Saturday, 31 December 2016 11:16

የግብፅና የኢትዮጵያ መንግስት ሌላ የውዝግብ ምዕራፍ

Written by  አለማየሁ አንበሴ
Rate this item
(31 votes)

- “የኢትዮጵያ መንግስት ግብፅን ያለማስረጃ ከመወንጀል ይቆጠብ” - ግብፅ
- “የግብፅ መንግስትን ይፋ ምላሽ እየጠበቅን ነው” - ኢትዮጵያ

የግብፅ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የስራ ኃላፊ፤ የኢትዮጵያ መንግስት በማስረጃ ላይ ያልተመሰረተ ውንጀላ ከማቅረብ እንዲቆጠብ ያስጠነቀቁ ሲሆን የኢትዮጵያ መንግስት በበኩሉ፤ ‹‹ላቀረብኩት ጥያቄ አሁንም ቢሆን ይፋ ምላሽ እየጠበቅሁ ነው›› ብሏል።
የግብፅ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ ኃላፊ በመግለጫቸው፤ “የኢትዮጵያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዶ/ር ወርቅነህ ገበየሁ፣ ባለፈው ሰኞ ካይሮ የኦሮሞ ተቃዋሚ ኃይሎችን ትደግፋለች ማለታቸው የሁለቱን ሀገራት ወዳጃዊ ግንኙነት ይጎዳዋል” ብሏል፡፡
መቀመጫው በተባበሩት አረብ ኢምሬትስ ለሆነው “ዘ ሚድል ኢስት ሞኒተር” ጋዜጣ ማብራሪያ ሰጡ የተባሉ ስማቸው በይፋ ያልተገለፀ አንድ የግብፅ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ከፍተኛ የስራ ኃላፊ፤ “ሀገራቸው ተቃዋሚዎችን እንደምትደግፍና በሀገሪቱ የውስጥ ጉዳይ መግባቷን በተመለከተ የኢትዮጵያ መንግስት ማስረጃ እንደሌለው በመጠቆም፣ በግብፅ የሚገኙ ኢትዮጵያውያን ስደተኞችም በማናቸውም የፖለቲካ እንቅስቃሴ ላይ የተጣለባቸውን የህግ ገደብ አክብረው የሚንቀሳቀሱ መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡
“ግብፅ በኢትዮጵያ የውስጥ ጉዳይ የምትገባበት ምንም ምክንያት የላትም” ያሉት ባለስልጣኑ፤ በየጊዜው ሁለቱ ሀገራት በተለያዩ ጉዳዮች የሚወዛገቡ ቢሆንም ጠንካራ ታሪካዊ ግንኙነት እንዳላቸው ሊካድ አይገባም ብለዋል - የኢትዮጵያ መንግስት መረጃ ላይ ካልተመሠረተ ውንጀላ እንዲታቀብ በማስጠንቀቅ፡፡
ባለስልጣኑ ሰጡ በተባለው መግለጫ ዙሪያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃለ አቀባይ አቶ ተወልደ ሙሉጌታ በሰጡት ማብራሪያ፤ ኢትዮጵያን ለማተራመስ የሚሰሩ፤ ‹‹የሽብር ቡድኖችንና ፀረ-ሠላም ሃይሎችን አንዳንድ የግብፅ ተቋማት እንደሚደግፉ ከተለያዩ ማስረጃዎች ለማወቅ መቻሉን ጠቁመው፣ ከኢትዮጵያ ጋር በመልካም ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት ላይ የሚገኘው የግብፅ መንግስት ይፋዊ ማብራሪያ እንዲሰጥ መጠየቁንና እስካሁንም ይፋዊ ምላሽ አለመገኘቱን አስታውቀዋል፡፡
በሁለቱ ሃገራት መካከል ልዩነቶች ቢኖሩ እንኳ በውይይትና በድርድር ሊፈታ ይገባል የሚል ፅኑ አቋም የኢትዮጶያ መንግስት እንዳለው የጠቀሱት አቶ ተወልደ በአባይ ጉዳይ ግብፅ፣ ሱዳንና ኢትዮጵያ በመልካም የስምምነት ሂደት ላይ እንደሚገኙ አስረድተዋል፡፡
የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር፣ ሃገሪቱ የኢትዮጵያ ተቃዋሚዎችን እንደምትረዳ ለቀረበባት መረጃ ምላሽ እንዲሠጠው ላቀረበው ጥያቄ አሁንም የግብፅ መንግስት ይፋዊ ምላሽ እንደሚጠበቅ አስታውቀዋል፡፡

Read 8758 times