Sunday, 18 December 2016 00:00

የአውሮፓ ፓርላማ የዶ/ር መረራ ክስ እንዲገለፅለት ጠየቀ

Written by  አለማየሁ አንበሴ
Rate this item
(21 votes)

• ለፕሬዚዳንት ዶ/ር ሙላቱ ደብዳቤ ፅፏል
• ዶ/ር መረራ ፍ/ቤት ቀርበው የ28 ቀን ቀጠሮ ተጠይቆባቸዋል

በዶ/ር መረራ ጉዲና እስር ጉዳይ የኢትዮጵያ መንግስት ማብራሪያ እንዲሰጠው የአውሮፓ ህብረት ፓርላማ ለፕሬዚዳንት ዶ/ር ሙላቱ ተሾመ ግልፅ ደብዳቤ ፃፈ፡፡
ዶ/ር መረራ ሰሞኑን ከጠበቆቻቸው ጋር የተገናኙ ሲሆን ፍ/ቤት ቀርበው ፖለሊስ የ28 ቀናት የምርመራ ቀነ ቀጠሮ እንደጠየቀባቸው ተጠቁሟል፡፡
የአውሮፓ ህብረት ፓርላማ ፕሬዚዳንት ማርቲን ቹሎዝ ትናንት ለፕሬዚዳንት ዶ/ር ሙላቱ ተሾመ በፃፉት ደብዳቤ፤ በኦፌኮ ሊቀመንበር ዶ/ር መረራ ጉዲና ድንገተኛ እስር መደናገጣቸውን ጠቁመው የቀረበባቸው ክስ በይፋ እንዲገለፅላቸው ጠይቀዋል፡፡ ዶ/ር መረራ በህብረቱ ጋባዥነት ብራስልስ ተገኝተው ከህብረቱ የፓርላማ አባላት ጋር መወያየታቸውን የጠቀሱት ማርቲን፤ “የአውሮፓ ፓርላማ የዲሞክራሲ ማራመጃና የተለያዩ ድምፆች የሚሰሙበት መሆኑን ላስገነዝብ እወዳለሁ” ብለዋል በደብዳቤያቸው፡፡
በብራስልስ የኢትዮጵያ አምባሳደር በጉዳዩ ላይ ለቀረበላቸው የማብራሪያ ጥያቄ፤ ዶ/ር መረራ የታሰሩት የኢትዮጵያ መንግስት በአሸባሪነት ከፈረጃቸው ድርጅቶች አመራሮች ጋር በመገናኘታቸው መሆኑን መረዳታቸውን የጠቀሱት የፓርላማው ፕሬዚዳንት የህብረቱ ፓርላማ የመንግስትም ሆነ የተቃዋሚ አመራሮች የሚጋበዙበት መሆኑን አስረድተዋል፡፡
በሌላ በኩል በእስር ላይ የሚገኙት አንጋፋው ፖለቲከኛ ዶ/ር መረራ ጉዲና፣ ፍ/ቤት ቀርበው ፖሊስ የ28 ቀናት ተጨማሪ የምርመራ ጊዜ ቀጠሮ የጠየቀባቸው ሲሆን ከተደጋጋሚ ሙከራዎች በኋላ ሰሞኑን ከጠበቆቻቸው ጋር ተገናኝተው መነጋገራቸውም ታውቋል፡፡
ባለፈው ህዳር 21 የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁን በመጣስ፣ ከሽብርተኛ ድርጅት ጋር ግንኙነት ፈጥረዋል በሚል ተጠርጥረው በቁጥጥር ስር የዋሉት አንጋፋው ፖለቲከኛ፤ ከተያዙበት ጊዜ አንስቶ ላለፉት ሁለት ሳምንታት ከጠበቆቻቸው ጋር መገናኘት አልቻሉም ነበር ተብሏል፡፡ የህግ አማካሪዎቻቸው ዶ/ር ያዕቆብ ኃ/ማርያምና አቶ ወንድሙ ኢብሳ ባለፈው ረቡዕ ከጠዋቱ 3 ሰዓት ዶ/ር መረራ በታሰሩበት ማዕከላዊ ተገናኝተው እንደተነጋገሩ ለአዲስ አድማስ አስረድተዋል፡፡
ዶ/ር መረራም ፍ/ቤት መቅረባቸውንና ፖሊስ ተጨማሪ የ28 ቀን የምርመራ ጊዜ ቀጠሮ እንደጠየቀባቸው የተናገሩት ጠበቃቸው፤ የተጠረጠሩበት ጉዳይም “በቅርቡ ወደ አውሮፓ በመጓዝ ከሽብርተኛ ድርጅቶች ጋር መገናኘት” የሚል መሆኑን ገልፀው፣ የተለያዩ ምርመራዎች እየተደረጉባቸው እንደሆነም ማረጋገጣቸውን ገልፀዋል፡፡ ለ30 ደቂቃዎች ያህል ከዶ/ር መረራ ጋር ተነጋግረናል ያሉት ዶ/ር ያዕቆብ፤ ጤንነታቸው በመልካም ሁኔታ ላይ እንደሚገኝ፤ ነገር ግን ብቻቸውን እንደታሰሩና ምግብ በቀን አንድ ጊዜ እንደሚገባላቸው ለአዲስ አድማስ ገልፀዋል ታሪሳውን በመጥቀስ ነግሮኛል ብለዋል፡፡
ደንበኛቸውን ከሶስት ጊዜ ምልልስ በኋላ ለማግኘት እንደቻሉ የገለፁት ዶ/ር ያዕቆብ፤ “ደንበኛችንን እንዳናገኝ መደረጉ አግባብ አልነበረም” ሲሉ አማረዋል፡፡ “አንድ በህግ ቁጥጥር ስር የዋለ ሰው በተቻለ ፍጥነት ቤተሰቡን፣ የሃይማኖት አባቱንና የህግ አማካሪውን የማግኘት መብት እንዳለው የህገ መንግስቱ አንቀፅ 21 ይደነግጋል” ያሉት የህግ ባለሙያው፤ “ይህ አለመከበሩ አለማቀፍ የሰብአዊ መብት ስምምነቶችንም የሚጥስ ነው” ብለዋል። አክለውም ዶ/ር መረራ ብቻቸውን እንዲታሰሩ መደረጉን አጥብቀው እንደሚቃወሙ ገልፀው፤ “ህጉ የሚለው አንድ ሰው ብቻውን የሚታሰረው፣ ለሌሎች እስረኞች አደጋ የሚፈጥር ሲሆን ነው” ብለዋል፡፡

Read 6245 times