Sunday, 13 November 2016 00:00

ወጋገን ባንክ ከ478 ሚሊዮን ብር በላይ አተረፈ

Written by 
Rate this item
(1 Vote)

  20ኛ ዓመቱን ለማክበር በዝግጅት ላይ የሚገኘው ወጋገን ባንክ፣ባለፈው ዓመት ባደረገው እንቅስቃሴ ከታክስ በፊት 478.5 ሚሊዮን ብር ማትረፉን አስታወቀ፡፡
ባንኩ ከትናንት በስቲያ ባካሄደው 23ኛ መደበኛና 12 ድንገተኛ ዓመታዊ የባለአክሲዮኖች ጉባዔ የባንኩ ፕሬዚዳንት አቶ አርአያ ገ/እግዚአብሔር ባቀረቡት ሪፖርት፣ አምና (2015/16) ባደረገው እንቅስቃሴ ታክስ፣ መጠባበቂያና ሌሎች ውጪዎች ከተቀነሰ በኋላ 375.6 ሚሊዮን ብር የተጣራ ትርፍ ማግኘታቸውን ገልጸዋል፡፡
ለመንግሥት 102.9 ሚሊዮን ብር ግብር መክፈላቸውን፣ የተገኘው ትርፍ ከቀደመው ዓመት ጋር ሲነፃፀር የ6.6 በመቶ ብልጫ ማሳየቱንና ከእቅዱ 92 በመቶ ማሳካቱም ተጠቁሟል፡፡  
ካቻምና 1.5 ቢሊዮን ብር የነበረው የባንኩ የተከፈለ ካፒታል፣ አምና 1.8 ቢሊዮን ብር መድረሱንና ጠቅላላ ካፒታሉም ወደ 2.8 ቢሊዮን ብር ማደጉን ለማወቅ ተችሏል፡፡ የባንኩ ጠቅላላ ሀብት ካቻምና ከነበረው 13.7 ቢሊዮን ብር አምና ወደ 16.2 ቢሊዮን ብር ደርሷል፡፡ የተሰበሰበ ተቀማጭ ገንዘብ 11.8 ሚሊዮን ብር ሲሆን የመደበኛ ብድር መጠንም የግምጃ ቤት ሰነድ ግዢን ሳይጨምር 7.6 ቢሊዮን ብር እንደሆነ ተነግሯል፡፡
ባንኩ እ.ኤ.አ በ2025 በአፍሪካ ከሚገኙ 10 ስመጥርና ተፎካካሪ ባንኮች አንዱ የመሆን ራዕዩን ለማሳካት እየተጋ መሆኑን የጠቆሙት ፕሬዚዳንቱ፤ የደንበኞች አገልግሎት አሰጣጥን ለማሻሻል፣ የሰው ኃይል ብቃትን ለማጎልበት፣ የአገልግሎቱን ተደራሽነት ለማስፋትና የኢንፎሜሽን ቴክኖሉጂ አቅሙን ለማሳደግ እየሠራ ነው ብለዋል፡፡  
የባለአክሲዮኖች ቁጥር 2,456 የደረሰ ሲሆን ባንኩ በአሁኑ ሰዓት 3,385 ሠራተኞችን በሥሩ ያስተዳድራል፡፡ ወጋገን፤ ስታዲየም አካባቢ በማስገንባት ላይ ያለው ባለ 23 ፎቅ፣ ዘመናዊ የዋና መ/ቤት ሕንፃ፣75 በመቶ መጠናቀቁ ተጠቁሟል፡፡

Read 1435 times