Saturday, 10 March 2012 11:01

“ራእየ ዮሐንስ…” ለበይነ

Written by  ገዛኸኝ ፀ.
Rate this item
(3 votes)

ዲሲፕሊናዊ ንባብ የሚየተጋ መጽሐፍ

ዳንኤል ክብረት የተፈተነበት፣ አንባቢ የሚፈተንበት ጥንቁቅ ሥራ…

በተለያዩ ሃይማኖታዊ ፍልስፍናዎችና የሥነ እውቀት ንድፈ ሃሳቦች የሚዳኝ መጽሐፍ…

ፈር መያዣ:- የዚህ ጽሑፍ ዓላማ፣ “ራእየ ዮሐንስ - የዓለም መጨረሻ” በሚል ርዕስ ዲያቆን ዳንኤል ክብረት በቅርቡ ለንባብ ባበቃው መጽሐፍ ላይ ወፍ በረራዊ የሆነ ሂሣዊ ምልከታ ማቅረብ ነው፡፡ “ራዕይ ዮሐንስ - የዓለም መጨረሻ” መጽሐፍ መሠረቱ መጽሐፍ ቅዱስ ሲሆን፣ በተለይ ለብዙ ትንቢታዊ ገለፃዎችና ፍካሬያዊ ምልከታዎች የተጋለጠው “የዮሐንስ ራእይ” ዋነኛ ማጠንጠኛ ነው፡፡ 400 ጥቅሶች፣ 22 ምዕራፎች ያሉት “የዮሐንስ ራእይ”፣ ከሁሉም የሀዲስ ኪዳን መፃሕፍት የበለጠ፣ በርካታ የብሉይ ኪዳን መፃሕፍት ማጣቀሱን፣ የዘርፉ ሊቃውንት ይመሰክራሉ፡፡ ለምሣሌ ከትንቢተ ዳንኤል፣ ከትንቢተ ሕዝቅኤል ብዙ ማጣቀሻዎች መወሰዳቸውን መመርመር ይቻላል፡፡

በርካታ ማጣቀሻ፣ ማናበቢያ መፃሕፍት የተጠቀመ፣ በርካታ ትንቢታዊና ምሣሌያዊ ትዕምርቶችን የተጠቀመ፣ በርካታ ሰብአዊና መለኮታዊ ምስጢሮችን የተጠቀመ መጽሐፍን (የዮሐንስ ራእይን)፣ አንብቦ መረዳት በራሱ ከባድ ነው፤ ነገረ ሀሳቦችን እያናበቡ ለማስተንተን መሞከር ደግሞ በርግጥም፣ ከባድ ብቻ ሳይሆን ፈታኝ ሥራም ይመስለኛል፡፡ በዘርፉ ላይ ተመሳሳይ ጥናት ያደረጉ የሌሎች ሀገር የሥነ መለኮት ሊቃውንትም፣ ሆኑ በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ ጥናት ያደረጉ የተለያየ የሥነ እውቀት ዘርፍ ምሁራን፣ ይህንኑ ሀሳብ በተለያየ መንገድ አስተጋብተዋል፡፡

እንደ የዮሐንስ ራዕይ አይነት መጽሐፍ፣ ከተጠቀመባቸው በርካታ የማጣቀሻ መፃሕፍት ጋር እያናበቡ ለማስተንተን መሞከር ከባድ እንዲሆን የሚያደርገው፣ በ2 ዋነኛ ምክንያቶች ይመስለኛል፡፡ ይኸውም፣ በመጀመሪያ፣ እያናበቡ ማስተንተን ወይም ትርጓሜ (ፍካሬ) መሻት (በተለይ በብዙ የመረጃ ምንጮች ላይ ተመስርቶ የሚካሄድ ከሆነ) በራሱ ውስብስብ መሆኑ ነው፡፡ ሁለተኛው ደግሞ፣ ተመራማሪው ርዕሰ ጉዳዮችን የሚመለከትበት የእይታ መነጽር፣ አመክንዮዋዊ (logical) እና መለኮታዊ ከመሆኑና አለመሆኑ የሚመነጭ ነው፡፡

በዩኒቨርሲቲ ውስጥ ለአካዳሚክ ተግባር በሚውሉ የዘርፉ ምርምሮች ሙሉ በሙሉ ሊባል በሚችል ደረጃ አመክንዮዋዊውን መንገድ እንዲከተሉ ይገደዳሉ፡፡ አመክንዮዋዊ ሲባል፣ የርዕሰ ጉዳዮቹ መመዘኛ ሳይንስ ሆነ ማለት ነው፡፡ ሌላኛው መንገድ መንፈሳዊ ወይም መለኮታዊ ምልከታ ነው፡፡ መለኮታዊው፣ የርዕሰ ጉዳዮቹ የመጨረሻ መዳኛ “እምነት” (ማመን) ብቻ ነው ወይም “የፈጣሪ (የእግዚአብሔር) ሥራ ነው” ብሎ በየዋህነት “መቀበል” ማለት ነው፡፡ እዚህ ላይ ግን፣  በመፈንሳዊ (በመለኮታዊ) መነጽር በሚደረጉ ምርምሮች በአንፃራዊነት አመክንዮዋዊ (logical) አካሂያዶች መከተል የተለመደ፣ ብቻ ሳይሆን ግድ የሚልም ነው ማለት ይቻላል፡፡ በሌላ አነጋገር፣ ይህን ውስብስብ የትርጓሜ ሥራ በመሥራት፣ (ምርምር ለማድረግ) የምንከተለው ንድፈ ሀሳባዊ መሠረት (Theoretical Framework) ሊኖር ይገባል ማለት ነው፤ ይህ ንድፈ ሃሳባዊ አቅጣጫ ደግሞ፣ እንደተመራማሪው አቅም፣ እራሱ ያረቀቀው ወይም ከሌላ የተዋሰው ይሆናል፡፡

“ራእየ ዮሐንስ - የዓለም መጨረሻ” መጽሐፍ የተገኘውም፣ ቀደም ሲል በስሱ የተመለከቱትን ነቢባዊና ገቢራዊ ውስብስብነት ሁሉ አልፎ ነው፡፡ እኔ እስከማውቀው በሀገራችን በአማርኛ ቋንቋ የተዘጋጀ የመጀመሪያው የዮሐንስ ራእይ ማስተንተኛ መጽሐፍ ይመስለኛል፡፡ የመጽሐፉ አዘጋጅ ዳንኤል ክብረትም፣ ቀደም ሲል ወደ 17 ያህል መፃሕፍትን ሲጽፍ፣ ያካበተውን ልምድና እውቀት መነሻ ሳያደርግ ዘሎ የገባበት መጽሐፍ እንዳልሆነ መገመት አይከብድም፡፡ የምርምሩን ረቂቅነት፣ ውስብስብነትና ፈታኝነትም፣ ከአዘጋጁ የሕይወት ልምድና የሥነ - መለኮት እውቀት ትይዩ ሊዳኝ የሚችል ይመስለኛል፡፡

እኔም፣ የሥነመለኮት እውቀት የሚጠይቁትን ርዕሰ ጉዳዮች ለመስኩ ሊቃውንት ትቼ፣ መጽሐፉ ለፈርጀ ብዙ የሥነ እውቀት (“በይነ ዲሲፕሊናዊ”) ንባብ ያለውን ጠቀሜታ በጥቂቱ ለማመልከት እሞክራለሁ፡፡ “በይነ - ዲሲፕሊናዊ” የሚለው የጽንሰ ሃሳብ ስያሜ “Interdisciplinary” የሚለውን የእንግሊዝኛ ቃል የሚተካ ሲሆን፣ ከቴዎድሮስ ገብሬ “በይነ - ዲሲፕናዊ የሥነ ጽሑፍ ንባብ” (2001 ዓ.ም) መጽሐፍ የተወሰደ ነው፡፡ በዚህ መጠነኛ ጽሑፍ ሊጠቆም የተፈለገውን ዓላማ ለማሳካት፣ የቴዎድሮስን አይነት መጻሕፍት ማንበብ የምርጫ ጉዳይ ሳይሆን፣ ግድ የሚለንም ይመስለኛል፡፡

“የራእየ ዮሐንስ…” መጽሐፍ አወቃቀር

መጽሐፉ፣ በአምስት አብይ ክፍሎች ተከፍሏል፡፡ በእያንዳንዱ ክፍሎች የተካተቱት ምዕራፎች ተመሳሳይ መጠን የላቸውም፤ 22ቱም ምዕራፎች፣ ከመጽሐፈ ቅዱሱ “የዮሐንስ ራእይ” የተወሰዱ ሲሆኑ፣ በእያንዳንዱ ምዕራፎች የተለያዩ ርዕሰ ጉዳዮች ተወስተዋል፡፡ መጽሐፉ፣ በግርጌ ማስታወሻ 356 መረጃዎች ተመላክተዋል፡፡ እነዚህ መረጃዎች እንደምንጭ ያገለገሉ ከ75 በላይ መፃሕፍት በዋቢነት ተዘርዝርዋል፡፡ መጽሐፉ፣ የቅዱሳት ስዕላትንም ለማናበቢያነት ተገልግሏል፡፡ 221 ገጽ ያለው ይህ መጽሐፍ፣ በአምስት ክፍሎች ስለመከፈሉ እንጂ የተከፈለበትን ተጠያቂያዊ ምክንያት አልጠቆመም፡፡

የትርጓሜ ንድፈ ሃሳባዊ ዳራዎች (Theoretical Background)

ከመጽሐፉ ጠንካራ ጐኖች አንዱ፣ የትርጓሜ ንድፈ ሃሳባዊ ዳራዎችን (“ልዩ ልዩ የትርጓሜ መንገዶች”ን) ያነሳበት ክፍል ነው፡፡ የመስኩ ሊቃውንት የተለያዩ “የትርጓሜ መንገዶች” መጠቀማቸውን ጠቁሞ፣ ሰባት ያህል የንድፈ ሃሳብ መሠረቶችን ዘርዝሯል፡፡ በመጨረሻ ላይ፣ “እንደ ቤተክርስቲያን ሊቃውንት ከሆነ የዮሐንስ ራእይን በተሻለ መልኩ ለመተርጐም ሁሉንም መንገዶች እንደ አስፈላጊነታቸው መጠቀሙ የተሻለ ነው፡፡ አንዱ መንገድ ብቻውን ፍጹማዊ ነው ለማለት አይቻልም” በማለት መጽሐፍ፣ ሁሉንም ንድፈ ሃሳባዊ መሠረቶች እንዳስፈላጊነቱ እያሰባጠረ መጠቀሙ ተገልጿል፡፡

መጽሐፉ፣ ንድፈ ሃሳባዊ ፈር መያዣዎችን ለማንሳት መሞከሩ ትልቅ ነገር ነው፤ ነገር ግን፣ ንድፈ ሃሳቦችን ከመበየን ባለፈ፣ ደካማና ጠንካራ ጐናቸውን በሚያሳይ መልኩ ተጨምቀው ቢቀርቡ ጥሩ ነበር፡፡ “እንደ አስፈላጊነታቸው ሁሉንም መጠቀሙ” ያለውን አግባብነትና ተመራጭነት ለመረዳትም ይቻል ነበር፡፡

ነገር ግን፣ ከሰባቱ የንድፈ ሃሳብ መሠረቶች ሦስቱ ማለትም፣ “ነገ ተኮር” (Futurist theory)፣ “የመንፈሣውያን መንገድ” (The spiritualist way) እንዲሁም፣ “ጥንታዊ ዲስፔንሲሽናሊስትስ” (Classical Dispensationalist) ከአራት መስመር በላይ አልተብራሩም፡፡

ንድፈ ሃሳባዊ መሠረቶቹ በተወሰነ መልኩ ዘርዘር ብለው ቢተዋወቁ፣ አንባቢያንም ሆኑ ሌሎች ሊቃውንት መጽሐፉን የሚያዩበትን አማራጭ መነጽሮችን ማብዛት ማለት ነበር፡፡ በተለያየ መንገድ እያነበቡ የሥነ መለኮት እውቀትንም ሆነ በዚያ ትይዩ ያሉ ሌሎች የሥነ ምርምር ዘርፎችን እንዲያጐለብቱ የሚያነቃቃ ይመስለኛል፤ አዘጋጁ፤ “ለመነሻ የሚሆኑ ጠቁሚያለው፤ ዝርዝር ነገሮችን የፈለገ አንባቢ ወይም ተመራማሪ ተጨማሪ የተጠቀሱትን ዋቢዎች በአጽንኦት ሊፈትሽ ይችላል” የሚል ምላሽ ሊያቀርብ ይችላል፤ ምላሹን ታዲያ፣ ምክንያታዊ አይደለም ማለት ይከብዳል፡፡

የመረጃዎች ጥንቅርና ዋጋ አሰጣጥ

መጽሐፉ፣ ቀደም ሲል እንደተጠቀሰ በርካታ የመረጃ ምንጮች ተጠቅሟል፡፡ የመጽሐፉ አዘጋጅ ለመረጃዎች ስሱ መሆኑ፣ በተለይ ለሀገራዊ መረጃ ዋጋ መስጠቱ ለማረጋገጥ በርካታ ማስረጃዎች መጥቀስ ይቻላል፡፡ ከመጽሐፈ “መቅድም” ላይ ዲያቆን ዳንኤል፣ “ይህንን መጽሐፍ ሳጠናቅቅ አንድ የሚቆጨኝ ነገር አለ፡፡ እቴጌ መንትዋብ አስጽፈው ለጐንደር ቁስቋም የሰጡት፣ አፄ ቴዎድሮስ ወደ መቅደላ የወሰዱት፣ በኋላም እንግሊዞች ሰርቀው በብሪቲሽ ሙዚየም ያስቀመጡትን የራእየ ዮሐንስ መጽሐፍ ለማግኘት ባለመቻሌ፡፡ ይህንን መጽሐፍ ለማግኘት ያላደረግኩት ጥረት አልነበረም” በማለት ቁጭቱን ብቻ ሳይሆን፣ ተስፋ ሳይቆርጥ ወደፊትም እንደሚያስፈልገው ጭምር ይናገራል፡፡

የመረጃ ስሱነቱንና ዋጋ አሰጣጡን የበለጠ የምንረዳው ገጽ 18 ላይ ፣ “…በአሁኑ ጊዜ ይህ መጽሐፍ በብሪቲሽ ቤተመጻሕፍት በMs or. 533 ተመዝግቦ ይገኛል፡፡” የሚለውን ስናነብ ነው፡፡ የመዝገብ ቁጥሩን መዝግቦ መምጣቱ ለመረጃው ታማኝነት ብቻ የተከፈለ ዋጋ አድርጐ ማሰብ፣ ልፋቱን ዋጋ ማሳጣት ነው፤ “የቻልክ ኢትዮጵያዊ በዚህ መዝገብ ቁጥር የተገለፀ ሀብትህ እንግሊዝ ሃገር አለና ለማስመለስ የቻልከውን ሁሉ አድርግ” ማለቱን ለማጠየቅ ደግሞ፣ የክርስትና ሃይማኖት ተከታይ መሆን ግድ ሳይል ኢትዮጵያዊነት ብቻ በቂ ይመስለኛል፡፡

የመጽሐፉ አስፈላጊነት

የመጽሐፉ አስፈላጊነት አንድ የሚለው፣ ገና ከመነሻው ከመቅድሙ ላይ፣ የሥነ ፍጥረት እውቀት ምልኁ የሚሆነው በአንድ ሰው ሳይሆን በሰው ልጆች የማያቋርጥ ጥረት መሆኑን በመጠቆም ነው፡፡ ሌሎች ሰዎች መሰል በይነ ዲስፕሊናዊ መጽሐፈ አሻሽለው እንዲያዘጋጁ ትጋት ለመፍጠር፣ “እንዲህ ያለ መጻሕፍት በአንድ ጊዜ ፍፁማን አይሆኑም፡፡ አዳዲስ መረጃዎች እና ማብራሪያዎች ሲገኙ ይበልጥ እየተብራራ ይሄዳል፡፡ ሌሎች ከእኔ የተሻሉ ሊቃውንት የበለጠ ሥራ ሠርተው እንደማይ አምናለሁ” ማለቱን ልብ ይሏል፡፡

“ራእየ ዮሐንስ - የዓለም መጨረሻ” መጽሐፍ ከገጽ 3-6፣ “የመጽሐፉ ጠቀሜታ” ብሎ ወደ 6 ነጥቦችን ይዘረዝራል፡፡ ሁሉም፣ ጠቀሜታዎች በእምነት ስለሚገኙ ትሩፋቶች ወይም ሀይማኖታዊ ተልዕኮዎች ላይ ብቻ ነው የሚያነጣጥሩት፡፡ ለምሣሌ “የምስጋና መጽሐፍ” መሆኑ፣ “የመንግስተ ሰማያት መገለጫ መጽሐፍ” መሆኑ ወዘተ ናቸው፡፡ መጽሐፉ፣ ሥርአተ ቤተክርስቲያንና የሥነ መለኮት እውቀትን ማዕከል አድርጐ፣ የተዘጋጀ ሃይማኖታዊ መጽሐፍ መሆኑ ግልጽ ነው፡፡ ይህ ማለት ግን፣ ለሥነመለኮት ትምህርት፣ ለፍካሬ ንባብ፣ በተለይ መጽሐፍ ቅዱስን እንዳሻ በመተርጐም (በመፈክር) ከሚፈጠር ድፍረት ታቅቦ፣ በእውቀት ለመመራት መጽሐፉ ያለውን ተግባራዊ ጠቀሜታ ሊጠቆም ይገባ ነበር፡፡

“እንደ የዮሐንስ ራእይ ያሉት መፃሕፍት፣ ሌሎች የብሉይና የሃዲስ መፃሕፍት እያጠቀሱ ሲፃፉ፣ አንባቢያቸውም እንደተጠቀሙት የመረጃ ዝንቅነትና ጥልቅነት ይወሰናል፡፡ ሃይማኖታዊ ዋጋቸውን ሣያጡ ለመቆየትም፣ በሥነመለኮት ትምህርትና እውቀት የብሉይና የሀዲስ መፃሕፍት ሳይጣረሱ፣ በወጉ ተናበው የሚፈለገውን ሃይማኖታዊ ርዕዮተ ዓለም ማቀንቀን አለባቸው፡፡

“ራእየ ዮሐንስ - የዓለም መጨረሻ” መጽሐፍም፣ በተግባር በርካታ መረጃዎች ከበርካታ የሙያና የሥነ እውቀት ዘርፎች እያጣቀሰ፣ መረጃዎች ሳይጣረሱ እንዲያቀርብ ብዙ ዋጋ ተከፍሎበታል፡፡ የመጽሐፍ አዘጋጅ በሀገር ውስጥም ሆነ በበርካታ የውጭ ሀገራት መንከራተቱ፣ ተጨባጭና ታማኝ መረጃዎች ለማግኘት ከተደረገ ጠንካራ ውሳኔና ጽናት የመነጨ ይመስለኛል፡፡

የበርካታ የሙያ መስክ የምርምር ውጤቶች፣ ለመጽሐፉ ቀጥተኛ ግብአት ሆነዋል፡፡ በአርኪዮሎጂ፣ በፎክሎር፣ በሥነጽሑፍ፣ በሥነ ሥዕል፣ በታሪክ፣ በሥነመለኮት፣ በፍልስፍና ወዘተ የሙያ መስኮች የተገኙና የተረጋገጡ መረጃዎች ጥቅም ላይ ውለዋል፡፡ በሌላ አነጋገር፣ መጽሐፉ ለነዚህ ሁሉ ፈርጀ ብዙ የሥነ እውቀት መስኮች ተጋልጧል፡፡ መጽሐፉን የሚያነቡ ሰዎችም፣ በቀጥታም ይሁን በተዘዋዋሪ ከተለያዩት ዘርፎች እውቀት ማግኘታቸው አይቀርም፤ መጽሐፉ የተለፋበትን ያህል አንባቢያን ይረዱት ዘንድ፣ በየየሥነ እውቀት ዘርፎቹ ቢያንስ የመነሻ እውቀት ሊይዙ ይገባል፡፡

ለዚህ ነው፣ ይህ መጽሐፍ በበይነ-ዲሲፕሊናዊ ንባብ የሚጠይቅ መጽሐፍ ነው የምለው፤ በርግጥ በይነ ዲሲፕናዊ ምልከታንም፣ አንብቦ የመረዳት አቅምንም ያዳብራል፤ ለምሣሌ ሰባት ቁጥር በራእየ ዮሐንስ ውስጥ ያለው ተምሣሌታዊ ትርጓሜ ብዙ ነው፡፡ አንባቢያን በተለያየ መነጽር (የንድፈ ሃሳብ መሠረቶች) ሲያዩት፣ የተለያየ ትርጓሜ ይሰጡታል፡፡ ሌሎች ቁጥሮችም ለምሣሌ እንደ 144ሺህ አይነቶች ትእምርቶች በተለያዩ ሊቃውንት የተለያዩ ፍካሬ የመፍጠራቸው ዝንቅነት ሲታዩ፣ የመጽሐፉን  በይነ-ዲሲፕሊናዊነት ሊጠቁመን ይችላል፡፡ “ልዩነቶች” ከሃይማኖት አንጻር ችግር ፈጣሪዎች የሚሆኑትም፣ ትእምርቶች፣ በእውቀት ላይ ባልተመሠረተ ፍርደ ገምድልነት ሊተረጐሙ ስለሚሞከር ይመስለኛል፡፡

በሌላ በኩል፣ የትርጓሜ “ልዩነቶች” ባይኖሩ፣ በዓለም የሥ እውቀት ቅብብሎሽ ላይ ትልቅ ደንቀራ ይፈጠር ነበር፤ ዛሬ ያለችው ዓለም የተፈጠረችው በእውቀት ላይ በተመሠረቱ “የትርጓሜ ልዩነቶች” መሆኑ ግልጽ ነው፡፡ የዓለማችን ታዋቂ የፎክሎርና የስነሰብ ባለሙያ፣ አሜሪካዊው ፕሮፌሰር አለን ዳንደስ፣ “Interpreting Folklore” በሚለው መጽሐፍ 3 ቁጥር በአሜሪካ ባህል ውስጥ ያላትን ተምሣሌታዊ ትርጓሜ ያስተነተነበትን መንገድ ያነበበ፣ የዮሐንስ ራዕይ 7 ቁጥር ሃይማኖታዊ አውድ ውስጥ እንዳለ እየተነተኑ ለማስተርጐም ብዙ ክህሎት ያገኛል፡፡ በተመሳሳይ ሁኔታ፣ 7 ቁጥር በራእየ ዮሐንስ መጽሐፍ እንዴት እንደተተረጐመ ያነበበ፣ በአሜሪካ ባህል ውስጥ 3 ቁጥርን ለማተርጐም ድፍረት ብቻ ሳይሆን እውቀትም ያገኛል፡፡ የዳንኤል የራእየ ዮሐንስ መጽሐፍ፣ ዝንቅነትና በይነዲሲፕሊናዊነት ከዚህም በላይ ያመራምራል፤ ያስፈልጋልም - “እውቀትን ለምትሹ ሁሉ!”

 

 

Read 4223 times Last modified on Saturday, 10 March 2012 11:04