Sunday, 23 October 2016 00:00

ዞሮብናል፤ ይልቅ መፍትሄውን እንፈልግ!

Written by  ዮሃንስ ሰ.
Rate this item
(8 votes)

“ውለዳት” - ኤልያስ ቦጋለ ካሳተመው የግጥም መድበል ጋር ላስተዋውቃችሁ። ለመፍትሄ ያግዛል።
“ሀብት በማፍራት፣ ራስን የመቻልና የመበልፀግ አላማ” እጅግ ቅዱስ አላማ እንደሆነ፣ በቅጡ ማስተዋልና መገንዘብ አልሆነልንም፡፡ ወይም አልፈለግንም፡፡ እህስ? መስዋዕት መሆንንና መፅዋችነትንና  እንደ ጣዖት እናመልካለን፡፡ እና ከድህነት ጋር ተጣብቀን፣ መላቀቅ አለመቻላችን ይገርማል?
ፖለቲካችንንም ተመልከቱ፡፡ አንዳንዴ ይነሳበታል። በጭፍን ስሜትና በሆይሆይታ አገሬው ወደ ነውጥና አመፅ ይንደረደራል፡፡ ግን ብዙም ሳንቆይ፣ ትርምሱ ከደጃፋችን ሲደርስ፣ መንፈሳችን ይቀየራል፡፡ በምትኩ፣ ገናና መንግስትን በመፍራት፣ አንገታችንን መድፋት እንጀምራለን፡፡
ቀስ በቀስ፣ በረዥም ጊዜ እቅድ፣ የእያንዳንዳችን ነፃነት የሚከበርበት፣ የእያንዳንዱን ሰው ነፃነት የምናከብርበት፤ መልካም ስርዓት ለመፍጠር አንጥርም። ወይ ዛሬውኑ ጉልበተኛ አዛዥ ናዛዥ ለመሆን ሆ ብለን እናናውጣለን፡፡
በሰዎች ህይወትና ንብረት ላይ፣ እንዳሻን እየወሰንን መስዋዕት እናደርጋቸዋለን - መስዋዕት የመሆን “የሞራል” ግዴታ አለባቸው እያልን፡፡ ነውጡና አመፁ ወደ ባሰ ጥፋት እንደሚያስገባን ሲገለጥልን ደግሞ፣ ወደ ቀድሞው “ሞድ” እንገለበጣለን፡፡ በጉልበተኛ ገናና መንግስት ስር፣ በፍርሃት አንገት እንደፋለን፡፡ “መስዋዕት የመሆን ግዴታ አለባችሁ” ብሎ ሲገስፀንና ሲሰብከን ለመከራከሪያ የሚሆን አፍ የለንም፡፡ የራሳችንን ስብከት ነው መልሶ የሚነግረን፡፡ ምናለፋችሁ፡፡ ከአዙሪቱ ያልወጣነው፤ በዚሁ የመስዋዕትነት ስብከታችን ሳቢያ ነው፡፡
እንዴ፣ በእውነተኛ መረጃ ላይ የተመሰረተ ቀና የውይይት ነፃነትኮ፣ ከአቅማችን በላይ ወይም ከፍላጎታችን ውጭ ሆኗል፡፡ ነፃነት ማለት፤ እውነትን አሽቀንጥረን በመወርወር፣ ጭፍን የጥላቻ ስሜትን ታጥቀው፣ እየተሰዳደቡና እየተወነጃጀሉ አገሬውን መቀወጥ እናስመስለዋለን፡፡ ከጭፍን ድጋፍና ከጭፍን ተቃውሞ ውጭ፣ … “እውነትን መናገር”፣ እንደ ክህደት እንቆጥረዋለን፡፡ “ሰላም ማውረድና መግባባት” ማለት ደግሞ በአስመሳይነት እየተስማማን፣ የወገኖች አሰልቺ ንግግርን እየተቀባበልን ማነብነብ እንደማለት አድርገነዋል - እውነትን አፍነን እየቀበርን፣ እውነትን እንደ ወንጀል እየቆጠርን፡፡ ታዲያ በጭፍን የጥላቻ ስድብ እና በጭፍን አፈና መሀል ከመንገራገጭ አለመገላገላችን ይገርማል እንዴ?  
የተምታታ ሃሳብ ነው፣ የውድቀት አዙሪት!
ብቃትን ሳይሆን ሚስኪንነትን እንደ ፅድቅ ስናከብር፤... የራሳችን ትርፋማነት ላይ ሳይሆን የተቀናቃኛችን ኪሳራ ላይ ማነጣጠርን እንደ አላማ ስንመርጥ፤... ቅንጣት አትጠራጠሩ፡፡ ነገር አለሙን ሁሉ እንዳምታታነው፣ ከዚህ በላይ ማስረጃ የለም፡፡ የራስን ጥቅም ለማሳደግ ሳይሆን የሌላውን ሰው ጉዳት ለማክበድ፣ የምቀኝነትን ሚዛን እንደ መርህ ስንይዝ፤... በቃ፣ ህይወት ከስረመሰረቷ በአፍ ጢሟ ደፍተናታል፡፡
እውነትን እንደ ክህደት፣ ስቃይ እንደ ጥረት፣ ጉዳት እንደ ሃብት፣ ጉድለት እንደ እንደንብረት፣ ውድቀት እንደ ውጤት እየቆጠርን፣ ስኬትን ሳይሆን መስዋዕትነትን እንደ በረከት ስንመዘግብ... ግራ ቀኙ ሁሉ ሲምታታብን፤... ምን ቀረ? ሰማይ ምድሩ ዞሮብናል ማለት ነው።
አሃ! ብቃት እንደ ሃጥያት፣ ስኬት እንደ ጥፋት የሚታይ ሲሆንኮ፤ በእነዚሁ ምትክ ሚስኪንነትና መስዋዕት ገንነው ይነግሳሉ። ማትረፍ፣ ራስን ማክበር፣ መደሰት ነውር ከሆነኮ፣ ሌሎች ሰዎች ሲከስሩ፣ ሲዋረዱና ሲሰቃዩ የማየት አባዜ ይሰፍናል። በዚህ አባዜ የተቃኘ፣ የሁለት መንግስታት፣ የሁለት ፓርቲዎች፣ የሁለት ፖሊከኞች፣ የሁለት ባለ አክሲዮኖች … ግንኙነት ምን እንደሚመስል አስቡት፡፡ ወይም አስታውሱ። በመጠፋፋት አዙሪት ወደ እንጦሮጦስ ሲወርዱ በተደጋጋሚ አይተናላ፡፡
የሁለት ሰዎች የፍቅር ግንኙነት ውስጥ የሚፈጠረውን ውጥንቅጥ በመመልከት መጀመር ትችላላችሁ - ከኤልያስ ቦጋለ ምርጥ ግጥም።  
ነገሩ እንዲህ ነው፡፡ ከሁለቱ ፍቅረኞች ጎጆ፣ ፍቅር ርቋል፡፡ ‘ጥፋተኛ ነህ’ ብላዋለች ልጅቱ። ጥፋቱ ምን ብሎ እንደሆነም ነግራዋለች። እሱ ምን ብሎ ይመልሳል?
‘አይ፣ እንደዚያ አላደረኩም’ ሊል ይችላል - ጥፋት ካልሰራ። ወይም፣ ‘አዎ እንደዚያ አድርጌያለሁ፣ ግን ጥፋት አይደለም’ ብሎ ማስረዳትም ይችላል - እውነትም ጥፋት ካልሆነ። አልያም፣ ጥፋቱን አምኖ፣ ወደ መፍትሄ ማምራት ይችላል። እነዚህ ሁሉ፣ ጤናማ አማራጮች ናቸው።
አሳዛኙ ነገር፣ ብዙውን ጊዜ የምናየው ክስተት፣ ከእነዚህ ጤናማ መንገዶች የራቀ ነው። እና ምላሹ ምን ይሆናል? አጥፍተሃል፤ አስተካክል›› ስላለችው አንገብግቦታል፡፡ እናም ሁሉንም ነገር በጭፍን እየካደ፣ ጥፋቱን እያላከከ፣ በተገላቢጦሽ ‘ሚስኪን ተጎጂ’ ሆኖ ለመቅረብ ይሟሟታል። እሷን ደግሞ፣ ‘ጨካኝ ሰይጣን ነሽ’ ይላታል፡፡ የአፀፋ ውንጀላ እየደረደረ፣  ጠላትነትን እያወጀ፣ ተራራ የሚያክል የጥፋተኝነት ስሜት ያሸክማታል - እንክትክቷ ሲወጣ ለማየት እየተመኘ። የመጠፋፋት አዙሪቱ ተጀመረ ማለት ነው፡፡     “አንድ እኩል” ከተሰኘው የኤልያስ ግጥም፣ ጥቂት ስንኞችን እናንብብ፡፡         
አትስከር ትላለች፤... ጭራሹን አትጠጣ
ሞኝሽን ፈልጊ፣... በሏት እርሟን ታውጣ
እቀዳለሁ ገና፣... እጨሳለሁ ብዙ
በሷ ከምቆስለው፣... አይብስም መዘዙ
[ተጎጂ፣ ምስኪን እንደሆነ ለማሳየት ይሞክራል። ለሱ ጥፋት፣ … ዋና ተጠያቂዋ እሷ እንደሆነች ማመን ነበረባት። ግን ይህንን አልተረዳችም፣ ደልቶኝ ይመስላታል ሲል ያማርራል። መነሻው አልገባትም ... የዚህ ሁሉ ጣጣ]
የፍቅር ጥማቴን፣... እቆርጥበት ባጣ
በሷ እንደምሰክር፣... በሷ እንደምጠጣ
[ለካ፣ ጥፋተኛዋ እሷ ናት። ይህም ብቻ አይደለም። የራሱን ጥፋት በሷ ላይ በማላከክ ብቻ አላቆመም፤ ውንጀላ ጨምሮበታል። እሱ እንደሚለው ከሆነ፤ ደህንነቱን ንዳ፣ እምነቱን አፍርሳለች! ምኑ ተረፈ? ገድላዋለችኮ። እንዲያውም፣ አማላጅ ሽማግሌ ሰብስባ ብትልክበት፣ ፈፅሞ እንደማይሰማ ዝቷል። ደላላ አዋዋይ ቢንጋጋ አልቀበልም። አትልፉ ብሏል። እህሳ?]
ፍትህ የጎደለው፣... መች ይዳለልና፣... ይዋዋላል ካሳ
እርቅ ብሎ ነገር፣... አይኖርም ከንግዲህ፣... በቃ ሁሉን ትርሳ።
[ምንም ብናስረዳው፣ ብናባብለው... ፍንክች የለም። አማላጅ መላኳ፣ ደጅ መጥናቷ... የውሸት ነው - ለማስመሰል። በከንቱ መቅለስለሷ፣ መንፈሴን ልትፈትንና ልትረታ ፈልጋ ነው ይላል። የፅድቅ ስራዎቹን እንድንመዘግብለትም ይዘረዝራል- ሚስኪንነትን የሚያረጋግጡ የመስዋዕትና የተጎጂነት ዝርዝር፡፡ እኔ ምስኪኑ በፍቅር ተንበርክኬ፣ ህይወቴን አስይዣት፣ ሁለመናዬን ወርሳ ነግሳለች እያለ ያለቃቅሳል። እሷን ደግሞ ሰይጣን ለማስመሰል ይወነጅላታል...]
ነፍሴ ምኗም አይደል፣... ምኔ ያጓጓታል?
ካዳሞቿ መንጋ፣...
አንድ እኔ ብቀነስ፣... ምን ይጎድልባታል?
የሚያብለጨልጯት፣... ውጪ ሞልተዋታል።
[ኧረ፣ እንዲህ ባልተጨበጠ ወሬ፣ ስሟን ማጥፋት ነውር ነው። የወንድ መንጋ? ታውቃለህ፡፡ እሷ እንዲህ አላደረገችም። ጨዋ ናት፡፡ እንዲህ እውነታውን  የሚነግረው ሰው ቢያገኝ፣ ጭፍን ውንጀላውን ትቶ ወደ ህሊናው ይመለስ ይሆን? ጨዋ መሆኗን ቢያውቅ እንኳ፣ ይተናነቀዋል። ከየት እንዴት ብሎ፣ የፍቅር መንፈስ ያዛት? ሊሆን አይችልም እያለ ይከዳል። አፍቃሪ መምሰሏ ተንኮል ነው - ይህቺ ብልጣብልጥ ሴረኛ...]
ይሄ ፍቅር ‘ሚሉት፣... ዟሪ መንደርተኛ
ከመቼ ወዲህ ነው፣... ልቧ ላይ የተኛ?
እንዲህ በቀላሉ፣... እንዴት አደብ ገዛች
እንዲህ በቀላሉ፣... ምን መንፈስ አወዳት
እንቅዥቅዥ ስሜቷን፣... ሰክኖ ያበረዳት?
      *  *  *
አታጭስ ትላለች፣... እራሷው ለኩሳ
ውስጧ እያሴረ፣... አፏን አመንኩሳ
[ይሄ ሰውዬ ጤና የለውም! በተጎጂነት ስሜት እያላዘነ እድሜውን በስቃይ የመግፋት አባዜ፣ የምስኪንነት ሱስ ተጠናወተው እንዴ? እሺ ምንድነው የሚፈልገው? እሷ ያለ ጥፋቷ በጥፋተኝነት ስሜት ስትብሰለሰል ማየት ነው የሚፈልገው። ግን፣ እሷ ብትሰቃይ፣ ምን ይጠቀማል? ምን ያተርፋል? የጥቅም እና የትርፍ ጉዳይማ፣ ጨርሶ በሃሳቡ ውስጥ የለም፡፡ ነውር ነዋ፡፡ ሁለት አማራጮች ብቻ ናቸው የሚታዩት፡፡ ወይ እሱ መስዋዕት ይሆናል፡፡ ወይ እሷ በተራዋ መስዋዕት እንድትሆን ያደርጋል፡፡ ወይ እሱ በምስኪንነት መላወስ፣ ወይም እሷ በምስኪንነት መንከባለል አለባት። የየራሳቸውን ክብር ጠብቀው፣ በፍቅር መኖርና መደሰት አይችሉም። ገዢ እና ተገዢ፣ በዳይና ተበዳይ፣ ጨካኝና አቅመ-ቢስ፣ ረጋጭና ተረጋጭ፣ እብሪተኛና ምስኪን... ከዚህ ውጭ አማራጭ አይታየውም። እና ምን ይደረግ? ምንስ ትሁንለት?]
እርግጥ ከተሰማት፣...
ጣሬን ከተጋራች፣... ቁስለቴ ካመማት
ድንድን ህሊናዋ፣... ታምር ካቀለጠው
እዚ-ዛ ማለቷን፣... ጊዜ ከለወጠው
[እሰይ] ትደፋልኝ፣... እግሬን በ’ንባ ትጠብ
የ‘ይቅርታ’ መዓት፣... አዝንባልኝ ልርጠብ
እንደኔ ትጨቆን፣... ትንሽ ትየው አዝና
በስጋት ይበርበር፣... በማጣት ይሰበር፣... የመውደዷ ካዝና
...
የውስጧ ፀፀት ነውጥ፣... ወጀቡ ሳይሰክን
ላንቃዋን ሳግ ደፍኖት፣... ቃል ፅንሷ ሲመክን
ጥቂት ልሳቅባት፣... ልግፋት በተራዬ
ኩራት ያመፃድቀኝ፣... ይግነን ፉከራዬ
የብቻነት አሳር፣... ዋይታዋ ላይ ነግሶ
ቅስሟን ብራቅ ይምታው፣... በፍርሃት ተወርሶ
[ያለ ጥፋቷ የሚወርድባት ይሄ ሁሉ ቅጣት፣ በአንድ ቀን የምትገላገለው ስቃይ አይደለም። ገና ይቀጥላል። ማቅ እንደለበሰች በተማፅኖ እስክትደክም ድረስ፣ በብሶት ጨቅይታ ከአፍንጫዋ በላይ ደርሶ ህይወት እስኪያንገሸግሻት ድረስ፣ ... ማንነቷ ክብሯ ተሰባብሮ ከንቱ ብኩን፣ ከመናኛም ምስኪን እስክትሆን ድረስ፤... የሱ ገናና ገዢነት፣ አብጦ ሰፍቶ እስኪሰለቸው ድረስ!!! ከዚያስ? በዕለተ ምፅዓቱ፣... የእንጦሮጦስ መግቢያ፣ ጥልቁ አፍ ሲከፈት...]
ጭላንጭል ተስፋዋን... አፈር ሳታለብሰው፣... ቀን ሳይከዳት በፊት፣
ያኔ በውሃው ቀን፣... እታረቃታለሁ፣... ያለናንተ ግፊት።
[መስሎታል! ምን ይመስለዋል? ማንነቷ ተንኮታኩቶ፣ የራስ ክብሯ ተሰባብሮ፣ ኦና ከሆነች በኋላ፣ “እንታረቅ” ሲላት፣ እንደማትሰማው ያውቃል። አማላጅ ቢያንጋጋ፣ ምላሿ ምን እንደሚሆን አያጣውም። እሷም፣ በተራዋ በተጎጂነት እያላዘነች፣ … እሱ በተራው ሲሰቃይ፣ ሲዋረድ፣ ሲንከባለልና አፈር ድሜ ሲበላ ለማየት እንደምትቋምጥ ይጠብቃል። ምን ትጠቀማለች? ምንም! ደግሞስ፣ የጥቅም ፉክክር ሳይሆን፣ የተጎጂነት ፉክክር ውስጥ፣ ጥቅም ከየት ይመጣል? በዳይና ተበዳይ፣ ገዢና ተገዢ የመሆን ሱስ፣ ማብቂያ የሌለው አዙሪት ነው። እየተፈራረቁና ቦታ እየተቀያየሩ፣ አንድ እኩል፣ ሁለት እኩል... እያሉ እድሜያቸውን በክፋትና በስቃይ ይጨርሳሉ። ለግጥሙ፣ “አንድ እኩል” የሚል ርዕስ ሰጥቶታልኮ - ገጣሚው ኤልያስ]
መቼም፣ አንድ እኩል … ሁለት እኩል እያለ በሚጦዘው የመስዋዕት ፉክክር ውስጥ፣ በፍርርቆሹ መሃል፣ የየዙሩ አሸናፊ እስኪታወቅ ድረስ፣ ለጊዜውም ቢሆን፣ ትንቅንቅ ይኖራል። አሳዛኙ ነገር፣ ከትንቅንቁ አንዳችም ጥቅም አያገኙበትም።
መሃላችን፣ ድንበር ሰርተን፣... ማናችንም፣ ላንከብርበት
ተግተን ጉድጓድ እንምሳለን፣... በየተራ ልንወድቅበት
ይቅርታ፣ የገጣሚውን ሃሳቦች ባላዘባም፣ አንድ ሁለት ቃላት ስቻለሁ፡፡ ድንቅ ስንኞቹን በቀጥታ እያነበብን እንድናጣጥም በመፅሃፉ ገፅ 5 ላይ ከሰፈረው ግጥም እነሆ።
“እኔና አንቺ” ...ትግል ይዘን፣ ለዘመናት፣
ተተ...ናንቀን፣ እኩል-ለኩል፤
ልብሽ ጓዳ፣ የስጋት ካብ፣ ስትጠርቢ፣
አይንሽ ግርጌ፣ የቅናት ጡብ፣ ስኮለኩል፡፡
...
ባንድ ልሳን፣ ያዚያዚያመን፣
ያቀኛኘን፣ ፍቅር ቋንቋ፣
እንደ ወትሮ፣ ላያግ...ባባን፤
ነጋችንን፣ የጋረደ፣
ለዝንታለም፣ የማይናድ፣
የጥል ባቢ...ሎን ገነባን።
እሱና እሷ የገቡበት አዙሪት፤ መውጪያ የሌለው፣ አሳዛኝ እጣፈንታ ይመስላል። ጥቅም ላይገኝበት፣ በየተራ ለመውደቅ፣ መተናነቅ፤... ገዢ እና ተገዢ እየሆኑ ለመፈራረቅ፣ እብሪትን ከጥፋተኝነት ስሜት ጋር፣ ሚስኪንነትን ከተበዳይነት ስሜት ጋር እየቀባቡ ማላዘን። ይሄ ለምን ይሆናል? ምንድነው ችግሩ?
እንዲህ ይላል “ልንገርሽ” የሚለው የኤልያስ ግጥም
የራዕይሽ፣ ሳንካ ሆኜ፣....
ህይወት ጥድፊያ_ሽን ከገታሁ፤
የጉድፌን ቋ_ጥኝ ፈንቅዬ፣...
ልንድሽ አ_ፌን ከፈታሁ፤
...
ክቡድ ገፅሽ፣ ጭጋግ ወርሶት፣
   ንጋቴ ላይ፣ ከተጋረጥሽ፤
የነውር ትቢያ፣ ልት_ቀቢኝ፣
   የነገር ጭ_ቃ ካላቆጥሽ፤
እኔም ሴቴን፣ አላገኘሁ፣
   አንቺም ወንድ_ሽን አልመረጥሽ።
እርስ በርስ፣ ሳንካ ወይም ጋሬጣ ለመሆን ከተሸቀዳደሙ፣... ወይም... በየተራ መስዋዕት አቅራቢና መስዋዕት ተቀባይ እንሁን ሲሉ … ማናቸውም የማይደሰቱበት የስቃይ ፈረቃ ውስጥ ይገባሉ። ፍቅር ማለት፣... ከመነሻው የተፋቀሩበትንና የተዋደዱበትን፣ መልካምና አኩሪ ማንነታቸውን፣ በከንቱ የሚያስረክቡበት የእርድ ስፍራ መስሏቸዋል። የደስታና የእርካታ ጭላንጭል እስኪጠፋ ድረስ፣ እያፈራረቀ ራዕይዋንና ስኬቱን የሚያከስል፣ በየተራ አንዱ ማገዶ፣ ሌላኛው ማገዶ አቀባይ የሚሆኑበት የመሰዊያ እቶንን ነው የገነቡት። ይሄ ፍቅር አይደለም። ይሄ ሲኦል ነው።
ፍቅር፣ የዚህ ተቃራኒ ነው፡፡ እሷ አበባው፣ እሱ ልምላሜዋ የሚሆኑበት፣ ብሩህ መስክ ይሆንላቸው ነበር ቢያውቁበት።
በእውነተኛው የፍቅር ዓለም ውስጥ፤ እሷ ራዕይዋን መስዋዕት አታደርግም፤... የሱ ስራ፣ ሳንካ መሆን አይደለምና። እሱ፣ ንጋቱን መስዋዕት አያደርግም፤... የሷ ድርሻ ጋሬጣ መሆን አይደለምና። ራዕይዋ፣... የእኔነቷ፣ የማንነቷ ገፅታ ነው። ግን፣ የሷ ራዕይ፣ ለሱም ብርሃንና ብርታት ይሆንለታል። ንጋት፣... የግል ህልውናውና የማንነቱ አካል ነው። ግን፣ የሱ ንጋት፣ ለሷም ሙቀትና ጉልበት ይሆንላታል።... ፍቅር እንዲህ ነው።... በትክክል ተጣጥመው የሚገጣጠሙበት። ‘እሱም አግኝቷታል። እሷም መርጣዋለች’ የምንልበት ሕይወት!!
በአንድ በኩል፣ በምስኪንነት የመስዋእት ሲኦል ውስጥ መግባት ይችላሉ - ካለመረዳት ወይም በምርጫ። በሌላ በኩል ደግሞ፣ መልካም ራዕይንና የስኬት ንጋትን የሚቋደሱበት ጣፋጭ አለም ውስጥ መግባት ይችላሉ - ነገሩ ከገባቸው፣ ከተገነዘቡት፣ ከተጣጣሩ፣ ምርጫቸው ከሆነ።    
በአጭሩ፣ ጉዳዩ … የግንዛቤና የምርጫ ጉዳይ ነው። የመስዋዕት ዓለም እና የስኬት ዓለም እንደሚለያዩ መገንዘብና አንዱን መምረጥ፣ የእያንዳንዱ ሰው ድርሻ ነው፡፡ ከኤልያስ ቦጋለ ምርጥ ግጥሞች መካከል፣ አንዷን እንድታጣጥሙ ብጋብዛችሁ ይሻላል - የሁለቱ አለማት ልዩነት እንዲገባንና፣ አንዱን መርጠን እንድንገባ።
ምርጫ
ከገባህ........
መስራት በሚያስከብር፣... በትጉዎች መንደር፤
እስኪያልብህ እሩጥ፣... እንቅልፍ አጥተህ እደር።
በስምህ እን_ዲዋብ፣... የስኬትህ ዋንጫ፤
ዛሬህ መሰላል ነው፣... ነገን መወጣጫ።
ካልገባህ........
ፅኑነት ባል_ዋጀው፣... የምስኪኖች አለም፤
አትሁን ተስ_ፈኛ፣... ነገ ‘ሚባል የለም።
ቁርጧ እስከሚታወቅ፣... ህይወት ብስክስኳ፣
ዛሬህ ላይ ተ_ኝተህ፣... ትናንትን አ_መስኳ።

Read 5002 times