Sunday, 09 October 2016 00:00

ከብሔራዊ ሀዘን አዙሪት እንዴት እንውጣ?! “Injustice to anyone is injustice to everyone

Written by  ክብሮም ዘቢብ
Rate this item
(4 votes)

    ባለፈው እሁድ መስከረም 22፣ በኦሮሞ ማህበረሰብ ዘንድ ትልቅ ቦታ በሚሰጠው የኢሬቻ በዓል ላይ በደረሰው አስከፊ አደጋ፣ በርካታ ኢትዮጵያውያን መሞታቸውን ተከትሎ ለ3 ቀናት ብሄራዊ ሀዘን ታውጇል፡፡ የፖለቲካ ጨዋታውን ትተን፣ የዜጎቻችን ሞት በእጅጉ ያሳዝናል፡፡ በዚህ ረገድ ፖለቲከኛና ህዝብ የተለያዩ ናቸው፡፡ በተለይ ጤነኛ ያልሆነ ፖለቲካ ለሚያራምድ ሰው መሞትና መግደል የህይወት መመርያው ነው፡፡
ለዚህም ነው በሁለቱም ፅንፍ ያሉት ፖለቲከኞች የየራሳቸውን ጨዋታ መጫወትን የመረጡት፤ ለዚህም ነው እርስ በርስ መወነጃጀልን የተያያዙት። “Injustice to anyone is injustice to everyone” እንደሚባለው፤የአንድ ሰው ሞትም ቢሆን ሊያንገበግበን ሲገባ፣ቁጥር የመጨመርና የመቀነስ ፖለቲካ የጤና አይደለም፡፡  ለሟቾች፣ ለቤተሰቦቻቸውም ሆነ ለሀገሬው ህዝብ አስፈላጊ የሚሆነው መኖር ነው፡፡ ልጅ የአባቱንና የእናቱን መኖር ይሻል፡፡ ህዝብ የዜጋውን መኖር ይፈልጋል፤ ጤናማ ማህበረሰብም የመኖር ውጤት ነው፡፡ የሰው ልጅ ረዥም ዕድሜ አልተቸረውም፡፡በሰለጠነውና ዘመኑን በዋጀው ፖለቲካዊ አስተሳሰብ፣ ባለመግባባት የሚከሰቱ ግጭቶችና ሞትን ማስቀረት ተችላል፡፡ እልህና ግትርነት፣ ሴራና ምቀኝነት ባለበት ደግሞ የአንዱ መሞት ሳያስተምር ቀርቶ የሁሉንም መሞት እንደሚያስከትል ሩቅ መሄድ ሳያስፈልግ በጎረቤቶቻችን የምናየው ሀቅ ነው፡፡
የመንግስት ሚዲያዎች የዜጎቻችን፣ የወንድም እህቶቻችን ሞት፣ የነውጥ ፈጣሪዎች ስራ እንደሆነና እርስ በርስ በመረጋገጥና በመፈታተግ እንዲሁም ገደል በመግባት የተከሰተ መሆኑን እየገለፁ ነው፡፡ በተቃራኒው፣ በተለይ በውጪ የሚኖሩ ፖለቲከኞች፣ የሞቱ ምክንያት የመንግስት የፀጥታ ሀይሎች በወሰዱት እርምጃ የተከሰተ መሆኑን እየተከራከሩ ነው፡፡ በሌላኛው ገፅ ያሉት ትልልቅ የዓለም ሚዲያዎች ደግሞ የሞቱ ምክንያት እርስ በርስ መረጋገጥ (Stampede) መሆኑንና የሟቾች ቁጥርም መንግስት የጠቀሰውን እየደገሙ ነው። በዚህ የተራራቀ የፖለቲካ ቀመር መሀከል ቀጣይ ችግር እንጂ ቀጣይ መፍትሔ ማንበብ አልተቻለም። ከሁኔታው መረዳት የሚቻለው፣ ሁሉም ፖለቲከኛ የራሱን ትርፍ ለማስላት መጣደፉንና ከጥድፍያውም ብዛት መፍትሔ እያየን አለመሆኑን ነው፡፡ ሁሌም ቢሆን ሊያሳስበን የሚገባው ህመሙ ብቻ ሳይሆን መድሃኒቱና ክትባቱም ጭምር ነው፡፡
የችግሩን ምክንያት ማወቅ ግማሽ መፍትሔ ነው
ወጣቶች የሚጫወቱበት የኳስ ሜዳ ቢያጡ አስፋልት ላይ እንደሚጫወቱ በየመንገዱ የምናየው ሀቅ ነው፡፡  አስፋልት ላይ መጫወት ትክክል አለመሆኑንና ለሞትና ለአደጋ የሚዳርግ መሆኑን እየታወቀ እንኳን መፍትሔ እስኪገኝ ድረስ መጫወታቸውን አያቆሙም፡፡ ፖለቲካም ቢሆን ራሱን የቻለ ጨዋታ ሲሆን የራሱ ሜዳና የራሱ ህግ ያስፈልገዋል፡፡ የሀገሪቱ መንግስት የጨዋታ ሜዳውን የማስተካከል፣ ለሁሉም የሚሆን  የመጫወቻ ህግ የማውጣትና የማስተግበር ግዴታ ሲኖርበት፣ የሀገሬው ተቃዋሚም በእጁ ሳይሆን በእግሩ የመጫወትና ለህጉ የመገዛት ግዴታ አለበት። መንግስት የሀገሪቱን  ፖለቲካ ተጫውተው፣ የሀገሪቱን ክብርና ጥቅም የሚያስከብሩ ተጫዋቾች መፍጠርና ያንን የሚያመጣ ሁኔታ ማመቻቸት ይገባዋል፡፡ ያ ካልሆነ ግን ጨዋታው  አስፋልት ላይ ይሆንና አደጋውም ለሀገር ይተርፋል፡፡
አሁን ያለው የሀገሪቱ ፖለቲካ የዚህ ማሳያ ነው፡፡ ኢህአዴግ የሚወክለው ህዝብ ይኖራል። ኢህአዴግ አይወክለኝም የሚለው ደግሞ በትከክለኛ ወኪሎቹ ይወከል ዘንድ መፈቀድ አለበት፡፡ ይህን የሚያመጣ የፖለቲካ ባህልና ንቃተ-ህሊና፣ ከሌላው ዓለም በመማርም ማግኘት ይቻላል፡፡ ይህ ባልሆነበት ሁኔታ፣ ሰዎች የፖለቲካ ፍላጎታቸውን የሚያወጡበትና የሚጫወቱበት መንገድ ባልተዘጋጀበት ሁኔታ የትኛውንም አጋጣሚ ተጠቅመው ሀሳባቸውን መግለፃቸው አይቀርም። የፈይሳ ሌሊሳ ተቃውሞም ሆነ የጳጳሱ ምክር እንዲሁም የኢሬቻ በዓል ተቃውሞ የዚሁ ማሳያ ናቸው፡፡ ፖለቲካ የሚጫወት ባለሙያ ሳይኖር ሲቀር፣ ሁሉም ፖለቲከኛ ለመሆን ይገደዳል፡፡ ያኔ ታድያ ከውዥንብርና ግራ መጋባት ባለፈ፣ ይህ ነው የሚባል ሁነኛ መፍትሔ አይኖርም፡፡ ሲጠቃለል፣ የመድብለ ፓርቲ ስርዓት፣ ነፃና ተአማኒ ሚድያ፣ግልፅነትና ተጠያቂነት፣ መተማመንና መከባበር፣ ሰላማዊ የስልጣን ሽግግርና ዲሞክራሲያዊ ምርጫ፣ ፍትሕና ርትዕ በሌለበት ሁሉ አሁን የምናየውና ከዛም በላይ ችግር ማስከተሉ አይቀርም፡፡
የአንዱ መሞት የሁሉም ሞት ነው
“ኑር ሌሎችም እንዲኖሩ አድርግ” የሚለው የኤችአይቪ ኤድስ መፈክር ቁምነገር የበዛበት ነው። ለመኖር ሌሎችም እንዲኖሩ መፍቀድ ያስፈልጋል። ይህ ማለት የሌሎች መኖር የእኛ መኖርን እንደሚያመጣ፣ የሌሎች መሞትም የኛን ሞት ያስከትላል፡፡ መግደል መሞትን ያመጣል፡፡ ደርግ መግደል የጀመረ ጊዜ መሞት መጀመሩን  ከኢህአዴግ በላይ የሚያውቅ የለም፡፡ ልጅ እናትዋን ምጥ አስተማረች ካልሆነ በቀር የደርግ ሞት የሌሎች ሞት ያስከተለው መሆኑን መንግስት ያውቃል፡፡ ልዩነትና ብዝሀነት በበዛበት ሀገር፣ “ልዩነታችን ውበታችን”  የሚለውና በጥንት ዘመን ሳይቀር በግሪካውያን ይታወቅ የነበረውን መፈክር መስቀል በቂ አይደለም። በተግባር ሲፈተሸ፣ በሀገራችን ያለው ልዩነት የብሄርና የሀይማኖት ብቻ የሚመስለው መንግስት፤ መሰረታዊ የአቋም ለውጥ እንደሚያስፈልገው ግልፅ ነው፡፡ እርግጥ ነው፣ መርሳት የማያስፈልገው ነገር፣ የኢህአዴግ መንግስት በቋንቋና በማንነት እንዲሁም በልማት ዙርያ የሰራቸው ስራዎች የሚታወስባቸው ሀውልቶች ናቸው፡፡ ሰዎች በአፍ መፍቻ ቋንቋቸው እንዲማሩ፣ በማንነታቸው እንዲኮሩና ባህላቸውን እንዲያሳድጉ በማድረጉ ሲመሰገን፣ ቀሪ የአንድነት የቤት ስራዎች ባለመስራቱም ይወቀሳል፡፡
መሬት ላይ ባሉ እውነታዎች ሲለካ፣ መንግስት በሀገሪቱ የፖለቲካ ብዝሀነት (political diversity) መኖሩን በአግባቡ የተረዳ አይመስልም፡፡ ህገ-መንግስቱን በማየት በጣም እንደገባው ያስታውቃል የሚል ተከራካሪ ሊኖር ይችላል፡፡ ይሁንና፣ ህገ-መንግስትንና (Constitution) ህገ-መንግስታዊነትን (Constitutionalism) ያጠና የ16 ዓመት የስነ-ዜጋ ተማሪ፣የነገሩን እውነታ ይረዳል፡፡ ሰላማዊ ሰልፍ ማድረግ መብት እንደሆነ የሚያስተምር ህገ-መንግስት የመኖሩን ያህል፣ በሰልፍ የተገኘን ሁሉ በዱላ የሚነርት ፖሊስና ይህ እንዲሆን የሚያዝ ከንቲባ መኖሩን ስናውቅ  የንድፈ-ሀሳባዊነትና የተግባር ልዩነቱ ግልፅ ይሆናል፡፡ “ነፃ፣ተአማኒና ፍትሓዊ” ምርጫ እናደርጋለን የሚል አብዮታዊና ዲሞክራስያዊ መፈክር የሰማ የ8ኛ ክፍል ተማሪ፤ የፖለቲካ ልዩነቶች በአግባቡ እየተስተናገዱ ነው ብሎ ሊያምን ይችላል፡፡ የማታ ማታ፣ የሰፈር ሰው ሁሉ በኢህአዴግ መማረሩንና ኢህአዴግን አለመምረጡን የሰማው ልጅ፤”መቶ በመቶ ወይም 96 በመቶ አሸነፍኩኝ “ ማለቱን ሲሰማ ግራ መጋባቱ አይቀርም። የተሻለ ሀሳብ ያላቸውና የተሻለ መፍትሔ የሚጠቁሙት ሁሉ አፋቸውን ይዘውና  መንግስትን ሊተኩ የሚችሉት ፓርቲዎች፤ ድራሻቸው ሲጠፋ ያየ ሰው፤ የምንመራው በህገ-መንግስት ሳይሆን በህገ-ኢህአዴግ ነው ቢል ምን ይፈረዳል? አይፈረድም!!
በመሆኑም፣ በኢህአዴግ መንደር የሚታዩት ችግሮች ሁሉ ከህገ-መንግስት ወደ ህገ-ኢህአዴግ መሸጋገሩን የሚጠቁሙ ናቸው፡፡ ይህ በህግ ያለመመራት አባዜ ያተረፈልን ነገር ቢኖር ሞትና ስጋት ነው፡፡ ፖለቲካዊ መቻቻል የሌለበትና ሁሉም ሁሉንም በሚጠራጠርበት ጊዜ ላይ ሆነን፣ የውጤቱን ምክንያት ስናስብ፣ የህገ-መንግስት አለመከበርን እናያለን፡፡ ህገ-መንግስት በማይሰራበትና የግለ-ሰብ ህግ (rule of man) በተንሰራፈበት ሁኔታ አሁን የምናየው ምስቅልቅል የሂደት ውጤት ይሆናል። የጉልበተኞችና የዝሆኖች ፍትጊያና መተሻሸት ባለበት ደግሞ ከምንም በላይ የሚጎዳው ህዝቡና ሳሩ ነው፡፡ ህዝብና ሳር የሌለበት ሀገር ደግሞ ሰሃራ በረሃ ከመሆን አይዘልም፣ መሪዎችም ቢሆኑ የሰው ደሴት ሆኖ ለመኖር አይችሉም፡፡ በዚህ ረገድ አንድ የማከብረው ጓደኛዬ፣ ራስጌው ስር ያኖራት የጆን ዶን  ግጥም፣የሰው ህሊና ያለውን ሁሉ የመንካትና የማስተማር ዓቅም ያላት ናት፡፡
No man is an island
At most he is a promontory
Every man’s death reduces me
Don’t ask for whom the bell tolls
It tolls for thee.
አዎ! ጆን ዶን ልክ ነው! የሞት ደውሉ ላንተም ለኔም ነው፡፡ የየትኛውም ሰው ሞት የሁሉም ሞት ነው፤ ማንም ቢሆን ደሴት አይደለምና!
“መምሃሪን አይትግበረኒ፣ መምሃሪንከ አይትክለአኒ”
ይህ የትግርኛ ተረት ብዙ ይናገራል፡፡ አስተዋይና ጠቢብ ሰው፣ ከሰው ችግር ይማራል፡፡ አስተዋይና ጠቢብ ፖለቲከኛ፣ ከደቡብ ሱዳን ይማራል። ደቡብ ሱዳን የነዳጅና የሀብት መናኸሪያ ብትሆንም፣ ሁለት መሪዎች በፈጠሩት ፖለቲካዊ ምስቅልቅሎሽ፣ ሰው ሰውን የሚበላባት የገሃነም ምድር ሆናለች። አስተዋይና አርቆ አሳቢ ፖለቲከኛ ከሶርያ  ይማራል፡፡ የሶሪያ ነገር እንኳን ለሰው ልጅ ምድር ውስጥ ለሚኖር ፍጥረት አይመችም። የሶሪያውያን ፖለቲከኞች መካረርና የዋህነት፣ የሶሪያን ህዝብ ሀገር አልባ ከማድረጉም ሌላ፣ ሀገሪትዋን የሰቀቀን ሀገር አድርጓታል፡፡ በሁለቱም ፅንፍ የቆሙት የሀገሬው ፖለቲከኞች፣ ባሁኑ ሰዓት ተቀራርበው ቢመክሩ እንኳን ነገርየው ከዐቅማቸው በላይ ነው፡፡ ባሁኑ ሰዓት፣ በሶሪያ ጉዳይ መደራደር የሚችሉት ከመጋረጃው ጀርባ የነበሩት ጉልበተኞች እንጂ ህዝብ አልባ መሪዎች አይደሉም፡፡ ከዚህ መማር የሚቻለው በሀገር ጉዳይ መካረርና ጫፍ ላይ መቆም፣ የገዛ ወገንን እሳት ላይ መጣድ ነው። በመቻቻልና በመከባበር፣ በስራና በብቃት ስልጣን ማሸጋገርና አርፎና ተንፈላስሶ መኖር ሲቻል፤”እኔ ከሞትኩኝ ሰርዶ አይብቀል” የሚሉት የሁለት ፅንፍ ፖለቲካ፣ የሶሪያውያን መንገድ ነው፡፡ ሞትን ከሶሪያ፣ ትንሳዔን ከማንዴላና ከጋንዲ መማር ይቻላል፡፡ ማንዴላ ከሩስያ እስከ ኩባ፣ ከአፍሪካ እስከ አሜሪካ ያሉት ሁሉ አልቅሰው የቀበሯቸው፣ ለይቅርባይነትና ለመቻቻል ፖለቲካ በሰጡት ቦታና ክብር ነው፡፡ አልበርት አንስታይን ሳይቀር፣ ማህተማ ጋንዲን፤ “በአንድ ወቅት ምድራችን እንዲህ አይነት ሰው አብቅላ ነበር ብለን፣ ለታሪክና ለትውልድ ለመንገር የምንኮራበት  ሰው “ብሎ ለማንቆለጳጰስ የበቃው፣ ለሰላምና ለፍቅር በነበረው አቋም ነው፡፡ እኛ ግን ያንድ እናት ልጆች ሆነን ሳለ፣ ያንድ ዓይነት ቀለምና ዘር ውጤት ሆነን ሳለ፣ የረዥም ታሪክና ስልጣኔ ባለቤት እንዲሁም የተወሳሰብን ሆነን ሳለ፣ እንዴት ታንዛንያን መሆን አቃተን፤ እንዴትስ ከጋናና ከቦትስዋና መማር አቃተን?! ያሳዝናል!!
እንኳን እኛ በአንድ አገር የምንገኝ ዜጎች ቀርቶ የአለም ህዝብ እርስ በርሱ በአንድም ሆነ በሌላ መንገድ የተወሳሰበና የተሳሰረ ነው /from the deeper reality and beyond time and space, we may all be part of one body /ያለው ማን ነበር?
አሁንም ማለት የሚቻለው አልረፈደም ነው። ከመቅረት መዘገየት (better late than never) እንዲሉ፣ መፍትሔው አሁንም በእጃችን ነው፡፡ የሞት፣ የውድመት፣ የስጋትና የስደት ታሪክ ማቆም ያለበት አሁን ነው፡፡ የሀገሪቱና የኢትዮጵያችን ጠላቶች፣ እኛው በለኮስነው ክብሪት ቤንዚን ሲጨምሩ እያየን ዝም ማለት የለብንም፣ ሙጭጭ ማለትም አያስፈልግም፡፡ በቃ! የታሰሩት ይፈቱ፣ የተሰደዱት ይመለሱ፣ የበደሉት በህግ ይወቀሱ፣ የተበደሉት ይካሱ፣ መፍትሔውና እውቀቱ እያላቸው ዝም ያሉት ይተንፍሱና፣ ሀገራችንን እናድን፡፡ አሸናፊና ተሸናፊ የሌለበትና ሁሉም አሸናፊ የሚሆንበት የመቻቻል ፖለቲካ በመገንባት የኢትዮጵያን ስም በድንቃ ድንቅ ማህደር ማፃፍ ይቻላል፡፡
ልዩነት ለዘላለም ይኑር!!

Read 2250 times