Monday, 12 December 2016 11:56

ተቃዋሚዎች፤ ሳንመረጥ ፓርላማ አንገባም አሉ

Written by 
Rate this item
(14 votes)

   መንግስት ተቃዋሚ ፓርቲዎች በዓመት ሦስት ጊዜ ፓርላማ ገብተው በውይይት እንዲሳተፉ ለማድረግ ማኑዋል እየተዘጋጀ መሆኑን የገለፀ ሲሆን ተቃዋሚዎች በበኩላቸው፣ ሳይወከሉ በፓርላማ ውይይት ህገ መንግስታዊ አይደለም ሲሉ ተችተዋል። ተቃዋሚዎች ለምን አላማ ከመንግስት ጋር በዚህ መንገድ እንዲወያዩ እንደተፈለገ አይገባንም ያሉት የአረና ም/ሊቀመንበር አቶ ጎይቶም ፀጋዬ፤ ውይይቱ በፓርላማ መደረጉ ምናልባት ኢህአዴግ ብቻውን ተቆጣጥሮታል የሚለውን ሃሜት ለማስቀረት ካልሆነ በቀር ሌላ ፋይዳ አይኖረውም ብለዋል። “የተቃዋሚዎች የመወሰን ሚና ጨርሶ በሌለበት ሁኔታ የሚደረጉ ውይይቶች ጥቅማቸው እምብዛም ነው” ይላሉ አቶ ጎይቶም፡፡
የኦሮሞ ፌደራሊስት ኮንግረስ (ኦፌኮ) ም/ሊቀመንበር አቶ ሙላቱ ገመቹ በበኩላቸው፤ ተቃዋሚዎች የህዝብ ውክልና ሳይኖራቸው በፓርላማ መገኘታቸው በምን አግባብ ነው? ሲሉ ይጠይቃሉ፡፡ “ፓርላማው ላይ መገኘት የሚቻለው በህዝብ ሲወከሉ ብቻ ነው” ያሉት አቶ ሙላቱ፤ ተቃዋሚዎች የመወሰን ሚና ሳይኖራቸው የሚያደርጉት ውይይት ምንም ፋይዳ አይኖረውም ብለዋል፡፡
“መንግስት ከተቃዋሚዎች ምክር የሚፈልግ ከሆነ፣ በፓርላማው መሆን የለበትም” ያሉት አቶ ሙላቱ፤ ሌሎች ልዩ መድረኮች መዘጋጀት አለባቸው ይላሉ፡፡ ተግባራዊ ይደረጋል ብለው እንደማያምኑ የተናገሩት ም/ሊቀመንበሩ፤ ከዚህ በፊት መሰል የውይይት መድረኮች ይዘጋጃሉ ተብሎ መቅረቱን ያስታውሳሉ፡፡ አሁን መንግስት ማድረግ ያለበት ለህዝብ ጥያቄ መልስ መስጠት ነው ብለዋል - አቶ ሙላቱ፡፡
የፓርቲዎች የጋራ ምክር ቤት አባል የሆነው የኢትዮጵያ ራዕይ ፓርቲ (ኢራፓ) ፕሬዚዳንት አቶ ተሻለ ሰብሮ በበኩላቸው፤ “መንግስት ከተቃዋሚዎች ጋር ይወያያል የተባለው ከ2002 ምርጫ ማግስት ጀምሮ ነው፤ ሆኖም ተፈፅሞ አያውቅም፤ የአሁኑም የፓርላማው ውይይት የተስፋ ቃል ነው” ይላሉ፡፡
የመንግስትና የተቃዋሚዎች ውይይት እስካሁን ተግባራዊ ሲሆን አለማየታቸውን የገለፁት አቶ ተሻለ፤ “በእውን የሚደረግ ከሆነም፣ “በምን አግባብ ይከናወናል? መቼ ነው የሚጀምረው? እንዴት ነው ተቃዋሚዎች የሚሳተፉት? የሚሉትን ጥያቄዎችን መመለስ አለበት” ብለዋል፡፡ “የውይይት መድረኩ እውን ይሆናል ብለን እንድናምንና ምልክቶች መታየት አለባቸው ብለዋል” - ሲሉ አክለዋል፡፡
“የተቃዋሚዎች በፓርላማ መሳተፍ ምንን መርህ አድርጎ ነው? ህገ መንግስታዊ ነው? በአዋጅ የሚያሳትፍ ነው? የፖሊሲ አቅጣጫ አለው?” ሲሉ የጠየቁት የኢዴፓ ፕሬዚዳንት ዶ/ር ጫኔ ከበደ በበኩላቸው፤ “ተቃዋሚዎች በምን መንገድ፣ የትኛውን የህብረተሰብ ክፍል ወክለው  ነው በፓርላማ ሊሣተፉ የሚችሉት” ብለዋል፡፡
‹‹መንግስት ቅድሚያ መስጠት ያለበት ለህዝቡ ቀጥተኛ ጥያቄዎች መልስ መስጠት ላይ ነው ያሉት ዶ/ር ጫኔ፤ በአሁኑ ሰዓት ህዝብ ለተቃዋሚዎችም ለመንግስትም ፍላጎት ባላሳየበት ሁኔታ ተቃዋሚዎች በምን አግባብ ነው ፓርላማ ገብተው ሊነጋገሩ የሚችሉት ሲሉ ጠይቀዋል፡፡  ኢዴፓ ተቃዋሚዎችን ፓርላማ አስገብቶ በመወያየት ብቻ ችግሮች ይቀረፋሉ የሚል እምነት  እንደሌለው የጠቆሙት ፕሬዚዳንቱ፤ ፓርቲያቸው የፖሊሲ አቅጣጫዎች እንዲሻሻሉና ህግ ሙሉ ለሙሉ እንዲከበር እንደሚፈልግ ገልፀዋል፡፡
በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የፖለቲካ ሳይንስና የፌደራሊዝም መምህር አቶ ናሁሠናይ በላይ የፓርላማውን ውይይት በተመለከተ ተጠይቀው ሲመልሱ፤ በፓርላማው ለየት ያለ ሃሳብ እንዲንፀባረቅ መፈለጉ መልካምና ጠቃሚ መሆኑን ገልፀው፤ የተቃዋሚዎች ሚና የሚለካው ከገዥው ፓርቲ ጋር በመገናኘታቸው ብቻ አይደለም፤ ገዥው ፓርቲ በተቃዋሚዎች ሚና የሚያምን ከሆነ፣ እንደ ፖለቲካ ፓርቲ የሚንቀሣቀሱበትን የመጫወቻ ሜዳ ምቹ ማድረግ አለበት ብለዋል፡፡
“ኢህአዴግ የፖለቲካ ፓርቲዎች ገንቢ ሚና አላቸው ብሎ ማመን መጀመሩን ለማሳየት ከፈለገ፣ በፖለቲካ እንቅስቃሴያቸው ላይ እንቅፋት ከመሆን መቆጠብ ይኖርበታል፤ በአመት ሶስት ጊዜ ተቃዋሚዎችን በፓርላማ አሳትፋለሁ ማለት ብቻውን በቂ አይደለም፤ የተለያዩ መድረኮች መዘጋጀት አለባቸው” ያሉት ምሁሩ፤ “አሁን የሃገሪቱ ሁኔታ እንደ ቀድሞ የኔ ሃሳብ ብቻ  ይሰማ የሚባልበት ባለመሆኑ፣ ኢህአዴግ ከልቡ ተምሮ ከሆነ፣ ይህን ውጥኑን ተግባራዊ ሊያደርግ ይችላል” ሲሉ እምነታቸውን ገልፀዋል፡፡

Read 7547 times