Saturday, 11 March 2017 12:40

ኦባማ “ትራምፕን ለማስገደል አሲረዋል” የሚለው የጎግል መረጃ እያነጋገረ ነው

Written by 
Rate this item
(1 Vote)

ታዋቂው ድረገጽ ጎግል የቀድሞው የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ ስልጣናቸውን ያስረከቧቸውን አዲሱን ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕን ለማስገደል ሲያሴሩ ነበር በሚል ባለፈው እሁድ ያሰራጨው ሃሰተኛ መረጃ፣ ብዙዎችን እያነጋገረ መሆኑ ተዘግቧል፡፡
በድረገጾች አማካይነት የሚሰራጩ ሃሰተኛ ዜናዎችን እየተከታተለ እንደሚያጠፋና አሳሳች መረጃዎችን እንደሚቃወም ከወራት በፊት በይፋ ያስታወቀው ጎግል፤ ፊቸርድ ስኒፔትስ በተባለው ልዩ የድረገጽ የመረጃ አገልግሎቱ ኦባማ ከቻይና ጋር በመተባበር ትራምፕን ለማስገደል ሲያሴሩ ነበር የሚል ሃሰተኛ መረጃ ማሰራጨቱን ዘ ጋርዲያን ዘግቧል፡፡
ዌስተርን ሴንተር ፎር ጆርናሊዝም የተባለ ተቋም ይፋ ካደረገው ሚስጥራዊ ቪዲዮ አገኘሁት በሚል ጎግል ባለፈው እሁድ ይፋ ባደረገው በዚህ መረጃ፣ ኦባማ በስልጣን ዘመናቸው ማብቂያ ሰሞን ትራምፕን ለማስገደል ሲያሴሩ እንደነበር ማስታወቁን የጠቆመው ዘገባው፣ ጉዳዩ ብዙዎችን ማነጋገር መጀመሩን ተከትሎ ጎግል መረጃው ሃሰተኛ ነው ሲል ማስተባበሉን ገልጧል፡፡
ጎግል ባወጣው የማስተባበያ መግለጫ ሆን ብሎ ሃሰተኛውን መረጃ እንዳላሰራጨ በመጥቀስ፣ ተጠቃሚዎች ለሚያነሷቸው የተለያዩ ጥያቄዎች ምላሽ የሚሰጥበት ፊቸርድ ስኒፔትስ የተባለው ልዩ የመረጃ አገልግሎቱ፣ ምላሾችን የሚሰጠው ከተለያዩ ድረገጾች የሚያገኛቸውን መረጃዎች መሰረት በማድረግ ከመሆኑ ጋር በተያያዘ ያልተረጋገጠው መረጃ ከተጠቃሚዎች ዘንድ ሊደርስ መቻሉን አስታውቋል፡፡
ኦባማ በትራምፕ ላይ የግድያ ሴራ ሲያደርጉ ነበር የሚለው መረጃ ሃሰተኛ መሆኑን በማረጋገጥ በአፋጣኝ ከድረገጹ እንዲወገድ ማድረጉን የጠቆመው ጎግል፤ ሃሰተኛው መረጃ በመሰራጨቱ ሳቢያ ለሚደርሰው ማንኛውም ጉዳት ይቅርታ እንደሚጠይቅም ባወጣው መግለጫ አስታውቋል፡፡

Read 4425 times