Sunday, 13 November 2016 00:00

የአሜሪካ ምርጫ ውጤት ተቃውሞ ተባብሶ ቀጥሏል

Written by 
Rate this item
(6 votes)

የጸረ-ትራምፕ ተቃውሞው ከ27 በላይ ከተሞችን አዳርሷል
    በዘንድሮው የአሜሪካ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ ሪፐብሊካኑን ወክለው የተወዳደሩት ዶናልድ ትራምፕ ማሸነፋቸውን የሚገልጸው የምርጫ ውጤት ይፋ መደረጉን ተከትሎ፣ በአገሪቱ የተለያዩ አካባቢዎች ባለፈው ረቡዕ የተቀሰቀሰው ተቃውሞ ተባብሶ መቀጠሉ እየተዘገበ ነው፡፡
የትራምፕን በምርጫ ማሸነፍ በመቃወም ወደ አደባባይ የወጡ ተቃዋሚዎች በአስር ሺህዎች እንደሚቆጠሩ የዘገበው ሲኤንኤን፤ ረቡዕ ዕለት የተጀመረው ተቃውሞ ወደ በርካታ የአገሪቱ አካባቢዎች መዛመቱንና እስከ ሃሙስ ድረስም ከ25 በላይ በሚሆኑ የአገሪቱ ከተሞች ተቃውሞ መደረጉን ጠቁሟል፡፡
ተቃዋሚዎቹ ትራምፕ ስልጣን መያዛቸው አግባብ አለመሆኑንና አገር የመምራት ብቃት እንደሌላቸው በመግለጽ፣ ፎቶግራፋቸውን ከማቃጠልና በተለያዩ ተቋማት ላይ ጥፋት ከማድረስ አልፈው በአንዳንድ የአገሪቱ አካባቢዎችም የምርጫ ውጤቱ እንዲሰረዝና ሄላሪ ክሊንተን ስልጣን እንዲይዙ እስከመጠየቅ መዝለቃቸውን ዘ ጋርዲያን ትናንት ዘግቧል፡፡
ረቡዕ የጀመረው ተቃውሞ ሃሙስም ወደ ዴንቨር፣ ሚኒያፖሊስ፣ ፖርትላንድ፣ ኦክላንድና ሌሎች የአሜሪካ ከተሞች መስፋፋቱን የዘገበው ዘ ጋርዲያን፣ በፖርትላንድ 4 ሺህ ያህል ተቃዋሚዎች አደባባይ በመውጣት በፖሊስ መኮንኖችና በመደብሮች ላይ ጥቃት መፈጸማቸውንና ፖሊስም ከ29 በላይ ሰዎችን ማሰሩን ገልጧል፡፡
በዴንቨርም 3 ሺህ ያህል አሜሪካውያን ተቃውሞ ማድረጋቸውን የጠቆመው ዘገባው፣ በመቶ ሺህዎች የሚቆጠሩ አሜሪካውያን በቀጣይም ተቃውሟቸውን ለመቀጠልና የትራምፕን አሸናፊነት እንደማይቀበሉ የሚገልጹ ድርጊቶችን ለመፈጸም እያቀዱ ነው ሲል ዘ ጋርዲያን ትናንት ዘግቧል፡፡
በዋሽንግተን ሰፋ ያለ ተቃውሞ ለማድረግ ታስቦ በፌስቡክ የተከፈተው ዘመቻ እስከ ሃሙስ ተሲያት ድረስ፣ 30 ሺህ አባላትን ማፍራቱን የጠቆመው ዘገባው፤ ተቃውሞውን የሚደግፉ የቡድኑ አባላት ቁጥር በየሰዓቱ በሺህዎች እያደገ እንደሚገኝ አስታውቋል፡፡
አሜሪካ በትራምፕ አሸናፊነት በተከፉ ተቃዋሚዎች ብትጥለቀለቅም፣ በምርጫ ቅስቀሳው ወቅት አንዳቸው ሌላኛቸውን ሲያብጠለጥሉና ሲወነጅሉ የከረሙት ተመራጩ ዶናልድ ትራምፕና ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ ግን፣ ሃሙስ በዋይት ሃውስ ተገናኝተው ልዩነትን ያሸነፈ ውይይት አድርገዋል ተብሏል፡፡
ኦባማና ትራምፕ 90 ደቂቃ በፈጀው ውይይታቸው፤ ሰላማዊ የስልጣን ሽግግር በሚደረግበት ሁኔታና በሌሎች ብሄራዊና የውጭ ጉዳይ ፖሊሲዎች ዙሪያ መምከራቸውን ዘ ጋርዲያን ዘግቧል፡፡


Read 5176 times