Monday, 05 December 2016 09:04

አቶ ገብሩ አስራት ስለ ኢህአዴግ ግምገማዎች፣ ተሃድሶና ተቃዋሚዎች

Written by  አለማየሁ አንበሴ
Rate this item
(6 votes)

• ሙሰኞች አሉብን ብለዋል፤ እስካሁን ግን አንድም በሙስና የተከሰሰ አላየንም
        • ሚሊየነሮቹ እንዴት ነው “ሀብታችሁ ከየት መጣ?” ተብለው የሚጠየቁት?
        • በሃቅ ላይ የተመሰረተ ግምገማ ይኖራል የሚል እምነት የለኝም
        • ‹‹ኢትዮጵያዊነት›› በሚለው ዙሪያ መሰባሰብ አስቸጋሪ እየሆነ ነው

        በወቅቱ የኢህአዴግ ግምገማዎች፣ በተሃድሶና በተቃዋሚ ፓርቲዎች እንቅስቃሴ ዙሪያ ቀድሞ
የህውሓት/ኢህአዴግ አንጋፋ ታጋይና አመራር ከነበሩት አሁን የተቃዋሚው አረና ፓርቲ
አባል ከሆኑት አቶ ገብሩ አሥራት ጋር የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ አለማየሁ አንበሴ ተከታዩን
ቃለምልልስ አድርጓል፡፡

      በፌደራል መንግስት የካቢኔ ለውጥ መደረጉና ምሁራን በካቢኔው መካተታቸው ለህዝቡ ጥያቄ ምላሽ የመስጠት አካል እንደሆነ መንግስት ይገልጻል። በዚህ ጉዳይ ላይ የእርስዎ አስተያየት ምንድን ነው?
በኔ አስተያየት ይሄ ለውጥ እንዴት መጣ? ለምንስ ተደረገ? የሚለውን ማወቁ ተገቢ ይመስለኛል፡፡ የኢትዮጵያ ህዝብ ለረጅም ጊዜያት የሚጠይቃቸው መሰረታዊ ጉዳዮች አሉ፡፡ “በስርአቱ ውስጥ በከፍተኛ ደረጃ ሙስና ተንሰራፍቷል፤ ነፃነታችን መብታችን ተገድቧል፤ ፍትህ አጥተናል፣ ንብረታችን እየተዘረፈ ነው” የሚሉ ጥያቄዎች ሲነሱ ቆይተዋል። የእነዚህ ጥያቄዎች ምንጭ ደግሞ ስርአቱ ነው፡፡ እነሱም ይሄን አምነው ተቀብለዋል፡፡ ይሄ ነገር እያየለ ሲመጣ በአማራ፣ በኦሮሚያ፣ በደቡብና በተወሰነ መልኩ በትግራይ---ጠንካራ የህዝብ ተቃውሞና እንቅስቃሴዎች ታይተዋል፡፡ በዚህ ሂደት ብዙ ህይወት ጠፍቷል፤ ብዙ ንብረት ወድሟል፡፡ እነዚህን የህዝብ ጥያቄዎች ለማስተንፈስ መጀመሪያ ላይ “የኛ የውስጥ ችግር ነው” ብለው ተናግረዋል፡፡ በመሰረቱ ግን የአፈፃፀም ችግር ስለሆነ በአፈፃፀም እንፈታለን የሚል እንጂ ህዝቡ የሚያነሳቸውን ጥያቄዎች በአግባቡ ተገንዝበው ለመፍታት ዝግጁ የነበሩ አይመስለኝም፡፡
እንዲህ አይነት ቀውሶች ሲከሰቱ ደግሞ ችግሩን በሁለት አይነት መንገድ ማስታገስ ይቻላል፡፡ አንደኛው የበለጠ ማፈን ነው፡፡ ሁለተኛው መሰረታዊ ተሃድሶዎች ማድረግ ነው፡፡ ኢህአዴግ ደግሞ ይሄን መሰረታዊ ተሃድሶ ለማድረግ ዝግጁ አይመስልም። ስለዚህ የካቢኔ ሹም ሽር በማድረግና የጊዜያዊ አስቸኳይ አዋጅ በማወጅ ነው ችግሩን ለመፍታት እየሞከረ ያለው፡፡ እነዚህ ህዝቡ ከሚያነሳቸው ጥያቄዎች አንፃር የሚመጥኑ ምላሾች አይደሉም፡፡ ጥያቄዎቹ መሰረታዊ የፖሊሲ ለውጦችን ጭምር ነው የሚያመላክቱት፡፡ እነሱ ደግሞ በራሳቸው ማዕቀፍ ውስጥ ሆነው ነው ለውጥ የሚሉት፡፡ ያም ቢሆን የተሟላ አይደለም፡፡ ለምሳሌ ሙስናና ሙሰኞች አሉብን ብለዋል፤ እስካሁን ግን አንድም በሙስና የተከሰሰ ባለስልጣን አላየንም፡፡ የባለስልጣናት ብወዛ ነው የተደረገው እንጂ ግለሰብ ባለስልጣናት በህግ ሲጠየቁ አላየንም፡፡ ጥልቅ ተሃድሶ የሚባለው እነዚህን ካልመለሰ ትርጉሙ ግልፅ አይሆንም፡፡
እስኪ በትጥቅ ትግሉ ወቅት የነበረውን ግምገማና ዛሬ ከ25 ዓመት በኋላ በኢህአዴግ ውስጥ የሚደረገውን ግምገማ ያነፃፅሩልን?
ማወቅ ያለብን ኢህአዴግ ያኔ ሀብት አልነበረውም፡፡ ሰዎቹም ሀብት አልነበራቸውም። ሁሉም በጋራ፣ በራሽን ነበር የሚኖረው፡፡ ስለዚህ በዚያን ጊዜ በሚደረጉ ግምገማዎች ማንኛውንም ነገር አንስቶ ለመወያየትም ሆነ ለመተቸት ምንም ፍርሃትና ተግዳሮት አልነበረም፡፡ ምክንያቱም ሁሉም ተመሳሳይ አላማና ደረጃ ነበረው፡፡ ሁሉም ለመስዋዕትነት የተዘጋጀ ነበር፡፡ ግምገማዎች፣ ሂሶችና ግለ ሂሶችም በመሰረታዊ ጉዳዮች ላይ ያተኮሩ ነበሩ። የደከመውን ድክመቱን በግልፅ ለመንገር ምንም ፍርሃት አልነበረም፡፡ አሁን ደግሞ እንደምናየው 25 ዓመት ሞልቶታል፡፡ ድርጅቱ አሁን በሁለት የተከፈለ ነው፡፡ በአንዱ ረድፍ ሚሊዬነሮች የሆኑ አባላት የተሰባሰቡበት፣ ብዙ ቤትና መሬት፣ ሃብትና ንብረት ከነቤተሰቦቻቸው ያካበቱ ያሉበት ነው፡፡ በሁለተኛው ረድፍ ደግሞ ምንም የሌላቸው፣ በጣም የተቸገሩ የከፋቸው የሚገኙበት ነው፡፡ ከዚህ ተነስቼ ግምገማውን ሳስብ፣”እንዴት ነው እነዚህ ሁለት የተራራቀ የኑሮ መሰረት ያላቸው ሰዎች በአንድ ክፍል ውስጥ ተቀምጠው የሚገማገሙት?” የሚል ጥያቄ ይፈጥርብኛል፡፡ ሚሊየነሮቹ እንዴት ነው የሚነሱት? እንዴት ነው “ሀብታችሁ ከየት መጣ?” ተብለው የሚጠየቁት? ቢጠየቁስ ምን መልስ አላቸው? ስለዚህ ይሄ ግምገማና ሂስ የሚሉት የታችኛውን የበለጠ ለመርገጥ ካልሆነ በስተቀር ዋናዎቹ ላይ ለውጥ ያመጣል ብዬ አላምንም፡፡ ምክንያቱም ዋናውን ጥያቄ እናንሳ ከተባለ፣ ድርጅቱ የሙስና ችግር አለብኝ ብሏል፡፡ ስለዚህ እነዚያን ሰዎች “ይሄን ሃብት ከየት አመጣችሁት?” ብሎ መጠየቅ የግድ ነው፡፡ ነገር ግን ስልጣኑ የተያዘው አስቀድሜ እንዳልኩት ምንም በሌላቸውና በተቃራኒው በሃብት በበለፀጉ አባላት ስለሆነ፣ በትጥቅ ትግሉ እንደነበረው በሃቅ ላይ የተመሰረተ ግምገማ ይኖራል የሚል እምነት የለኝም፡፡ ታችኛውን የመምታት ውጤት ሊኖረው ይችላል እንጂ የላይኞቹን የሚነካ አይሆንም፡፡ ጎጠኝነት፣ በኔትወርክ መተሳሰር፣ ሙስና----የመሳሰሉት ዝም ብለው ይወራሉ እንጂ እርምጃ አይወሰድባቸውም፡፡  
መንግስት ግን “ጥልቅ ተሃድሶ” ለማድረግ ቁርጠኛ ነኝ ብሏል፡፡ የህዝብ ጥያቄዎችም ከወትሮው በተለየ የማያወላዱ ከመሆናቸው አንጻር እውነተኛ ግምገማ ማድረግ ይኖርበታል፡፡ አይመስልዎትም?
እውነተኛ ግምገማ ከተደረገና ህዝብ የሚያነሳቸው ጥያቄዎች ይመለሱ ከተባለ ሰለባ የሚሆነው የላይኛው አመራር ነው የሚል ስጋት ስለሚኖር ነው በሃቅ ላይ የተመሰረተ ግምገማ  አይደረግም የምለው፡፡ ሙስና፣ በኔትዎርክ መተሳሰር፣ ስልጣንን እንደ ርስት ይዞ መበልፀግ ---የሚመለከተው የታችኛውን ጀማሪ ባለስልጣን ሳይሆን የላይኛውን ነው፡፡ ታዲያ እንዴት ነው ይሄን ሊያነቃንቅ የሚችልን ነገር የሚነኩት?
እርስዎ ስልጣን ላይ በነበሩበት ወቅት የሚደረጉ ግምገማዎች ትኩረታቸው ምን ላይ ነበር?
የስራ አፈፃፀም ነው ወይስ የፖለቲካ አስተሳሰብ ጉዳይ ነው? በዋነኛነት ሲካሄድ የነበረው የስራ አፈፃፀም ውጤታማነት ላይ ነው፡፡ በተለይ በጦርነቱ ወቅት ጦርነቱ በአግባቡ ስለመካሄዱ፣ የኢኮኖሚ ጉዳይን በብቃት መምራትን በተመለከተ ከፍተኛና ጠንካራ ግምገማ በየእለቱ ይካሄድ ነበር፡፡ በትጥቅ ትግሉ ዘመን፣በድርጅቱ ጉባኤዎች ወቅት የርዕዮተ አለም አስተሳሰብ ግምገማ በግለሰቦች ላይ ይካሄድ ነበር፡፡ ግምገማዎች ግን በወቅቱ ጠንካራ ናቸው የሚባሉትም ሆነ የጥንካሬያቸው ምንጭ በየእለቱ በመደረጋቸውና ትንንሽ ክፍተቶች ባለመታለፋቸው ነበር፡፡
በአሁኑ ወቅት ኢህአዴግ ያንን ጠንካራ የግምገማ ባህሉን አጥቷል ብለው ያስባሉ?
ያኔ ሊያስፈፅመው የሚፈልገው የፖለቲካ አስተሣሠብ፣ ርዕዮተ አለም እንዲሁም አሠራር ነበረው፡፡ አሁን ይሄ ያለ አይመስለኝም፡፡ እኔ እንደውም ኢህአዴግ እንደ ፖለቲካ ድርጅት አለ ብዬ አላምንም፡፡ ስልጣንን ተቆጣጥሮ የማስቀጠል ጉዳይ ካልሆነ በስተቀር የርዕዮተ አለምና የፖለቲካ አቅጣጫ ጉዳይን በተመለከተ፣ በተለይ ቀድሞ ከተነሳለት አላማ አንፃር፣ አሁን ያለ አይመስለኝም። በዚህ የተነሳ ግምገማዎችም ጠንካራ ሊሆኑ አይችሉም። “ብገመገምም ምንም የሚደርስብኝ ነገር የለም” የሚል ሃሳብ ሊኖር ይችላል፡፡ ይሄን የምለው በየአመቱ በሚደረገው ግምገማ ለውጥ አለመምጣቱን በማየት ነው፡፡ ድሮ ሂስ ከተደረገ ውጤቱ ወዲያውኑ ነው የሚታየው፡፡ ያኔ ግምገማው በሚገባ አገልግሏል፡፡
ታዲያ ኢህአዴግ ወይም መንግስት ትርጉም ያለው ለውጥ/ውጤት ለማምጣት ምን ማድረግ አለበት ይላሉ?
እኔ ጠቅላላ የሃገሪቱን ሁኔታ ነው መመልከት የምፈልገው፡፡ ኢህአዴግ ብቸኛ የሃገሪቱ ገዥ ሆኖ ለመቀጠል ነው የፈለገው፡፡ አውራ ፓርቲ በመሆን። አንድ ፓርቲ፣ ብዝሃነት ባለበት ሃገር ውስጥ ለ40 እና 50 አመት ለመግዛት ሲሞክር ችግር ፈጣሪ እንጂ ችግር ፈቺ ሊሆን አይችልም፡፡ የተለየ ርዕዮተ አለም ያላቸው ሃይሎች በነፃነት የሚደራጁበት ሁኔታ መፈጠር አለበት። ነፃነቱ ሁሉ ክፍት መሆን አለበት። “አንድ ለአምስት”፣ “ኮሚኒቲ ፖሊስ”፣ “ጥቃቅንና አነስተኛ” በሚል የተያዘው ህብረተሰብ ነፃ እንዲሆን ማድረግ ያስፈልጋል፡፡ ነፃ ሚዲያ፣ ነፃ የፖለቲካ ፓርቲዎች፣ ነፃ የሲቪክ ማህበራት መኖር አለባቸው። የፖለቲካ ድርጅቶችን የሚገድሉ አዋጆች በሙሉ እንደገና ታይተው መሻሻል ወይም መሰረዝ ይኖርባቸዋል፡፡ ሁሉም ባለድርሻዎች የሚሳተፉበት ሰፊ የፖለቲካ ምህዳር መፈጠርና ለዚህም ቁርጠኛ መሆን ያስፈልጋል፡፡ ከዚህ ባነሰ የሚደረግ እንቅስቃሴ አርኪ አይሆንም፡፡ መሠረታዊ የዲሞክራሲ ለውጦች መምጣት አለባቸው፡፡ “ችግራችን የአፈፃፀም፣ የአሠራር ነው” የሚለው ብቻውን ወደ መፍትሄው አያደርስም፡፡ እውነተኛውን የችግሩን ባህሪና ምንጭ መመርመር ያሻል፡፡
ተቃዋሚዎች አሁን ሃገሪቱ ለገባችበት ችግር ሚና አላቸው ብለው ያስባሉ?
እዚህ ላይ ሁለት ነገሮችን ማጥራት አስፈላጊ ይመስለኛል፡፡ አንዱ ገዥው ፓርቲና ተቃዋሚዎችን በእኩል አይን አይቶ፣የመተቸት ነገር ነው፡፡ እኔ በዚህ አልስማማም፡፡ ኢህአዴግ በዚህች ሃገር ተቃዋሚ እንዳይኖር እያደረገ ነው፡፡ ከራሱ የተለየ ሃሳብ፣ አቋምና አቅጣጫ ያለው ግለሰብ እንዲኖር አይፈልግም፡፡ ጠላት ብሎ ነው የሚፈርጀው። ተቃዋሚዎች በዚህ አመለካከት ብዙ በደል ነው የደረሰባቸው፡፡ በዚህ ሁኔታ ውስጥ እያሉ “ተቃዋሚዎች ጠንክረው አልወጡም” በሚል መተቸት ተገቢ አይመስለኝም፡፡ ብዙ ፓርቲዎች አባሎቻቸው “ሽብርተኛ” እየተባሉ እየታሰሩባቸው ነው፡፡ በዚህ ሁኔታ ተቃዋሚዎችን ወይም ተበዳዮችን መልሶ መውቀስ ትክክል አይደለም፡፡  
ይህ ማለት ግን ተቃዋሚዎች ጋ ችግር የለም ማለት አይደለም፡፡ በተለይ ምሁራኑ ዘንድ ችግር አለ፡፡ ተቃዋሚዎች በተጠናከረ ሃሳብ ዙሪያ የመሰባሰብ ችግር አለባቸው፡፡ የሃሳብ ድህነትም ያለባቸው ይመስለኛል። በትንሽ ነገር መግባባት ሳይችሉ ተለያይተው ይበታተናሉ። ከመተባበር ይልቅ ልዩነትን እንደ ዋነኛ መስመር አድርገው የሚመለከቱ የፖለቲካ ፓርቲዎች ብዙ ናቸው፡፡ ከዚህ አዙሪት አልወጣንም፡፡ በሃገሪቱ መሠረታዊ ጉዳዮች ላይ መግባባት የለም፡፡ እንደውም አሁን አገር አቀፍነት ራዕዩም የጠፋ ይመስላል፡፡ ሁሉም የራሱን ክልልና ብሄር አስቀድሞ የመንቀሳቀስ ዝንባሌ እየተስተዋለ ነው።  ሁሉም ለራሱ ቅድሚያ ከሰጠ የጋራ ነገር አይገኝም፡፡ ‹‹ኢትዮጵያዊነት›› በሚለው ዙሪያ መሰባሰብ አስቸጋሪ እየሆነ ነው። ኢህአዴግ ሲያደርገው የነበረውን ነው እያደረጉ ያሉት፡፡ እንዲያም ሆኖ ዋናው ተበዳይና በዳይ እኩል መታየት የለባቸውም፡፡  
ሁሉም የተቃዋሚ ፓርቲ አመራሮች ሲጠየቁ እርስዎ የጠቀሱትን ችግሮች ነው የሚያነሱት። እዚህ ድረስ መግባባት ካለ ለምንድን ነው በጋራ የማትሰሩት? ለምሳሌ ኢዴፓ አንድ ጠንካራ ፓርቲ እመሰርታለሁ ብሎ እየተንቀሳቀሰ ነው ----?
እንግዲህ ኢዴፓ አንድ ጠንካራ ፓርቲ የሚመሰርት ከሆነ ለወደፊት የምናየው ይሆናል። እውነት እንደዚያ የሚያደርግ ከሆነ አስደሳች ነው።  ዋናው ግን በእውነት ዙሪያ ነው መሰባሰብ ያለብን፤ ዋናው ጉዳይ በሀሳቦች ዙሪያ መግባባት ነው፡፡ ሰጥቶ መቀበል የሚለውን መርህ ነው መተግበር ያለብን፡፡ ኢትዮጵያ ከዚህ በኋላ በቀድሞ ሃሳብ መራመድ የምትችል አይመስለኝም፡፡ ላቅ ወዳለ ሀሳብ የሚያመራ ነገር መነጋገር አለብን፡፡ በሰብአዊ መብቶች፣ በዲሞክራሲ ዙሪያ መነጋገር ይቻላል፤ ግን ከዚያም ባሻገር ያሉ አብሮ የመስራትና የመደራጀት ጉዳዮች ላቅ ያለ ሀሳብ የሚፈልጉ ናቸው፡፡ ብዝሃነት ባለበት ሀገር እንዴት ነው አንድ አገር አቀፍ ፓርቲ ወደፊት መራመድ ያለበት የሚለውን በጥንቃቄ ማየት ያስፈልጋል፡፡ ዋናው በሀሳብ ዙሪያ መግባባት ነው፡፡ ይሄ ነው ቆይቶ ወደ ድርጅትነት ሊቀየር የሚችለው፡፡ አዳዲስ ሃሳቦች መምጣት አለባቸው። በአሁኑ ወቅት ሁሉም አንድ የመሆን ፍላጎት አለው። ዋናው ግን አዲስ አስተሳሰብ ማምጣት ላይ ነው።
 አሁን ባለው ተጨባጭ ሁኔታ ጠንካራ ተቃዋሚ የመፍጠር ውጥን የሚሳካ ይመስልዎታል?
አንዳንድ ፅንፍ የሆኑ አስደንጋጭ ነገሮች ይታየኛል። ኢህአዴግን ተክተን እንመራለን የሚሉ ፖለቲከኞች የሚያነሷቸውና የሚያንፀባርቋቸው ነገሮች ያስፈሩኛል። ምክንያቱም በዘር ላይ የተመሰረቱ የፅንፍ ፖለቲከኞች እያየሉ የሄዱበትን ሁኔታ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ እያየን ነው፡፡ ህዝብን በብሄር እያናቆሩ እንደውም በከፋ ደረጃ ዘርን መሰረት ያደረገ እንቅስቃሴ እያደረጉ ነው፡፡ ዘርን መሰረት ያደረገ እንቅስቃሴ ጥፋት እንጂ ምንም መፍትሄ አያመጣም፡፡
አሁን በሀገራችን ላይ ያንዣበበው የፖለቲካ ስጋት ይሄ ነው፡፡ ኢህአዴግን ስንተችበት የነበረው አንዱ ከአንዱ የማጋጨት ተግባር፣በፅንፈኛ ተቃዋሚዎችም ዘንድ እየታየ ነው፡፡ ይሄ በጣም መጥፎና አስፈሪ ነው፡፡ ተቃዋሚዎች ከኢህአዴግ ተሽለው ካልተገኙ በስተቀር ይሄ የጥላቻና የስሜት ሩጫ አደጋ አለው፡፡
እኔ እንደ ታጋይና እንደ ፖለቲካ ፓርቲ አባል ተስፋ አልቆርጥም፡፡ ህዝብ የሚያደርገው እንቅስቃሴ ተስፋ አለው፡፡ እንቅስቃሴው ዝም ብሎ የመጣ አይደለም። አሁን የሚያስፈልገው ከኢህአዴግ በላይ ሀሳብ አምጥቶ ልቆ የሚሄድ እንጂ በኢህአዴግ ቁመና የሚሰፋ ወይም ከዚያ በታች ሆኖ በዘር የሚሰፋ ከሆነ ለውጥ አያመጣም። እኔ ተስፋ አለኝ፤ በህዝቡ ተገደውም ቢሆን ወደ መሰረታዊ ጉዳይ ይመጣሉ፡፡ ግን ብዙ ጥረት ማድረግ ያስፈልጋል፡፡

Read 6380 times