Wednesday, 25 January 2017 07:33

ማራኪ አንቀፅ

Written by 
Rate this item
(8 votes)

   ሊብራዎች ብልግና አይወዱም፡፡ ሰው ያፈቅራሉ፡፡ ብዙ ህዝብ ወደተሰበሰበበት መሄድ ግን አይፈቅዱም፡፡ እንደ ሰላም ምልክቷ ጨዋ እርግብ፣ የተጣላ ማስታረቅ ይወዳሉ፤ ክርክር ይሆናቸዋል፡፡ ጥሩ ባህሪ ያላቸው ናቸው እና አስደሳቾች ናቸው፡፡ አንዳንዴ ግን ለንቦጫቸውን የሚጥሉ አኩራፊዎችና ትዕዛዝ የማይቀበሉ ለጋሚዎች ይሆናሉ፡፡ በአንድ በኩል እጅግ በጣም ብልሆች ሲሆኑ በሌላ ጎናቸው ደግሞ እጅግ በጣም ገራገርና የዋሆች እንዲሁም ድልሎች ናቸው፡፡ አነብናቢዎች ቢሆኑም ጥ ሩ አ ድማጮችም ይሆናሉ፡፡ ግራ ተጋቡ እንዴ? ራሳቸውም በራሳቸው እስከሚገረሙ ድረስ ሊብራዎች ጠባያቸው ይዋዥቃል፡፡ ብዙ ሰው ሊብራዎች “ፍቅር ናቸው፤ ውበት ናቸው፣ ጣፋጭ ናቸው፣ ብርሃን ናቸው” ይላል፤ ጥሩ ነው። ግን በወርቅ የፍትህ ሚዛን እንደሚመሰሉም ማስታወስ ይጠቅማል፡፡ ሚዛኑ በቀላሉ ይዋዥቃል። ተስተካክሎ እንደቆመ ረግቶ ላይገኝ ይችላል፡፡ የሚዛን ሁሉ ተግባሩ ተስተካክሎ መቆም ነው፡፡ ተስተካክሎ ለመቆም ምን ይሆናል? ይዋዥቃል፡፡ አንዴ በዚህ፣ አንዴ በዚያ ተስተካክሎ እስከሚቆም ይዋዥቃል፡፡ ስለዚህ ሊብራን “ፍቅር፣ ውበት፣ ጣፋጭና ብርሃን” ሆኖ የሚያገኙት እድሜ ልክዎን ሳይሆን ለግማሹ ጊዜዎ ነው፡፡ በግማሹ አናዳጅ፣ ቁንጥንጥና ግራ የተጋባ ሆኖ ሊያገኙት ይችላሉ፡፡ የሊብራ ስሜት እንደሚዛን መዋዠቅ ጠባዩ ነው፡፡ ፍቅር ሰጠት ሲያደርጉት ግን ወዲውኑ ይስተካከላል፡፡ አካላዊ መልካቸውም እንደ ጠባያቸው ይስባል፡፡ ዲምፕል አላቸው፡፡ከዚያ
ይጀምሩ እና ቶሎ በግልጽ ወደማይታየው ውበታቸው ይግቡ፡፡ ዲምፕሉ በጉንጫቸው ላይ ካልታየ በእግራቸው ላይ መገኘቱ አይቀርም፡፡ ዲምፕል ሊብራ ባልሆኑ ሰዎች ላይም የሚገኘው የቬኑስ ተፅዕኖ ካረፈባቸው ነው፡፡ ዲምፕሉን ካገኙ በኋላ ፊታቸውን በአጠቃላይ
ይመልከቱ፣ አስደሳች ውበት ይታይዎታል፡፡ ሲቆጡ እንኳ ገራምነት ይነበብባቸዋል፡፡ ድምጻቸው ጣፋጭና ኮለል፣ እንደሞል ደወል ጥርት ያለ ነው፡፡ ሊብራዎች “ጠላሁህ!፣ ጥርስህን ላረግፍልህ ነው!” ብለው በጥሩ የድምጽ ቃና በግልጽ የሚናገሩ፣ በዓለም ላይ ልዩ የሆኑ ሰዎች ናቸው፡፡ ከንፈሮቻቸው ውቦችና ጉንጮቻቸውም እንደ ቸኮሌት የሚያጓጉ ናቸው፡፡ ሴቶቹም ወንዶቹም ቆንጆዎች ናቸው፡፡ ኮከባቸው ቬኑስ የውበት ተምሳሌት ናት፡፡ ሊብራ ሴቶች ሱሪ መልበስ ይወዳሉ፡፡ ወንዳ ወንድ ናቸው ማለቴ አይደለም፡፡ የተለየ ለዛ ያላቸው ልስልስና ወላንሳ ሴቶች ናቸው፡፡ ደም ግባታቸው ይማርካል፤ ፈገግታቸው ያቀልጣል፤ ሙሉ በሙሉ ካረፈብዎ ወከክ፣ ትርክክ ነው የሚሉት፡፡ ፀጉራቸው ከርል ነው፤ የታውረስ ተጽእኖ ካላረፈባቸው በስተቀር ወፍራሞች አይደሉም፡፡ ሌላው የሚስብዎ ነገር ደስ የሚል ሳቃቸው ነው፡፡ አንዴ ከሰሙት
አይረሳዎትም፡፡ አሁን ባለ ዲምፕልና ማራኪ ሆኖ መወለድ፣ ፍትሀዊና ተፈቃሪ መሆን፣ አስደሳችና በቀላሉም ተደሳች ሆኖ የመፈጠር ፀጋ መሆኑን ሳይረዱ አልቀሩም፡፡ ጨዋነት እና ብልህነት፣ ግርማ ሞገስ እና ሌሎችን የሚገነዘብ /አንደርስታንድ የሚያደርግ/ ኅሊናም የፈጣሪ ስጦታዎች መሆናቸውን ተገንዝበዋል፡፡ ሊብራ የወርቅ ሚዛኑ ሲስተካከልለት እነዚህን ሁሉ ይጣበሳል፡፡ ይህም ሰማያዊ መልዓከ ምድር ላይ የማግኘት ያህል የሚያስደስት ነገር ነው። ችግሩ ሚዛኑ ሲዋዥቅ ነው፤ ቢሆንም ፍቅር ሰጠት ሲያደርጉ ፈጥኖ ይስተካከልለታል፡፡
 
    (ከተርጓሚ አብርሃም ጎዝጉዜ “የፀሐይ ምልክቶች” የተሰኘ የአስትሮሎጂ መፅሃፍ ላይ የተቀነጨበ፡፡ ተርጓሚው የፕ/ር ፍቅሬ ቶሎሳን
   “The True Origin of Oromo and Amhara” የተሰኘ አነጋጋሪ መፅሐፍ “እውነተኛው የኦሮሞና
   የአማራ የዘር ምንጭ” በሚል የተረጎሙ ናቸው፡፡

Read 7889 times