Monday, 26 September 2016 00:00

ተመድ በብሩንዲ ዳግም የዘር ማጥፋት ሊፈጸም እንደሚችል አስጠነቀቀ

Written by 
Rate this item
(1 Vote)

የብሩንዲ መንግስት በዜጎቹ ላይ ግድያና አሰቃቂ ድብደባን ጨምሮ የተለያዩ አስከፊ የሰብዓዊ መብት ጥሰቶችን እየፈጸመ እንደሚገኝ የጠቆመው የተባበሩት መንግስታት ድርጅት፤ሁኔታዎች በዚህ ከቀጠሉ በአገሪቱ ዳግም የዘር ማጥፋትና እልቂት ሊከሰት እንደሚችል አስጠነቀቀ፡፡
የተመድ የሰብዓዊ መብቶች ምክር ቤት መርማሪዎችን ሪፖርት ጠቅሶ አጃንስ ፍራንስ ፕሬስ እንደዘገበው፤ የአገሪቱ መንግስትና ተላላኪዎቹ በዜጎች ላይ የከፋ የሰብዓዊ መብቶች ጥሰት እያደረሰ የሚገኝ ሲሆን በሺህዎች የሚቆጠሩ ዜጎች የግርፋት፣ የጾታዊ ጥቃትና የእስራት ሰለባ መሆናቸው ተረጋግጧል፡፡ የብሩንዲ መንግስት በዜጎች ላይ በሚፈጽመው የሰብዓዊ መብቶች ጥሰት ላይ ስር ነቀል ለውጥ ካላደረገና አለማቀፉ ማህበረሰብ ለጉዳዩ ትኩረት ሰጥቶ ችግሩን ለመፍታት ካልሰራ አገሪቱ ወደማትወጣው የጥፋት አዘቅት መግባቷ አይቀሬ ነው ብለዋል፤የተመድ ባለሙያዎች፡፡
የአገሪቱ ፕሬዚዳንት ፔሪ ንኩሩንዚዛ በሚያዝያ ወር 2015 ለሶስተኛ ጊዜ በምርጫ እንደሚወዳደሩ ማስታወቃቸውን ተከትሎ በአገሪቱ ከፍተኛ ተቃውሞና ብጥብጥ መከሰቱን ያስታወሰው ዘገባው፤ የተመድ የሰብአዊ መብቶች ምክር ቤትም ባለፈው ወር በአገሪቱ የሚደርሱ የሰብዓዊ መብት ጥሰቶችን የሚያጣራ ቡድን ማሰማራቱን ጠቁሟል፡፡
ቡድኑ ከ277 የአገሪቱ ዜጎችና የሚመለከታቸው አካላት ጋር ባደረገው ቃለ መጠይቅና ማጣራት፣ ብጥብጡ ከተከሰተበት ጊዜ አንስቶ ከ1 ሺህ በላይ የሚገመቱ የአገሪቱ ዜጎች መገደላቸውንና ከ300 ሺህ በላይ የሚሆኑትም አገራቸውን ጥለው መሰደዳቸውን ማረጋገጡን አስታውቋል ብሏል ዘገባው፡፡ የብሩንዲ ፕሬዚዳንት ቃል አቀባይ ዊሊ ኒያሚትዌ በበኩላቸው፤ ተመድ ያወጣውን ሪፖርት ፖለቲካዊ አንድምታ ያለውና በተጨባጭ ማስረጃዎች ላይ ያልተመሰረተ በማለት እንዳጣጣሉት ዘገባው አክሎ ገልጧል፡፡
እ.ኤ.አ በ2006 በተጠናቀቀው የብሩንዲ የእርስ በእርስ ጦርነት ከ300 ሺህ በላይ የአገሪቱ ዜጎች ለሞት መዳረጋቸውንም ዘገባው አስታውሷል፡፡

Read 1111 times