Saturday, 12 November 2016 13:28

ሔኖክ መሐሪ የ”አፍሪካ ሚዩዚክ አዋርድ” አሸናፊ ሆነ

Written by 
Rate this item
(2 votes)

ድምፃዊ ሔኖክ መሀሪ፤ ‹‹እውድሻለሁ›› በተሰኘው ዘፈኑ በ”ምርጥ የአር ኤንድ ቢ” እና የ”ሶል” አፍሪካዊ ድምፃዊ በመሆን፣ የ”ኦልአፍሪካ ሚዩዚክ አዋርድ” (አፍሪማ 2016) አሸናፊ ሆነ፡፡ ባለፈው እሁድ በናይጄሪያ ሌጎስ ከተማ በተካሄደው የሽልማት ስነስርዓት ላይ ሔኖክ ባሸነፈበት ዘርፍ 7 ታዋቂና ተፅዕኖ ፈጣሪ የናይጄሪያ ድምፃዊያን፣ ሁለት ደቡብ አፍሪካዊያን፣ አንድ ሩዋንዳዊና አንድ ማላዊ ድምፃዊያን ፉክክር አድርገው የነበረ ቢሆንም በመጨረሻ ሄኖክ ማሸነፉን ገልጾ፣ሆኖም አሸንፋለሁ ብሎ እንደላልጠበቀ ለአዲስ አድማስ ተናግሯል፡፡  
ጃኖ ባንድ ‹‹ዳሪኝ›› በተሰኘው ዘፈን፣ በ”ምርጥ ሮክ” እና “ምርጥ ቡድን”፣ ድምፃዊት ፍቅር አዲስ ነቅአጥበብ ደግሞ ‹‹ምስክር›› በተሰኘው ዘፈኗ፣”የምስራቅ አፍሪካ ምርጥ ሴት ድምፃዊት” እንዲሁም ድምፃዊ አንተነህ ምናሉ ‹‹ዋዮ›› በተሰኘው ዘፈኑ፣ “ተስፋ የተጣለበት ድምፃዊ” እና “ምርጥ የሬጌ አቀንቃኝ” በሚሉ ዘርፎች ታጭተው የነበረ ሲሆን ማሸነፍ ግን አልቻሉም፡፡
ውድድሩ 50 በመቶ በሙዚቃ ባለሙያ ዳኞች ነጥብ የሚሰጠው ሲሆን 50 በመቶው በህዝብ ምርጫ የሚገኝ ነጥብ መሆኑን የጠቆመው ድምፃዊ ሄኖክ፤ቅስቀሳ በተጀመረ ሰሞን ፌስቡክ መዘጋቱ ፈታኝ ቢሆንም ተስፋ ባለመቁረጥ በተለያዩ መገናኛ ብዙኃን ባደረገው ቅስቀሳና ዳኞች በሰጡት 50 በመቶ ነጥብ ማሸነፉ እንዳስደነገጠው አልደበቀም፡፡ ድምፃዊት ፀደንያ ገ/ማርቆስ ‹‹ሀርየት›› ለተሰኘው ፊልም በሰራቸው የማጀቢያ ሙዚቃ፣ባለፈው ዓመት (2015 አፍሪማ አዋርድ) “የምስራቅ አፍሪካ ምርጥ ሴት ድምፃዊት” በሚል ዘርፍ ማሸነፏ አይዘነጋም፡፡  
 በ34 የተለያዩ ዘርፎች አርቲስቶችንና የሙዚቃ ሥራዎቻቸውን አወዳድሮ አሸናፊዎችን ለሽልማት የሚያበቃው “አፍሪካ ሚዩዚክ አዋርድ”፤ በአህጉሪቱ ትልቁ ሽልማት እንደሆነ ይታወቃል፡፡ የሽልማት ውድድሩ በየዓመቱ የሚካሄድ ሲሆን ዘንድሮ 2714 አፍሪካዊያን አርቲስቶች ተመዝግበው እንደነበረም ለማወቅ ተችሏል፡፡ በሌጎስ በተካሄደው በዚህ የሽልማት ስነስርዓት ላይ ከ2500 በላይ ጥሪ የተደረገላቸው የተለያዩ አፍሪካዊያን እንግዶች ታድመው እንደነበር ለማወቅ ተችሏል፡፡

Read 1059 times