Sunday, 23 October 2016 00:00

ለ3 የግል ቴሌቪዥንና ለ3 የኤፍኤም ሬዲዮ ፈቃድ ተሰጠ

Written by 
Rate this item
(5 votes)

    የኢትዮጵያ ብሮድካስት ባለሥልጣን ለሁለት “ሴት ቶፕ ቦክስ” አምራቾች፣ ለሦስት የግል ቴሌቪዥንና ለሦስት የኤፍ ኤም ሬዲዮ ብሮድካስተር ድርጅቶች ፈቃድ ሰጠ፡፡  
ባለፈው ረቡዕ በሸራተን አዲስ በተከናወነው የፊርማ ሥነ-ሥርዓት፣ “ሴት ቶፕ ቦክስ” ለማምረት ከባለሥልጣኑ ዋና ዳይሬክተር ከአቶ ዘርዓይ አስገዶም ጋር የተፈራረሙት ጣና ኮሙኒኬሽን ኃ.የተ. የግ.ማ እና ብረታ ብረት ኢንጂነሪንግ ኮርፖሬሽን ሃይቴክ ኢንጂነሪንግ ኢንዱስትሪ ናቸው፡፡
የግል የቴሌቪዥን ብሮድካስት ፈቃድ የተሰጣቸው ሦስት ድርጅቶች፡- ፋና ብሮድካስት ኮርፖሬሽን፣ ዋልታ ኢንፎርሜሽን ማዕከልና አርኪ ብሮድካስቲንግ ሰርቪስ ኃ.ተ. የግ.ማ ናቸው፡፡ የግል ኤፍ ኤም ሬዲዮ ጣቢያ ብሮድካስቲንግ ፈቃድ የተሰጣቸው ሦስት ድርጅቶች ደግሞ ኤዲስቴለር ትሬዲንግ ኃ.የተ.የግ.ማ (አሐዱ 94.3)፣ አርኪ ብሮድካስቲንግ ሰርቪስና ዋን ላቭ ብሮድካስቲንግ ሰርቪስ ኃ.የተ. የግ.ማ (ሉሲ 107.8) ኤፍ ኤም ሬዲዮ ጣቢያዎች ናቸው፡፡ በዕለቱ የተሰጠው ሦስት የኤፍ ኤም ሬዲዮ ጣቢያ ፈቃድ፣ አሁን በአዲስ አበባና አካባቢያዋ አገልግሎት እየሰጡ ያሉትን ሰባት ጣቢያዎች ጋር ቁጥር ወደ 10 እንደሚያደርሰው ታውቋል፡፡
“ሴት ቶፕ ቦክስ” ማለት አሁን ያለው አናሎግ የቴሌቪዥን ስርጭት ወደ ዲጂታል ሲቀየር ስርጭቱን መቀበል የሚያስችል በቴሌቪዥን አናት ላይ የሚደረግ መሳሪያ ወይም በቴሌቪዥኑ ላይ የሚገጠም አንቴና ነው፡፡ መሳሪያው በዘጠኝ ወር ውስጥ ለአገልግሎት ይደርሳል ተብሏል፡፡ አቶ ዘርዓይ አስገዶም ንግግር ካደረጉ በኋላ የዕለቱ የክብር እንግዳ በምክትል ጠቅላይ ሚ/ር ማዕረግ የኢኮኖሚ ክላስተር አስተባባሪና የመገናኛና ኢንፎርሜሽን ሚኒስትር ክቡር ዶ/ር ደብረፅዮን ገብረሚካኤል  ንግግር አድርገዋል፡፡ በዚሁ ወቅት አቶ ታደሰ ካሳ፤ “ሴት ቶፕ ቦክስ” አምራቾችን፣ አቶ ወልዱ ይመስል፤ የቴሌቪዥን ብሮድካስተሮችን እንዲሁም አርቲስት ሰራዊት ፍቅሬ፤ የኤፍ ኤም ሬዲዮ ብሮድካስተሮችን በመወከል የተሰማቸውን ተናግረዋል፡፡

Read 6628 times