Sunday, 20 November 2016 00:00

በየቀኑ 547 ደቡብ ሱዳናውያን ወደ ኢትዮጵያ ይገባሉ

Written by 
Rate this item
(7 votes)

በኢትዮጵያ ሱዳናውያን ቁጥር 322 ሺህ 452 ደርሷል
    ወደ ኢትዮጵያ የሚሰደዱት ደቡብ ሱዳናውያን ቁጥር እየጨመረ ነው ያለው የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የስደተኞች ጉዳይ ከፍተኛ ኮሚሽን፤ በየቀኑ በኣማካይ 547 ያህል ደቡብ ሱዳናውያን ድንበር አቋርጠው ጋምቤላ ውስጥ ወደሚገኘው ፓጋክ የስደተኞች ማዕከል እንደሚገቡ አስታወቀ፡፡
በኮሚሽኑ የኢትዮጵያ ቃል አቀባይ አቶ ክሱት ገብረ እግዚያብሄርን ጠቅሶ ‹‹አናዶሉ ኤጀንሲ›› ትናንት እንደዘገበው፣ ካለፈው መስከረም ወር መጀመሪያ አንስቶ 40 ሺህ የሚደርሱ ደቡብ ሱዳናውያን ስደተኞች ወደ ኢትዮጵያ የገቡ ሲሆን፣ ከእነዚህም መካከል 86 በመቶ ያህሉ ሴቶችና ህጻናት ናቸው፡፡ ከስደተኞቹ ጋር በተያያዘ ከፍተኛ ፈተና የሆነው የምግብ እጥረት እንደሆነ የጠቆመው ዘገባው፤ ወደ ኢትዮጵያ ከገቡት ደቡብ ሱዳናውያን ህጻናት መካከል 4 ሺህ 929 ያህሉ የምግብ እጥረት ተጠቂ መሆናቸውንም አክሎ ገልጧል፡፡
ኮሚሽኑ ከሳምንት በፊት ያወጣው መረጃ እንደሚያመለክተው፤ እስካለፈው ህዳር አንድ ቀን ድረስ በጋምቤላና በአሶሳ የሚገኙ ደቡብ ሱዳናውያን ስደተኞችና ጥገኝነት ጠያቂዎች ቁጥር 322 ሺህ 452 ደርሷል፡፡

Read 2509 times