Sunday, 12 February 2017 00:00

የእውር ድንብር አመራር፤አስደንጋጭ የሕዝብ ሐብት ብክነት

Written by  አልአዛር ኬ.
Rate this item
(3 votes)

መንግስታት ህልውናቸው የተመሠረተበትና የመንግስትነት ስራቸውን የሚያከናወኑበት ገንዘብ ከሰማይ አይወርድላቸውም፡፡ ለዚህ የሚሆናቸውን ገንዘብ የሚያገኙት የሚመሩት ወይም የሚገዙት ህዝብ አለፈቃዱም እንኳ ቢሆን ከሚከፍለው ግብርና ቀረጥ ነው፡፡
በዚህ ከህዝብ የሚሰበሰብ ገንዘብ ላይ መንግስት የሚከተለው የአጠቃቀም ሁኔታ በሀገሪቱ እድገትና በህዝቡ የዛሬም ሆነ የነገ የኑሮ ሁኔታ ላይ ቀጥተኛ ተጽዕኖ ያሳድራል፡፡
ነገሩ ፈረንሳውያን፤ ‹‹ሙሉ በኩሉሄ የሆነ ሀገር በአለም ላይ ጨርሶ አይገኝም፡፡ ልባምና ባለ ራዕይ መሪዎች ግን ከሌሎች የተሻሉ ሀገራትን ይፈጥራሉ›› እንዳሉት ነው፡፡ በአለማችን የሀገራት ታሪክ ውስጥ በተደጋጋሚ ተፈጽሞ ያየነው ነገር ስለሆነ ይህ የፈረንሳውያን አባባል እውነትም፣ ትክክልም ነው፡፡
በነዳጅ ዘይት ሀብት የበለፀገችውና የአለማችን ልጅ እግር ሀገር የሆነችው ጎረቤታችን ደቡብ ሱዳን፣ ከሱዳን ተገንጥላ የራሷን ሉአላዊ መንግስት እንዳቆመች፣ መሪዎቿ ለዘመናት በጦርነትና፣ በረሀብ ቸነፈር ቁም ስቅሉን ሲያይ የኖረውን ህዝባቸውን ከነዳጅ ዘይት ሽያጭ የሚገኘውን ዛቅ ያለ ሲሳይ በአግባቡ በመጠቀም፣ ወደ እድገትና ብልጽግና፤ ያሻግሩታል ተብሎ በራሳቸው በደቡብ ሱዳናውያን ቀርቶ በመላው የአለማችንም ህዝብም ተገምቶ ሳይሆን ታምኖ ነበር፡፡
የደቡብ ሱዳንን የነፃነት ትግል በግንባር ቀደምትነት በመምራትና ሀገራቸውንና ህዝባቸውን ለነፃነትና ለሉአላዊነት በማብቃት ከሟቹ ከጆን ጋራንግ ቀጥሎ ሁነኛ የታሪክ ቦታ የያዙት ፕሬዚዳንቱ ሳልቫ ኪርና ምክትላቸው ሪክ ማቻርም ይህንን የህዝባቸውንና የአለምን ህዝብ እምነት በአጭር ጊዜ በብቃትና፣ በታማኝነት እውን እንደሚያደርጉት ባገኙት አጋጣሚ ሁሉ ምለው ተገዝተው ነበር፡፡
መቼም የማንኛችንም ሰብዕና ወይም ማንነታችን የሚገለፀው በተግባር በምናከናውነው ስራ እንጂ “እንሰራዋለሁ በምንለው ነገር እንዳልሆነ ለመረዳት፣ የተለየ አዕምሮና የተለየ የማስተዋል ጥበብ ባለቤት መሆን አይጠበቅብንም፡፡ ይህ እውነት ለግለሰቦች ብቻ ሳይሆን ለመንግስታትም ይሰራል፡፡
በ1932 ዓ.ም ጀርመናውያን በቻንስለር አዶልፍ ሂትለርና በናዚ ፓርቲ ፍቅር ወድቀው፣ እፍ ክንፍ ባሉበት ወቅት እየተደገሰ ያለውን የጦርነት ድግስና የሚያስከትለውን አስከፊ እልቂት በሚገባ የተረዳው ብርቅየው ሳይንቲስት አልበርት አይንሽታይን በተለይ ለአሜሪካኖች ማስጠንቀቂያውን የሰጠው፤ “ወዳጆቼ ናዚዎች ለሚናሩት ነገር ጨርሶ ቁብ አትስጡ፤ ይልቁንስ ዋነኛ ትኩረታችሁን ከሚሰሩት ስራ ላይ አድርጉ፤ ያን ጊዜ ሁሉም ነገር ይገለጽላችኋል” በማለት ነበር፡፡
የደቡብ ሱዳን ህዝብም ለዘመናት ሲመኘውና ሲያልመው የነበረው ሰላም እድገትና ብልጽግና ገና ከመፀነሱ እንደጨነፈገበት ያወቀው፣ የመሪዎቹን ንግግር ሳይሆን ድርጊታቸውን በግልጽ ማየት እንደ ጀመረ ነበር፡፡ እነኛ “ህዝባችንንና ሀገራችንን በእድገትና፣ በብልጽግና ጎዳና በመምራት የአዲስ ብሩህ ህይወት ባለቤት እናደርገዋለን” እያሉ ሌት ተቀን ሲምሉና ሲገዘቱ የነበሩት የደቡብ ሱዳን መሪዎች፤ ከነዳጅ ዘይት ሽያጭ የተገኘውን አምስት ቢሊዮን ዶላር የሚጠጋ የህዝባቸውን ሀብት ለግላቸው በመቀራመት፣ ያንን መከረኛ ህዝባቸውን በቀላሉ ከማይወጣው ዘር ተኮር የእርስ በርስ ጦነት ውስጥ ሲዘፍቁት የፈጀባቸው ጊዜ አስራ አንድ ወራት ብቻ ነበር፡፡
አሪፍ ከሆኑት የጀርመናዊው ፈላስፋ ሉድዊግ ቮን ማዝስ ንግግሮች አንዱ፤ “በሙስና እንደተበከለና ብቃት እንደሌለው መንግስት ያለ ለሰው ልጆች ስልጣኔና ብልጽግና ፀር የሆነ ነገር፣ በዚህ ዓለም ላይ ጨርሶ የለም” የሚል ነው፡፡ እነሆ ደቡብ ሱዳናውያንና የደቡብ ሱዳን መንግስት ከእልፍ አብነቶች አንደኞቹ ናቸው፡፡
እንደ እውነቱ ከሆነ፣ የሀገራትና የህዝባቸው የወደፊት እጣ ፈንታ፣ ዛሬ በሚሰሩት ስራ የሚወሰን መሆኑን ሀሰት ነው ብሎ ማን ከምሩ መከራከር ይችላል? የዱባይን የባለጠግነት መጠን የሚያውቁ በርካታ ሰዎች፤ ዜጎቿ የፈሰሰ ውሃ ሳያቀኑ እስከ ቂያማ ቀን ድረስ በምቾትና በድሎት አንቀባራ ማኖር ትችላለች ብለው ያምናሉ፡፡
ለመሪዋ ለሼክ ሞሀመድ ቢን ራሽድ አልማክቱም ግን ይህ አስተሳሰብ ጨርሶ ሊሰሙት የማይፈልጉትና “አጥፊ” የሚሉት አስተሳሰብ ነው፡፡ እሳቸው ከፈጣሪ የተቸራቸው የነዳጅ ዘይት ጠጋ፤ ነገ አሊያም ከነገ ወዲያ እንደሚያልቅና መላው ህዝባቸው እንደ ቅድመ አያቶቹ ወደ አሳ አጥማጅነትና ቴምር ሻጭነት እንደሚመለስ በሚገባ አውቀውታል፡፡
እነሆ ዛሬ ድፍን አለሙን ባስደመመ ሁኔታ እያካሄዱት ያለው የኢኮኖሚ ግንባታ መነሻውም ሆነ መድረሻው የህዝባቸው የነገና የተነገወዲያ ህይወት ብሩህ፣ ምቾትና ድሎቱም ያልተጓደለበት እንዲሆን ነው፡፡ ባለፈው ሀምሌ ወር ላይ በዱባይ የተካሄደውን የኮንስትራክሽን አለም አቀፍ ኤግዚቢሽን መርቀው ሲከፍቱ፤ “እኛ ዛሬ እየገነባን ያለነው ሌላ ነገር ሳይሆን ነገአችን ነው” ያሉበት ምክንያትም ለዚህ ነው፡፡  
የስኳር፣ የማዳበሪያና፣ የግድብ ግንባታ ሜጋ ፕሮጀክቶች ጉዳይ ግን ታሪኩ የተሳካ አይደለም በሚል ተራ የአዘቦት አገላለጽ ተነግሮ የሚያልፍ አይደለም፡፡ የእነዚህ ሜጋ ፕሮጀክቶች ግንባታ ጉዳይ የሀገሪቱንና የህዝቦቿን ነገ የሚያጨልም ብቻ ሳይሆን ጨርሶ የሚገድል፤ ያለ የሌለ ጥሪታቸውን እምሽክ አድርጎ እየበላ ሙልጫቸውን የሚያወጣ አደገኛ፣ በእጅጉ አስደንጋጭ የሆነ ጉዳይ ነው፡፡
እንደ እውነቱ ከሆነ፣ ኢትዮጵያ የምትገነባቸው ሜጋ ፕሮጀክቶች ዱባይ ከምትገነባቸው ሜጋ ፕሮጀክቶች ጋር በቁጥርም ሆነ በጠቅላላ ነገረ ስራቸው ሲወዳደሩ እዚህ ግቡ የማይባሉና የሚዛኑን ዘንግ ላመል ታህል እንኳ ማንቀሳቀስ የማይችሉ ናቸው፡፡
ይሁን እንጂ የአለም የኮንስትራክሽን ዘርፍ ከፍተኛ የባለሙያዎች ማህበር በአለማችን ከሚገነቡ ሜጋ ፕሮጀክቶች መካከል በቴክኖሎጂ አጠቃቀም፣ በግንባታ እቅድና ክትትል፣ በግንባታ ዲዛይን፣ በግንባታ በጀት አነስተኛነትና ቁጠባዊ አጠቃቀም፣ ግንባታውን በሚያከናውኑት ስራ ተቋራጮች አቅምና በጠቅላላ የፕሮጀክት አመራር ችሎታ መስፈርትነት ግንባር ቀደም ናቸው ተብለው አምና በ2008 ዓ.ም ከመረጧቸው ስምንት ሜጋ ፕሮጀክቶች ውስጥ የመጀመሪዎቹ አምስቱ ዱባይ የምታስገነባቸው ሜጋ ፕሮጀክቶች ናቸው፡፡
መቼም አብዛኞቻችን በቀላሉ ልንረዳው እንችላለን ተብሎ በባለሙያዎቹ እንደሚገመተው፤ ከላይ የተዘረዘሩት መስፈርቶች የኮንስትራክሽን ፕሮጀክት አመራር ሀሁ ናቸው፡፡ እነዚህን መስፈርቶች ስለምንነታቸው ብጥርጥርጥር ያለ ግንዛቤና እውቀት የሌለው ግለሰብም ሆነ ቡድን ሜጋ ፕሮጀክት ይቅርና መነኔ የሆነው የግንባታ ፕሮጀክት በስኬት ያጠናቅቃል ተብሎ አይጠበቅም፡፡
ሼክ ሞሐመድ ቢን ራሽድ አልማክቱም፤ ዱባይ አለምን ያስደመመችበት በርካታ ሜጋ ፕሮጀክቶች ከተገመተው ባነሰ የግንባታ ወጪና ያለአንዳች የሀብት ብክነት እጅግ በተሳካ ሁኔታ መገንባት የቻለችው በዋናነት ለፕሮጀክቶቹ እቅድ አወጣጥ፣ ለፕሮጀክቶቹ ዲዛይን፤ ለበጀት አጠቃቀም፣ ለስራ ተቋራጮች የፕሮጀክት ግንባታና አመራር አቅም የለየ ጥንቃቄና ትኩረት በመስጠት፣ እንዲሁም ለቀናት እንኳ ያልተቋረጠ የቅርብ ክትትልና ግምገማ ማድረግ በመቻላቸው እንጂ በአስማት ወይም በልዩ ተአምር እንዳልሆነ፤ ባገኙት አጋጣሚና ለጠየቃቸው ሁሉ ከማስረዳት ቦዝነው አያውቁም። ሀገራቸውንና ህዝባቸውን በቅንነትና በእውቀት ለማገልገል መልካም ራዕይና የማያወላውል ቁርጠኝነት ያላቸው መሪዎች አይነታቸውና መገለጫው እንዲህ ነው፡፡
በሀገራችን ያለው የአመራር አይነት መገለጫው ግን ከዱባዩ በእጅጉ የተለየ አራምባና ቆቦ ነው፡፡ ኢትዮጵያውያን ለዘመናት ባካሄዱት መራራ ትግልና በከፈሉት እጅግ ከፍተኛ መስዋዕትነት ህገ መንግስታዊ እውቅናና ዋስትና ያገኘውን ነፃነትና እኩልነታቸውን፣ ሰብአዊና ዲሞክራሲያዊ መብታቸውን ማክበር ባለመቻሉ፣ የተነሳበትን ህዝባዊ ተቃውሞና እምቢተኝነት ለማብረድ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ለማወጅ የበቃው ኢህአዴግና የሚመራው መንግስት፤ ሀገሪቱንና ህዝቧን ወደ ታላቅ የእድገትና የብልጽግና ህዳሴ ከፍታ ለማድረስ ቀረጽኳቸው ያላቸውን የተለያዩ ሜጋ ፕሮጀክቶች የሚያካሂዳቸው፣ የትም ሀገር በማይደረግ የአቦ ሰጡኝ ወይም የእውር ድንብር አመራርና እጅግ አስደንጋጭ በሆነ ከፍተኛ የህዝብ ሀብት በማባከን ነው፡፡
ለኢህአዴግና ለሚመራው መንግስት የፕሮጀክት እቅድ፣ ጥናት፣ አቅም፣ ዝግጅት፣ ዲዛይን፣ የአመራር ችሎታና ተገቢ ክትትል ወዘተ … የሚሉ መሰረታዊ የፕሮጀክት አስተዳደር ሀሁዎች፣ ምንም አይነት ትርጉም የማይሰጡ ባዶ የቃላት ክምር ናቸው፡፡
ለኢህአዴግም ሆነ ለመንግስት ሜጋ ፕሮጀክቶችን ለመገንባት የሚያስፈልገው ዋነኛ ቁልፍ ጉዳይ፤ ድፍረትና ድፍረት ብቻ ነው፡፡ የኢህአዴግና የመንግስት የሜጋ ፕሮጀክት የአመራር ዘይቤ አቦ ሰጡኝ ወይም የእውር ድንብር፣ የአመራር ፍልስፍናው ደግሞ “ደፋር ጭስ መውጫ አያጣም” የሚለው አገርኛ አባባል ነው። የፕሮጀክት አመራር ሳይንስ የግድ ስለሚላቸው መሰረታዊ ጉዳዮች መጨነቅ፣ ለኢህአዴግና ለመንግስት ሞኝነትና ጊዜ ማጥፋት ነው፡፡
ዋናው ጉዳይ መድፈርና ደፍሮ መግባት ብቻ ነው። ይህ ኢህአዴግንም ሆነ የሚመራውን መንግስት የመተቸትና የመውቀስ አባዜ ተጠናውቶኝ የማቀርበው ስሜት ጨርሶ አይደለም፡፡ ኢህአዴግና መንግስት በግልጽ የሚከተሉትና ራሱን ኢህአዴግን የሚመራውን መንግስት የሚመሩት ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ፤ ባደባባይ መስክረው ያረጋገጡት እውነት ነው፡፡
እዚህ ላይ የሚቀርበው መሰረታዊ ጥያቄ እንዲህ የሚል ነው፡- እንዲህ ያለው የኢህአዴግና የመንግስት የእውር ድንብር አመራር ክፍያው ምን ያህል ነው? ወዴትስ ያደርሰናል?›› የሳምንት ሰው ይበለን!!


Read 6037 times