፈረመበት ሁኔታ እና ሌሎችንም ተግባሮቹን ስንመለከት፣ ለስልጣኑ ሲል የትግራይንም ሆነ የኢትዮጵያን ህዝብ ጥቅም አሳልፎ ከመስጠት እንደማይመለስ እንረዳለን። በወልቃይት ጉዳይም ቢሆን ስልጣኑን ለማስጠበቅ ሲል ከትግራይ ህዝብ ጥቅም ውጪ በጉዳዩ ላይ ሊደራደር ይችላል፡፡
በዚህ ግዜ ትግሬው በሁለት በኩል ከባድ አደጋ ተደቅኖበታል። ባንድ በኩል በስልጣን ላይ ያለው መንግስት የሚያደርስበት ጭቆና፣ በሌላ በኩል በተቃዋሚው በኩል የተደበቁ ጥቂት ዘረኝነት ያለባቸው ሃይሎች የሚሰነዝሩበት ጥቃት። ስለዚህ ትግሉ በመንግስት የሚደርስበትን ጭቆና መቀልበስ ብቻ ሳይሆን፤ በጥቂት ዘረኞች የተቃጣበትን ጥቃት መቋቋም ጭምር ነው። የሌላው ብሄር ልሂቃንም ሆነ ህዝቡ ይህን ተረድተው ከትግሬው ጎን በመቆም ከአክራሪዎች የሚደርስበትን ጥቃት በጋራ ሊታገሉት ይገባል።
ለመላው ኢትዮጵያውያን መቅረብ ያለበት ጥያቄ፣ ትግሉ የትግራይን ህዝብ ለመጉዳት ነው? ወይስ የሁሉም ጥቅም የተከበረበት ዴሞክራሲያዊና ፍትሓዊ ስርዓት ለመመስረት ነው? አብዛኛው ቀና ኢትዮጵያዊ የሁሉም ጥቅም የሚከበርበት ዴሞክራሲያዊና ፍትሓዊ ስርዓት ለመመስረት እንጂ አንዱ ብሄር ላይ የተለየ ጉዳት እንዲደርስ ፍላጎት እንደሌለው አከራካሪ አይሆንም። የሁሉም ባለድርሻ ጥቅም የተጠበቀበት ስርዓት ለመመስረት፤ ሁሉም ባለድርሻ የሚሳተፍበት ሂደት ሊኖር ይገባል እንጂ አንዱ ተጠቅቶ ሰላማዊ ስርዓት ይፈጠራል ማለት ዘበት ነው። ስለሆነም የሚከተሉት ባለድርሻዎች የሚከተሉትን ተግባሮች ሊፈፅሙ ይገባል፡-
የትግራይ ህዝብ እስካሁን በጎንደር በደረሰበት በደልና በአንዳንድ አክራሪ ቡድኖች በሚካሄድበት ዘመቻ፣ ተጠቃሁ ብሎ በስሜታዊነት አላስፈላጊ እርምጃዎች ከመውሰድ መቆጠቡ የሚያስመሰግን ነው። ከዚህ ባሻገር ፅንፈኞቹ የሚያደርጉበትን ጥቃት ተደራጅቶና ከሌሎች ቅን ኢትዮጵያውያን ወንድሞቹ ጋር ተባብሮ ሊመክተው ይገባል። በተመሳሳይ መልኩ ልክ እንደ ኦሮሞና አማራ ወንድሞቹ በተደራጀና ሰላማዊ በሆነ መልኩ ፍትሓዊ ስርዓት እንዲፈጠር መንግስት ላይ ተፅእኖ ሊያደርግ ይገባዋል።
በሌሎች ክልሎች ያሉ ኢትዮጵያውያንም የጀመሩትን ሰላማዊ ትግል መቀጠል ይገባቸዋል። ሆኖም ትግላቸው ሰላማዊና የትኛውንም የህብረተሰብ ክፍል የማያጠቃ ሊሆን ይገባዋል።
ለዚህም የኦሮሞው ትግል ውጤታማነት አመላካች ነው። የኦሮሞው ትግል ማንንም ለይቶ ባለማጥቃቱና እጅን ወደ ላይ በመስቀል ሰላማዊ እምቢታን በመጠቀሙ የመላውን ኢትዮጵያዊ ድጋፍ ሊያገኝ ችሏል። በአማራው ክልል በተካሄደው ተቃውሞ፣ በአንዳንድ ጽንፈኛ ወገኖች የተሰነዘሩ  በትግሬው ላይ ያነጣጠሩ ጥቃቶች፣ ለሺዎች አመታት በጋራ የኖረውን የአማራና የትግራይ ህዝብ ታሪክ ለማጠልሸት የታለሙ በመሆናቸው የበለጠ ጉዳት ሳያደርሱ ሊታረሙ ይገባቸዋል።
በአገር ውስጥ የሚገኙ ተቃዋሚ የፖለቲካ ሃይሎች እርስ በርሳቸው መነቋቆሩን ትተው ህብረት መፍጠር ይኖርባቸዋል። ህዝቡንም ለመምራት ዝግጁ ሊሆኑ ይገባል። በቁጣ የገነፈለውን የተቃውሞ ማእበል መስመር ለማስያዝ የትግሉ አላማዎችንና መደራደሪያ ነጥቦችን ማዘጋጀት ይኖርባቸዋል። ተቃዋሚው ሃይል አንድ ወይም ሁለት ጠንካራ ቅንጅቶች ወይም ደግሞ ግንባሮች ሊፈጥር ይገባዋል። በውጭ የሚገኙ ተቃዋሚ የፖለቲካ ሃይሎች የኦሮሞ ዴሞክራሲያዊ ግንባር ጀምሮት እንደነበረው፣ አገር ውስጥ ገብተው በሰላማዊ ፖለቲካ ለመሳተፍ መዘጋጀት ይኖርባቸዋል። ኢትዮጵያን ማፈራረስ ዋና አጀንዳው የሆነው ሻዕቢያ ስር የታቀፉ ሃይሎች በፍጥነት ራሳቸውን ነፃ ማድረግ ይኖርባቸዋል።
በውጭ አገር የሚገኙ የመገናኛ ብዙሃን፣ ህዝብን ከህዝብ ከሚያጋጩ ተግባራት ተቆጥበው ህዝብን የሚያስተባብርና አገሪቱን ወደ ቀና መንገድ የሚወስዱ መልእከቶች ሊያስተላልፉ ይገባል። በኢትዮጵያ ፖለቲካዊ ምህዳር ውስጥ ምን አይነት ሚና መጫወት እንደሚገባቸው በጥልቀት ሊመረምሩ ይገባል። ገንቢ ሚና ይጫወቱ ዘንድ ራሳቸውን ከሻዕቢያ ጥገኝነት ነፃ ማድረግ ይጠበቅባቸዋል፡፡ ከኢህኣዴግ ለውጥ እንዲኖር የምንጠብቀውን ያክል ከተቃዋሚውም ለውጥ ያስፈልጋል። የኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን እንዲለወጥ የምንታገለውን ያህል በውጭ የሚገኙ መገናኛ ብዙሃንም እንዲለወጡ መታገል ይገባናል።
ከሁሉም በላይ ለሰላማዊ ለውጥ ስኬታማነት ኢህአዴግ መሪ ሚና ሊጫወት ይገባዋል። ኢህአዴግ ጭንቅላቷን አሸዋ ውስጥ እንደምትደብቀው ሰጎን፤ ነባራዊ ሁኔታውን ከመካድ ይልቅ፣ ከሌሎች የፖለቲካ ሃይሎች ጋር ለመደራደር ዝግጁ ሊሆን ይገባል። መጪው የቀበሌና የወረዳ ምርጫ ነፃ እንዲሆን ከማድረግ ጀምሮ አሸማቃቂውን የጸረ-ሽብርተኝነት ህግ ማሻሻል፣ በዚያ ህግ መሰረት የታሰሩትን ጋዜጠኞችና ፖለቲከኞች መፍታት ያስፈልጋል።
ከዚያም በተጨማሪ የምርጫ ቦርድ፣ የኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽንና ሌሎች ተቋማት በነፃ ቦርዶች እንዲተዳደሩ ማድረግ ይገባል። እነኚህ መፍትሄዎች ለኢህአዴግ ለመዋጥ የሚጎመዝዙ ነገር ግን አገሪቱን፣ ህዝቧንና ራሱን ኢህአዴግን ከጥፋት የሚያድኑ ብቸኛ መፍትሄዎች ናቸው። ያለበለዚያ እጣችን እንደ ሶሪያና ሊቢያ እንዳይሆን የሚከለክለው ነገር አይኖርም፡፡
ከአዘጋጁ፡- ጸሃፊውን በዚህ የኢ-ሜይል አድራሻው This email address is being protected from spambots. You need JavaScript enabled to view it. ማግኘት ይቻላል፡፡

Read 1937 times