Monday, 30 January 2017 00:00

ፓትርያርኩ: አወዛጋቢው የአዲስ አበባ አድባራት ሠራተኞች ዝውውር እንዲጣራ አዘዙ

Written by 
Rate this item
(12 votes)

ከደረጃ ዝቅ የተደረጉ፤ ከሥራና ደመወዝ የታገዱና የተሰናበቱ ይገኙበታል
የዋና ሥራ አስኪያጁ አካሔድ የፓትርያርኩን መመሪያ የጣሰ ነው፤ ተብሏል
    ከሚገባቸው በላይ የሰው ኃይል ክምችት በመያዝ እየተጨናነቁ በሚገኙት የአዲስ አበባ ገዳማትና አድባራት፣ የሚካሔደው የሓላፊዎችና የሠራተኞች ዝውውር እንዲሁም ከሥራ የማገድና የማሰናበት ርምጃ በአስቸኳይ እንዲጣራ፣ ፓትርያርክ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ አዘዙ፡፡
ፓትርያርኩ ትእዛዙን የሰጡት፣ በመ/ር ጎይትኦም ያይኑ ዋና ሥራ አስኪያጅነት የሚመራው የሀገረ ስብከቱ ጽ/ቤት፣ ከሕግና ሥነ ሥርዓት ውጭ የአስተዳደር በደል አድርሶብናል፤ የሚሉ የሃያ አመልካቾችን አቤቱታ፣ በአካልና በጽሑፍ ከተቀበሉ በኋላ በልዩ ጽ/ቤታቸው በኩል በጻፉት ደብዳቤ ነው፡፡
ከአስተዳዳሪነት ጀምሮ ባሉት የጽ/ቤት ሓላፊነቶች የሚሠሩት አቤቱታ አቅራቢዎቹ፦ ደመወዝ፣ አበልና የሥራ ደረጃን በሚቀንስ እንዲሁም፣ የተዛወሩበትን የሥራ መደብ፣ ደመወዝና አበል በማይጠቅስ ውሳኔ ተገቢ ያልሆነ ዝውውር ተፈጽሞብናል፤ ባልተጣራና ባልተወሰነ የሥራ ግድፈት ከሥራና ደመወዝ እንድንታገድና እንድንሰናበት በማድረግ በደል ደርሶብናል፤ በሚል ማመልከታቸውንና ፍትሐዊ ውሳኔ እንዲሰጣቸው መጠየቃቸውን ልዩ ጽ/ቤቱ በደብዳቤው ገልጿል፡፡
ሠራተኞቹ፣ ከአንዱ አጥቢያ ወደ ሌላው እንዲዛወሩ፤ ከሥራና ደመወዝ እንዲሰናበቱ የተደረገበት ማስረጃ ተገቢነት፣ ካቀረቡት አቤቱታና ከቤተ ክርስቲያኒቱ ሕግጋት አንፃር እየተገናዘበ በሀገረ ስብከቱ አስተዳደር ጉባኤ እንዲመረመር ፓትርያርኩ አዘዋል፤ አፈጻጸሙም፣ ሕጋዊውን አሠራር ያልተከተለ ኾኖ ሲገኝ፣ የሀገረ ስብከቱ አስተዳደር በምልዓተ ጉባኤ አስተካክሎና አርሞ አፋጣኝ ውሳኔ በመስጠት፣ ውጤቱ በአስቸኳይ እንዲገለጽላቸው በመመሪያቸው ማሳሰባቸውንም ልዩ ጽ/ቤቱ አስታውቋል፡፡
አቤቱታው፣ ባለፈው ኅዳር ለጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽ/ቤት ቀርቦ የታየና ሀገረ ስብከቱ በሕጉ መሠረት አስቸኳይ አስተዳደራዊ ውሳኔ እንዲሰጥ አስቀድሞ የታዘዘበት ከመሆኑም በላይ፤ ለሕዝብ ዕንባ ጠባቂ ተቋም፣ ለሰብአዊ መብቶች ኮሚሽንና ለፌዴራል ጉዳዮች ሚኒስቴርም ደርሶ በሚመለከተው አካል መፍትሔ እንዲያገኝ ሲጠየቅ መቆየቱ ተወስቷል፡፡
አቤት ባዮቹ፣ በተለይ ለሕዝብ ዕንባ ጠባቂ ተቋም በጻፉት ደብዳቤ፣ የሀ/ስብከቱ ዋና ሥራ አስኪያጅ፥ ከሕገ ወጥ ዝውውር በተጨማሪ፣ የሙስና ተግባራትን እንደሚፈጽሙና ያለምንም ጥፋት ከባድ ማስጠንቀቂያ የጻፉባቸውም ይህን በመቃወማቸውና የመብት ጥያቄ በማንሣታቸው እንደኾነ በቅሬታቸው ጠቅሰዋል፡፡
በሌላ በኩል፣ አቤቱታውን የሚያጣራ ስምንት አባላት ያሉት ቡድን ባለፈው ማክሰኞ በዋና ሥራ አስኪያጁ ተቋቁሞ ጉዳዩን የሚመለከት ሰነድ በማስቀረብ ሲያጠና መቆየቱን የጠቀሱ የሀገረ ስብከቱ ምንጮች፤ የማጣራቱ ውጤትም፣ ከትላንት በስቲያ በተካሔደውና ዋና ሥራ አስኪያጁን ጨምሮ 11 የዋና ክፍል ሓላፊዎች በተገኙበት የአስተዳደር ጉባኤ ታይቶ ውሳኔ ማግኘቱን ለአዲስ አድማስ ተናግረዋል፡፡
ምንጮቹ እንደተናገሩት፣ ከኻያዎቹ አቅራቢዎች መካከል፣ ሦስት የአድባራት ጸሐፊዎች፣ በዝውውሩ የተቀነሰባቸው ደመወዝ ካለ ባሉበት እንዲስተካከል፤ ታቦት ታቅፈው ሀገረ ስብከቱ ጽ/ቤት ድረስ ይዘው በመምጣት ከፍተኛ ድፍረትና የቀኖና ጥሰት ፈጽመዋል በሚል ከሥራና ደመወዝ በተሰናበቱ አንድ አለቃና ሦስት ሠራተኞች ላይ የተወሰደው የማሰናበት ውሳኔ ባለበት እንዲጸና፤ የተቀሩት 13 ሠራተኞችም፣ ይቅርታ እየጠየቁ በተገኘው ቦታ እንዲመደቡ መወሰኑን አስታውቀዋል፡፡
በበርካታ የሰነድ ማስረጃዎች የተደገፈውን አቤቱታ ማጣራት የሚገባው፣ 14 አባላት ያሉት የሀገረ ስብከቱ አስተዳደር ጉባኤ እንጂ፣ ዋና ሥራ አስኪያጁ በራሳቸው መርጠው ያቋቋሙት ቡድን አለመኾኑን የሚጠቅሱ ወገኖች በበኩላቸው፤ አካሔዱ፣ የፓትርያርኩን መመሪያ እንደሚፃረር፤ በጥቅማጥቅምና በአቅም ማነስ የተሠሩ የጽ/ቤቱን ስሕተቶች ለመሸፋፈን የተደረገ ሙከራ በመሆኑ እንደሚቃወሙት ገልጸዋል፡፡  
በሕገ ቤተ ክርስቲያን በሰፈረው የልዩ ሀገረ ስብከት ድንጋጌ መሠረት፣ በፓትርያርኩ የበላይ ሓላፊነት የሚመራው የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት፤ በእገሌ ሥራና በጀት እየተባሉ መዋቅርን፣ ዕውቀትን፣ ልምድንና በጀትን ማዕከል ባላደረጉ የዝውውር፣ ቅጥርና ሽግሽግ አሠራሮች ጋራ ተያይዘው በሚነሡ ውዝግቦች እየታወከ እንደሚገኝ ተጠቁሟል፡፡ ራሱን ችሎ ሊቀ ጳጳስ እንዲመደብለትና ሓላፊነትና ተጠያቂነት ያለበት ጠንካራ መዋቅርና አደረጃጀት እንዲዘረጋለት የተላለፉ ውሳኔዎች አፈጻጸምም መጓተቱን ምንጮች ጨምረው ገልጸዋል፡፡

Read 5172 times