የወጣት ሰዓሊያን ሀይሉ ክፍሌና ታምራት ስልጣን የስዕል ስራዎች ለእይታ የቀረቡበት ‹‹ታሪክን ለዛሬ›› የተሰኘ የስዕል አውደ ርዕይ፣ከትናንት በስቲያ ምሽት በድንቅ አርት ጋለሪ ተከፈተ፡፡ በኢትዮጵያ ታሪክ ላይ የሚያተኩረው አውደ ርዕዩ፤የሰዓሊያኑን አመለካከት፣ ሀሳብና ድንቅ የአሳሳል ጥበብ የሚያንፀባርቁ በርካታ ስዕሎችም እንደቀረቡበትየቤተ-ሥዕሉ ማናጀር ኤዶም በለጠ ገልፃለች። አውደ ርዕዩ ለተከታዮቹ 24 ቀናት ለተመልካች ክፍት ሆኖ ይቆያል ተብሏል፡፡ በተመሳሳይ አምስት ወጣት የሪያሊስቲክ ሰዓሊያን ስራዎቻቸውን ያቀረቡበት ‹‹ሀርመኒ›› የስዕል አውደርዕይ፤ባለፈው ቅዳሜ ከአትላስ አለፍ ብሎ በሚገኘው ኢሳያስ ያብዘር ጂምስቶንና አርት ጋለሪ ተከፍቶ እየታየ ነው፡፡ ሰዓሊ ዮሴፍ
አባተ፣ቴዎድሮስ ግርማ፣ዮናስ ደገፉ፣ አብይ እሸቴና መሀሪ ተሾመ በጋራ ከ25 በላይ ስራዎቻቸውን ያቀረቡበት ይሄው አውደርዕይ፤ ለአንድ ወር ያህል ለእይታ ክፍት ሆኖ እንደሚቆይ ለማወቅ ተችሏል፡፡
Published in
ኪነ-ጥበባዊ ዜና