Sunday, 16 October 2016 00:00

የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁን ማስፈፀሚያ ደንብ ወጣ

Written by  መታሰቢያ ካሣዬ
Rate this item
(16 votes)

- የሰዓት እላፊ ተግባራዊ የሚሆንባቸው ቦታዎች አሁንም ይፋ አልተደረጉም
- በሁከቱና ብጥብጡ ተሳታፊ የሆኑ ሰዎችን  በአንድ ማዕከል በማሰባሰብ እንደጥፋታቸው    መጠን እርምጃ የመውሰድ ሥራ ይሰራል
- በስራ ማቆምና በቤት ውስጥ መቀመጥ አድማዎች ላይ ተሳታፊ መሆን በአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ያስቀጣል
- በኢንተርኔት ስራ ላይ የተሰማሩ ሰዎች፣ በአፍራሽ ተግባር ላይ ተሰማርተው የቆዩ በመሆኑ ገድቦ ማቆየቱ ተገቢ ነው

የሰዓት እላፊ ተግባራዊ የሚሆንባቸው ቦታዎች አሁንም ይፋ አልተደረጉም
በሁከቱና ብጥብጡ ተሳታፊ የሆኑ ሰዎችን በአንድ ማዕከል በማሰባሰብ እንደጥፋታቸው መጠን እርምጃ የመውሰድ ሥራ ይሰራል
በስራ ማቆምና በቤት ውስጥ መቀመጥ አድማዎች ላይ ተሳታፊ መሆን በአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ያስቀጣል
በኢንተርኔት ስራ ላይ የተሰማሩ ሰዎች፣ በአፍራሽ ተግባር ላይ ተሰማርተው የቆዩ በመሆኑ ገድቦ ማቆየቱ ተገቢ ነው
በኦሮሚያና በአማራ ክልሎች የተነሳውን ተቃውሞና አመፅ ተከትሎ መስከረም 28 ቀን 2009 ዓ.ም የወጣውን የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ተግባራዊ ለማድረግ የሚያስችል የማስፈፀሚያ ደንብ  የሚኒስትሮች ምክር ቤት በትላንትናው ዕለት ማውጣቱ ተገለፀ፡፡
ጠቅላይ ዐቃቤ ህግ አቶ ጌታቸው አምባዬ ትናንት ለጋዜጠኞች በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ እንደተናገሩት፤ መንግስት የህዝብን ሰላምና ፀጥታ ለማስከበር የሚያስችል የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ አውጥቶ ለህዝብ ይፋ አድርጓል፡፡ ይህንኑ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ለማስፈፀም ተግባራዊነቱነ ለመከታተል የሚያስችል ዝርዝር ደንብ የሚኒስትሮች ምክር ቤት ማውጣቱንና በሥራ ላይ እንዲውል ማድረጉን ገልፀዋል፡፡ ደንቡ ከያዛቸው ዝርዝር ጉዳዮች መካከል አዋጁ የያዘቸውንና ተግባራዊ የሚደረጉትን ዝርዝር ሃሳቦች ለህዝቡ ይፋ ማድረግ፣ አስቸኳያ ሁኔታ በተጋረጠባቸው አካባቢዎች ልዩ ገደቦችን በመጣል ለህዝቡ ማሳወቅ፣ የተከለከሉ ጉዳዮችን ህዝቡ በዝርዝር እንዲያውቃቸው ማድረግና፣ ተላልፎ መገኘት የሚያስከትላቸውን ቅጣቶች ለህዝቡ ማሳወቅ ይገኙበታል፡፡ ማንኛውም ህብረተሰብ መረጃ የመስጠትና የመተባበር ግዴታ እንዳለበት በአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ውስጥ የተደነገገ ሲሆን መረጃ በመስጠቱ ምክንያት ለጉዳት የሚጋለጥ አካል ከለላ የመስጠት ሥራ ተግባራዊ እንደሚደረግ አቶ ጌታቸው በመግለጫቸው ጠቁመዋል፡፡
የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ በሁከትና በብጥብጡ ውስጥ ተሳትፎ አላቸው የተባሉ ሰዎችን ለመቅጣት የሚያስችል ህጎችን ያቀፈ መሆኑን የተናገሩት ጠቅላይ ዐቃቤ ህጉ፤ ዜጎች ባጠፉት ጥፋት ልክ ቅጣታቸውን የሚያገኙበት አሠራር ተግባራዊ እንደሚያደርግ ተናግረዋል፡፡
የጥፋታቸው ክብደትና መጠን አነስተኛ የሆኑና በሁከትና ብጥብጡ አስተዋፅኦና ድጋፍ የነበራቸው ወገኖችን በአንድ ማዕከል ውስጥ በማሰባሰብ እንደ ጥፋታቸው ደረጃ ተሃድሶና ትምህርት በመስጠት፣ ወደ ህብረተሰቡ እንዲቀላቀሉ የማድረጉ ሥራ ተግባራዊ እንደሚደረግና የጥፋታቸው መጠን ከፍተኛ የሆኑትን ደግሞ በህጉ መሰረት ወደ ፍርድ ቤት ቀርበው በፍርድ ሂደት የሚዳኙበት አሠራር ተግባራዊ ይደረጋል ብለዋል፡፡ ይህንን ሁኔታ ፀረ ህዝብ ኃይሎች በራሳቸው መንገድ ተርጉመው፤ ለራሳቸው የፖለቲካ ፍጆታ ማዋላቸው አይቀሬ ነው ያሉት አቶ ጌታቸው፤ በቀንደኞቹ ላይ የምንወስደው እርምጃ ሌሎችን የሚያስተምርና ለጥፋታቸው ተመጣጣኝ የሆነ ነው ብለዋል፡፡ የጥፋት ኃይሎቹ እያካሄዱት ያለውን የሽብር ተግባር በመደበኛ አዋጅና ህጎች መቆጣጠር ባለመቻሉ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁን ለማውጣት ተገደናል ያሉት ጠቅላይ ዐቃቤ ህጉ፤ የፀጥታና የሰላሙ ሁኔታ እየታየ ከአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ የምንወጣበት ሁኔታ ይኖራል ብለዋል። ጥፋት ሊደርስባቸው ይችላሉ ተብሎ የሚታሰቡ ቦታዎችን በመለየት፣ ጥፋት ሊያደርሱ ይችላሉ የተባሉ አካሎችን በአንድ ቦታ በማስቀመጥ ጥፋት እንዳያደርሱ መከላከልና ጥፋቱ ያደርስባቸዋል በተባሉ አካባቢዎች ላይ የሚኖሩ ሰዎችን ከጥፋት ለመታደግ ጥበቃ አድርጎ እዛው ማቆየት አሊያም ወደ ሌላ ቦታ እንዲዛወሩ የማድረግ ሥራም ተግባራዊ ይሆናል ብለዋል፡፡
በሁከትና ብጥብጥ ተግባር ተሳታፊ መሆን ተጠያቂነትን እንደሚያስከትል ሁሉ በሥራ ማቆምና የአገልግሎት መስጫ ተቋማትን በመዝጋት ተግባር ላይ ተሳታፊ መሆን በአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ መስራት ለቅጣት እንደሚዳርግም አቶ ጌታቸው ተናግረዋል። ሰሞኑን የኢንተርኔት አገልግሎት ከመቋረጡ ጋር በተያያዘ፣ ይህንኑ አገልግሎት ለህብረተሰቡ በመስጠት የሚተዳደሩ አካላት ጉዳት እንደደረሰባቸውና ይህ ሁኔታ እስከመቼ እንደሚቀጥል ለቀረበላቸው ጥያቄም አቶ ጌታቸው ሲመልሱ፤ ‹‹የኢንተርኔት አገልግሎት መስጫ ተቋማት ገንቢ በሆነ ሥራ ውስጥ ተሰማርተው ከሚሰሩበት ይልቅ አፍራሽ እንቅስቃሴና በህዝቦች መካከል ሁከትና ብጥብጥ መጠራጠርና ጥላቻ እንዲዘራ በማድረግ የነበራቸው ሚና ቀላል ግምት የማይሰጠው ነው፡፡ በዚህ የተነሳም በአገራችን ቀላል የማይባል ውድመት ደርሷል፤ ህገ መንግስታዊ ስርዓቱ አደጋ ላይ እንዲወድቅ ሆኗል፡፡ ስለዚህም ለእንደዚህ አይነት አገልግሎት የሚውሉና የማይውሉትን ለይቶ አስፈላጊውን እርምጃ መውሰድ እስከሚቻል ድረስ አገልግሎቱን ገድቦ ማቆየት አማራጭ የሌለውና የአገርንና የዜጎችን ህልውና የሚታደግ ጉዳይ ነው ብለዋል፡፡

Read 7661 times