Sunday, 26 February 2017 00:00

መንግስት የውጪ ሀገር ስደተኞችን ለማቋቋም እየሰራሁ ነው አለ

Written by  አለማየሁ አንበሴ
Rate this item
(3 votes)

     - የአውሮፓ ህብረትና ኔዘርላንድ ለስደተኞች ማቋቋሚያ የ720 ሚ. ብር ድጋፍ አድርገዋል
                - ወደ ኢትዮጵያ የሚገቡ ስደተኞች በየጊዜው እየጨመሩ ነው
                        
    የአውሮፓ ህብረትና የኔዘርላንድ ኤምባሲ፤ በኢትዮጵያ የሚገኙ የውጭ ሀገር ስደተኞችን ለማቋቋምና ስደተኞቹን እያስተናገዱ ያሉ አካባቢዎችን ለመደገፍ የሚውል የ720 ሚሊዮን ብር ፕሮጀክት ይፋ ያደረገ ሲሆን መንግስት በበኩሉ፤ ስደተኞችን ተጠቃሚ የሚያደርጉ አሰራሮችን እያዘጋጀ መሆኑን አስታውቋል፡፡
በአውሮፓ ህብረትና በኔዘርላንድ ኢምባሲ ይደገፋል የተባለውን የክልላዊ ልማትና እንክብካቤ ፕሮጀክትን በአዲስ አበባ ይፋ ያደረጉት በኢትዮጵያ የአውሮፓ ህብረት ልኡክ መሪ አምባሳደር ቻንታል ኧብረት፤ ኢትዮጵያ ለምትከተለው “ስደተኞችን እጅን ዘርግቶ የመቀበል” ፖሊሲ አድናቆት እንዳላቸው ገልፀው፤ ህብረቱም ይህን መነሻ አድርጎ ድጋፉን መለገሱን ተናግረዋል፡፡
720 ሚሊዮን ብሩ ስደተኞቹን ለመንከባከቢያና ስደተኞቹን ተቀብለው እያስተናገዱ ያሉ ማህበረሰቦችን ለመደገፍ እንደሚውል የተገለፀ ሲሆን ለትምህርት፣ ለውሃና ለኃይል አቅርቦት እንዲሁም ለሌሎች የመሰረተ ልማት ዝርጋታዎች ይውላል ተብሏል፡፡  የዚህ ፕሮጀክት ተጠቃሚዎች ስደተኛ ተቀባይ የሆኑት የትግራይ፣ አፋርና የሱማሌ ክልል ሲሆኑ የኤርትራና የሶማሊያ ስደተኞች የዚህ ፕሮግራም ዋነኛ ተጠቃሚ እንደሚሆኑ ተገልጿል፡፡
በስነ ስርአቱ ላይ ተገኝተው ስደተኞችን በተመለከተ መንግስት እያከናወናቸው ያሉ መርሃ ግብሮችን ይፋ ያደረጉት የስደተኞችና ከስደት ተመላሾች ጉዳይ ጽ/ቤት ም/ዳይሬክተር አቶ ዘይኑ ጀማል፤ በአሁን ወቅት የደቡብ ሱዳን፣ የኤርትራ፣ የሱማሊያ፣ የኬንያና የሌሎች ሀገራትን ጨምሮ 8 መቶ ሺህ ስደተኞች በኢትዮጵያ በተለያዩ ካምፖች እንደሚገኙ ጠቁመው መንግስት ስደተኞችን ማቋቋም የሚያስችል ፕሮግራም መንደፉን አስረድተዋል፡፡ እ.ኤ.አ በመስከረም 2016 ስደተኞችን አስመልክቶ በተደረገው የዓለም መሪዎች ስብሰባ ላይ፤ ኢትዮጵያ ስደተኞችን ለማቋቋም ቃል በገባችው መሰረት፡ የተለያዩ መርሃ ግብሮችን መቅረጿን ያመለከቱት አቶ ዘይኑ፤ ከስደተኞቹ 10 በመቶ ያህሉ (80 ሺህ)  ከካምፕ ውጪ የመኖር መብት ተጠቃሚ እንዲሆኑ፣ የስራ ፍቃድና፣ የነዋሪነት መታወቂያ ደብተር እንዲያገኙ መታቀዱን አስረድተዋል፡፡
አድልኦ ሳይደረግ የሁሉም ሀገር ስደተኞች ከመጀመሪያ ደረጃ አንስቶ እስከ ከፍተኛ የትምህርት ተቋም ድረስ ዘልቀው የትምህርት እድል እንዲያገኙ እንዲሁም በመስኖ ሊለማ የሚችልና 100 ሺህ ስደተኞችን ተጠቃሚ የሚያደርግ መሬት የሰብል ልማት እንዲያለሙበት ማዘጋጀቱን አስታውቀዋል፡፡  
በሀገሪቱ ከሚገነቡ የኢንዱስትሪ ፓርኮች መካከል የተወሰኑት ከሚቀጥሯቸው ሰራተኞች 30 በመቶዎቹ ስደተኞች እንዲሆኑ እንደሚደረግም ተገልጿል፡፡ ለመቶ ሺህ ሰዎች ከሚፈጠረው የስራ እድል ውስጥ 30 ሺህ ያህሉን ስደተኞች እንዲጠቀሙበት ለማድረግ ኢትዮጵያ ቃል ገብታለች ተብሏል፡፡ ለዚህ አይነቱ የሥራ ዕድል ከአውሮፓ ህብረት 50 ሚሊዮን ዩሮ እርዳታ  ከአውሮፓ ኢንቨስትመንት ባንክ 200 ሚሊዮን ዶላር ብድር እንደሚገኝም አምባሳደር ሻንታል በንግግራቸው ጠቁመዋል፡፡
መንግስት ስደተኞች የደህንነት ስጋትም ሆነ የዜጎች ተፎካካሪ ናቸው የሚል እምነት እንደሌለው ገልፀው፤ ስደተኞቹን አደራጅቶ የስራ እድል ተጠቃሚ ለማድረግ ታቅዷል ብለዋል፡፡
በደቡብ ሱዳንና በሶማሊያ ካለው ድርቅ ጋር በተገናኘም በቀጣይ ጊዜያት በርካታ ስደተኞች ወደ ኢትዮጵያ ይመጣሉ ተብሎ እንደሚጠበቅ የጠቆሙት አቶ ዘይኑ፤ የዝግጁነት እቅድ አውጥተን እየሰራን ነው ብለዋል፡፡ ከደቡብ ሱዳን ብቻ ባለፉት 5 ወራት፣ ከ58 ሺህ በላይ ተጨማሪ ስደተኞችን ተቀብለናል ብለዋል አቶ ዘይኑ፡፡
በጋምቤላ ለእርሻ ኢንቨስትመንት ለባለሀብቶች በተሰጠ መሬት ላይ ስደተኞች እየሰፈሩ ነው የሚለው አቤቱታ ሀሰተኛ መሆኑንም ም/ዳይሬክተሩ ገልፀው፤ ስደተኞቹ ከእንዲህ ያሉ መሬቶች ጋር ግንኙነት የላቸውም ብለዋል፡፡
ኢትዮጵያ ስደተኞችን ተቀብላ በማስተናገድ ከአፍሪካ 2ኛ ደረጃ ላይ የተቀመጠች ሲሆን ከ3 መቶ ሺህ በላይ የደቡብ ሱዳን፣ 250 ሺህ የሶማሊያና 265 ሺህ የኤርትራ ዜጎችን ጨምሮ የኬንያ፣ ሱዳንና የአረብ ሀገራት ስደተኞች ይገኛሉ፡፡  

Read 3416 times