Sunday, 20 November 2016 00:00

3 ሚ. ብር የሚገመት ወርቅ በድብቅ ወደ ህንድ ያስገባች ኢትዮጵያዊት ታሰረች

Written by 
Rate this item
(11 votes)

3.1 ኪሎ ግራም ክብደት ያለው ወርቅ በህገ-ወጥ መንገድ በድብቅ ወደ ህንድ ለማስገባት የሞከረች ኢትዮጵያዊት፣ ከትናንት በስቲያ በአውሮፕላን ጣቢያ የጉምሩክ ፍተሻ ሰራተኞች ተይዛ መታሰሯን “ዚኒውስ” የተባለው የአገሪቱ ድረገጽ ዘገበ፡፡
ስሟ ያልተገለጸው ይህቺው ኢትዮጵያዊት፣ ከአዲስ አበባ በመነሳት ወደ ህንድ ያደረገቺውን ረጅም የአውሮፕላን ጉዞ አጠናቅቃ፣ ኒው ደልሂ በሚገኘው ኢንድራ ጋንዲ አውሮፕላን ማረፊያ ጣቢያ ስትደርስ፣ የጉምሩክ ሰራተኞች በሻንጣዋ ላይ ባደረጉት ፍተሻ፣ በህገወጥ መንገድ ልታስገባቸው የነበሩ በድምሩ 3.1 ኪሎ ግራም የሚመዝኑ አምስት ቁራጭ ወርቆችና የወርቅ ጌጣጌጥ መያዛቸውን ዘገባው ጠቁሟል፡፡
የኒው ዴልሂ የጉምሩክ መስሪያ ቤት ጉዳዩን በተመለከተ ትናንት ያወጣውን መግለጫ በመጥቀስ፣ ግለሰቧ በድብቅ ልታስገባቸው የነበሩት ወርቆች በፖሊስ እንደተያዙና እሷም ወደ እስር ቤት እንደገባችም ዘገባው አክሎ ገልጧል፡፡
ትናንት በዋለው የብሄራዊ ባንክ የውጭ ምንዛሬና የወርቅ ዋጋ ተመን መሰረት፣ ኢትዮጵያዊቷ በህገ ወጥ መንገድ ወደ ህንድ ልታስገባው የሞከረቺው ወርቅ 3 ሚሊዮን ብር ያህል እንደሚያወጣ ይገመታል፡፡

Read 4588 times