Monday, 26 September 2016 00:00

‹‹ጥናትና ምርምር ማካሄድ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ግዴታ ነው››

Written by 
Rate this item
(1 Vote)

     የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተልዕኮ ማስተማርና ጥናትና ምርምር ማካሄድ ነው፡፡ ጥናትና ምርምር ካላካሄድን ከ2ኛ ደረጃ በምን እንሻላለን? ይላሉ የአድማስ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት ዶ/ር ሞላ ፀጋይ፡፡
አድማስ ዩኒቨርሲቲ የዛሬ ሳምንት ‹‹የትምህርት ጥራትና የዩኒቨርሲቲ ኢንዱስትሪ ትስስር›› በሚል ርዕስ በሳሮ ማርያ ሆቴል 10ኛውን ዓመታዊ ሀገር አቀፍ የጥናትና ምርምር ኮንፈረንስ አካሄዶ ነበር፡፡ በዚህ ኮንፈረንስ ላይ በተለያዩ ርዕሰ ጉዳዮች ላይ የተለያዩ ዩኒቨርሲቲዎች ምሁራን 8 ጥናታዊና የምርምር ጽሑፎች አቅርበው ውይይት ተደርጎባቸዋል፡፡ የዩኒቨርስቲው ፕሬዚዳንት ዶ/ር ሞላ ባደረጉት የመክፈቻ ንግግር፤ ዩኒቨርሲቲው በመቶ ሺዎች የሚቆጠር ገንዘብ እየመደበ፤ በየዓመቱ ጥናትና ምርምር እንደሚካሄድ ገልጸው፣ ከዚህ ቀደም ዘጠኝ ዓመታዊ ሀገር አቀፍ ኮንፈረንሶች፣ አንድ ዓለም አቀፍ የምርምር ኮንፈረንስ፣ ስድስት የተማሪዎች የምርምር ሲምፖዚየም ማካሄዳቸውን ጠቁመዋል፣ ጥናትና ምርምር የሚያካሂዱት በራዕይና ተልዕኮአቸው በግልጽ በመስፈሩ፣ በአገሪቷ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የፖሊስ ምርመር ማካሄድን ግዴታ በማድረጉ ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት የፈጠራ፣ የለውጥና የክህሎት ማበልጸጊያ ማዕከላት እንዲሆኑ በተቆጣጣሪ አካላት ከፍተኛ ትኩረት ስለ ተሰጠው እንደሆነ አመልክተዋል፡፡
የዘንድሮውን የጥናትና ምርምር ርዕስ፤ ‹‹የትምህርት ጥራትና የዩኒቨርሲቲ ኢንዱስትሪ ትስስር›› የሚል ርዕስ የያዘው ጉዳዩ የሕዝብና የመንግስት ከፍተኛ የትኩረት አቅጣጫ በመሆኑ ነው ብለዋል፡፡ ከኢንዱስትሪዎች ጋር ስላላቸው ግንኙነት ከጋዜጠኞች ለቀረበላቸው ጥያቄ ሲመልሱ ከኢንዱስትሪዎች ጋር ያለን ትስስር በአንፃራዊነት ጥሩ ነው፡፡ ተቋሙ ከዩኒቨርሲቲው ጋር ያለው ትስስር ሲጎለብት ጠንከር ብሎ  ይታያል፤ ላላ ሲል ደግሞ ድክመቶች ይስተዋላል፤ ክፍተቶች ግን የሉም ማለት አይቻልም ብለዋል፡፡
ዩኒቨርሲቲው በዋናነት የሚሰጣቸው ኮርሶች በቢዝነስ ላይ ያተኮሩ እንደሆነ ገልጸዋል፡፡ አካውንቲንግ ፋይናንስ፣ ማኔጅመንት፣ ማርኬቲንግ፣ ሆቴል ማኔጅመንት፣ አይቲ፣ ኮምፒዩተር ሳይንስ መሆናቸውን ጠቅሰው፤ ኢንዱስትሪዎች በዚህ ሙያ ይህን ያህል ምሩቃን ላኩልን እያሉ ይጠይቃሉ፡፡ የብዙዎችንም ጥያቄ እኔ ስለምፈርም፤ በአሁኑ ወቅት ሰልጥኖ ሥራ ያልተቀጠረ ተማሪ ይኖራል ብዬ አልወስድም ብለዋል፡፡
ብዙ ጊዜ የምርምር ግኝቶች የኅብረተሰቡን ችግሮች ሲፈቱ አይታዩም፡፡ ዕጣቸው መደርደሪያ ላይ ሆኖ አቧራ መልበስ ነው፡፡ በዚህ ረገድ የእናንተ ጥናትና ምርምር ምን ያህል ወደ ኅብረተሰቡ ወርዷል? በማለት ጋዜጠኞች ላቀረቡት ጥያቄ ዶ/ር ሞላ ሲመልሱ፤ ‹‹ብዙ አሉ፡፡ ለአብነት ያህል በአንድ ወቅት ጥቃቅንና አነስተኛ ኢንተርፕራይዞች ያሉባቸው ችግሮች ምንድናቸው? በማለት ጥናት አካሄድን፡፡ በውጤቱም የዕቅድና የአመለካከት ችግር እንዳለ አመለከተን፡፡ ስለዚህ በአዲስ አበባና ዙሪያዋ ያሉ የጥቃቅንና አነስተኛ ኢንተርፕራይዞችን በማስታወቂያ ጠርተን ሥልጠና ሰጥተናል›› በማለት ገልጸዋል፡፡

Read 3126 times