Sunday, 23 October 2016 00:00

‹‹የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ በቱሪዝም ላይ ከፍተኛ ጉዳት እያደረሰ ነው›› - አስጎብኚ ድርጅቶች

Written by  ናፍቆት ዮሴፍ
Rate this item
(6 votes)

     የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ መታወጁን ተከትሎ የውጭ አገር ቱሪስቶች ወደ ኢትዮጵያ የመጓዝ ፍላጎታቸው በእጅጉ መቀነሱን የገለፁ አስጎብኚ ድርጅቶች፤ ለችግሩ መላ ካልተገኘ አዋጁ በቱሪዝም ኢንዱስትሪ ላይ ከፍተኛ ጉዳት እንደሚያደርስ ተናገሩ፡፡ ‹‹አገር የማስጎብኘት ሥራ እንደ ማኑፋክቸሪንግ አይደለም፤ አንድ ፋብሪካ ቢቃጠል ወይም ሌላ ጉዳት ቢደርስበት በዓይን ይታያል። የቱር ኦፕሬሽን ሥራ፣ አገልግሎት ስለሆነ ጉዳት ሲደርስበት በዓይን አይታይም፡፡ አሁን በአገሪቱ በተፈጠረው ችግር ሳቢያ ዘርፉ ጉዳት ደርሶበታል›› ብለዋል፤ የኢትዮጵያ አስጎብኚ ድርጅቶች ማኅበር ፕሬዚዳንት፤ አቶ ያዕቆብ መላኩ፡፡
አስጎብኚ ድርጅቶች ከመስከረም ጀምሮ እስከ ታህሳስ፣ ጥርና የካቲት ያሏቸውን ገበያዎች ሸጠው እንደጨረሱና ደንበኞችም ክፍያ መፈጸማቸውን ጠቅሰው፣ ለሆቴሎችና ለሌላ አገልግሎት አቅራቢያዎችም ክፍያ መፈፀማቸውን ይገልፃሉ። ሆኖም በተፈጠረው ችግር ምክንያት ቱሪስቶች ወደ አገራችን  ለመምጣት  ፍላጎት አላሳዩም ያሉት ፕሬዚዳንቱ፤ አንዳንድ ቱሪስቶች የከፈሉት እንዲመለስላቸው እየጠየቁ መሆኑን ተናግረዋል፡፡  
የተለያዩ የጉዞ አማካሪዎችና ኤምባሲዎች የሚያሰራጩት ወደ ክልከላ ያደገ ማስጠንቀቂያ፣ ለጉብኝት ፕሮግራሞች መሰረዝ ዋነኛ ምክንያት እንደሆኑ የጠቀሱት አቶ ያዕቆብ፣ ‹‹አንዴ ፕሮግራም አድርጌአለሁ፤ ሄጄ ያለውን ነገር አያለሁ›› ብለው የሚመጡ ጥቂት ቱሪስቶች ቢኖሩም አብዛኞቹ ግን ‹‹እኔ እዚህ ዓይነት ችግር ውስጥ ራሴን አልከትም›› በማለት የኢትዮጵያን ጉዞ ሰርዘው፣ ወደ ሌላ አገር እንደሚሄዱ ገልጸዋል፡፡
ድርጅታቸው ሥራ ሲጀምር ጥቂት የነበረው የጎብኚዎች ቁጥር፣ በአሁኑ ወቅት አድጎ በዓመት ከአንድ ሺህ በላይ ቱሪስቶች እንደሚያስተናግድ የገለፁት የሞንፔይ አስጎብኚ ድርጅት ባለቤት አቶ ያሬድ ሙሉጌታ፤ ከኢሬቻ አደጋ በኋላ ፕሮግራሞችን እንደተሰረዙባቸው ተናግረዋል፡፡
መጀመሪያ አካባቢ በዓመት 40 ሺህ ብር ግብር ይከፍሉ እንደነበርና በአሁኑ ወቅት እስከ 1.4 ሚሊዮን ዶላር የሚደርስ ግብር እንደሚያስገቡ የጠቀሱት አቶ ያሬድ፤ ይህ ውጤታማ ሥራ አሁን አገሪቱ ላይ በተፈጠረው አለመረጋጋት እክል እየገጠመው ነው ይላሉ፡፡
‹‹የጎብኚዎች ፍሰት ያለው ከመስከረም አጋማሽ እስከ ግንቦት አጋማሽ ነው፤ በተለይ ታህሳስና ጥር ከፍተኛ የቱሪስት ወቅቶች በመባል ይታወቃሉ›› ያሉት ሥራ አስኪያጁ፣ በአገሪቱ በተከሰተው ብጥብጥተስፋ ሰጪ የነበረው የቱሪስት ፍሰት አደጋ ላይ እንደወደቀ ጠቁመው፤ መንግሥት ያወጣው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅም ጎብኚዎችን ፍርሃትና ጥርጣሬ ውስጥ እንደከተታቸው ያስረዳሉ፡፡  የተለያዩ አገራትም ዜጎቻቸው ወደ ኢትዮጵያ እንዳይሄዱ መከልከል መጀመራቸውም ለዘርፉ ትልቅ አደጋ ነው ብለዋል፡፡
በታህሳስና በጥር ወደ ኢትዮጵያ ለመምጣት ያቀዱ በርካታ ጎብኚዎች ጉዟቸውን እንዳይሰርዙ መንግሥት ከፍተኛ ሥራ መሥራት እንዳለበት የመከሩት የኢትዮ ቱርና ትራቭል መሥራችና ባለቤት አቶ ብሥራት ወልዱ፣ እሳቸው በድርጅታቸውም ሆነ በማኅበራቸው በኩል የሚቻላቸውን ሁሉ እያደረጉ እንደሆነ ገልጸዋል፡፡ ቱሪስት ወደ ኢትዮጵያ ሲጎርፍ የነበረው አገሪቷ ራሷን ስላስተዋወቀች ሳይሆን እዚህ መጥተው በአገሪቱ መስተንግዶ ረክተው የሚመለሱ ጎብኚዎች በሚያሰራጩት መረጃ ነው ያሉት አቶ ብሥራት፤ አሁንም ቢሆን አገር ውስጥ የነበሩ ጎብኚዎች ይህን ሥራ መሥራታቸው እንደማይቀርና ችግሮች በቅርቡ ተስተካክለው ሁሉም ነገር ወደ ቀድሞው እንደሚመለስ ያላቸውን ተስፋ ገልጸዋል፡፡
አገሪቱን ለማረጋጋትና ሰላም ለማስፈን የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ መታወጁ ፋይዳው የጎላ እንደሆነ ብዙዎቹ አስጎብኚዎች አልሸሸጉም፡፡

Read 4331 times