Sunday, 30 October 2016 00:00

የቀድሞ ፍቅረኛው ላይ አሲድ የደፋው፤ የ18 ዓመት ፅኑ እስራት ተፈረደበት

Written by 
Rate this item
(2 votes)

ባለፈው ዓመት ግንቦት ወር ላይ በዳንግላ ከተማ የቀድሞ ፍቅረኛው ላይ የአሲድ ጥቃት የፈፀመው ሰለሞን በላይ፤ የ18 ዓመት ፅኑ እስራት ተፈረደበት፡፡ የአማራ ክልል የዳንግላ ዞን ከፍተኛ ፍርድ ቤት በትናንትናው ዕለት በዋለው ችሎት ተጎጂዋ መሰረት ንጉሴ በአካል ተገኝታ የጥቃቷን መጠን አስረድታለች፡፡ ምንም እንኳ ጥፋተኛው የፈፀመው ጥቃት በሞትና በእድሜ ልክ እስራት የሚያስቀጣ ቢሆንም ድርጊቱን መፈፀሙን በማመኑና ከዚህ ቀደም የወንጀል ሪከርድ የሌለበት በመሆኑ፣ ፍ/ቤቱ በ18 ዓመት ፅኑ እስራት እንደቀጣው የዳንግላ ከተማ ሴቶች፣ ህፃናትና ሰራተኛና ማህበራዊ ጉዳይ ጽ/ቤት ሀላፊ ወ/ሮ አዛሉ ናደው ለአዲስ አድማስ ገልፀዋል፡፡
‹‹ጥፋተኛው ወንጀሉን ከፈፀመበት ዕለት አንስቶ በቁጥጥር ስር የዋለ ሲሆን እኛም በጉዳዩ ላይ ጥብቅ ክትትል ስናደርግ ነበር›› ያሉት ሀላፊዋ፤ ምንም እንኳ በሞትና በእድሜ ልክ እስራት የሚያስቀጣ ወንጀል ቢፈፅምም ፍ/ቤቱ አንዳንድ ነገሮችን ከግምት አስገብቶ የ18 ዓመት እስር መፍረዱ ሌሎችን የሚያስተምር ተገቢ ቅጣት ነው ብለዋል፡፡ ወጣቷ ተጎጂ አሁንም በከፍተኛ ስቃይ ላይ መሆኗን የገለፁት ሀላፊዋ፤ ወቅታዊው የፀጥታ ችግር ትኩረታቸውን ስቦት እንጂ ከዳንግላ ከተማ አስተዳደር፣ ከክልሉና ከባለሀብቶች ጋር በመተባበር ልጅቷ አስቸኳይ የውጭ ህክምና የምታገኝበትን መንገድ ለማፈላለግ እንተጋ ነበር ብለዋል፡፡
ወጣት መሰረት ንጉሴ አዲስ አበባ በሚገኙ በጎ ፈቃደኛ ግለሰቦች ድጋፍ ላለፉት አምስት ወራት የቀለብ፣ የህክምናና የቤት ኪራይ ወጪ ተሸፍኖላት፣ መጠነኛ ህክምና ብታደርግም ጤናዋ መሻሻል ባለመቻሉ ወደ ውጭ አገር ሄዳ ለመታከም እስከ 1 ሚ.ብር መጠየቋን ለአዲስ አድማስ ገልፃለች፡፡
ባለፈው ጥቅምት 3 ቀን 2009 ዓ.ም በአዜማን ሆቴል የገቢ ማሰባሰቢያ ፕሮግራም ተዘጋጅቶላት የነበረ ሲሆን በዚህ ዝግጅት ከ200 ሺህ ብር የበለጠ ባለመገኘቱ በአስቸኳይ ወደ ውጭ ሄዳ ለመታከም እንዳልቻለች ገልፃ፤ አሁንም የኢትዮጵያ ህዝብ እንዲደርስላት ጥሪ አቅርባለች፡፡
ፍርድ ቤቱ በወንጀለኛው ላይ የሰጠውን ፍርድ በተመለከተ ለአዲስ አድማስ አስተያየቷን የሰጠችው ተጎጂዋ፤ ‹‹በእርግጥ ሞት ወይም የእድሜ ልክ እስራት ይፈረድበት ብለሽ ይግባኝ ጠይቂ ተብዬ ነበር፤ 18 ዓመት ከህሊና ፀፀት ጋር በቂ ነው ብዬ ትቼዋለሁ›› በዋና የምግብ አብሳይነት (Chef) እየሰራች ራሷንና ወላጅ የሌላቸውን ታናናሽ እህቶቿን ታሳድግ እንደነበር ያስታወሰችው መሰረት፤ አሁን በደረሰባት ጉዳት እህቶቿ ያለ ረዳት መቅረታቸውን ጠቅሳ፤ ይህም ሌላ ህመም እንደሆነባት ተናግራለች፡፡

Read 4842 times