Monday, 13 March 2017 00:00

የአለም የሴቶች ቀን በአለም ዙሪያ በአድማና በተቃውሞ ተከብሯል

Written by 
Rate this item
(2 votes)

የዘንድሮው የአለም የሴቶች ቀን ከዚህ በፊት ባልተለመደ ሁኔታ የሴቶች መብቶች እንዲከበሩና በሴቶች ላይ የሚፈጸሙ ጥቃቶች እንዲቆሙ በሚጠይቁ እጅግ በርካታ ሴቶች የተሳተፉባቸው አድማዎችና የተቃውሞ ሰልፎች በአለም ዙሪያ በሚገኙ የተለያዩ አገራት ከተሞች ባለፈው ረቡዕ ተከብሮ ውሏል፡፡
በዕለቱ በማድሪድ ከ40 ሺህ በላይ ሴቶች አደባባይ ወጥተው የመብት ጥሰቶች እንዲቆሙ በተቃውሞ ሰልፍ የጠየቁ ሲሆን፣  ከአስር ሺህ በላይ የቱርክ ሴቶችም በመዲናዋ ኢስታንቡል ባደረጉት ሰልፍ “ወንዶች በሴቶች ላይ የሚፈጽሟቸው ጾታዊ ጥቃቶች ያብቁ” ሲሉ ድምጻቸውን አሰምተዋል፡፡
በአሜሪካ አንዳንድ ከተሞች “አንድ ቀን ያለ ሴት” የሚል መሪ ቃል ባለው አድማ፣ በርካታ ሴቶች በዕለቱ ከስራ ገበታቸው በመቅረት የሴቶችን ሚና ለማሳየት የሞከሩ ሲሆን ኒውዮርክንና ዋሽንግተንን ጨምሮ በተለያዩ የአገሪቱ ከተሞች በሺዎች የሚቆጠሩ ሴቶች የአለም የሴቶች ቀንን ምክንያት በማድረግ ሰልፍ እንደወጡ ቢቢሲ ዘግቧል፡፡
አየርላንዳውያን ሴቶች በበኩላቸው፤ ውርጃን የሚከለክሉ የአገሪቱ ህጎችን በመቃወም ከስራ የማቆም አድማ ከማድረግ ባለፈ ቀኑን ሙሉ ጥቁር ልብስ ለብሰው ውለዋል፡፡ የፖላንድ ሴቶች የእግር ጉዞ በማድረግ መንግስታቸው የጾታ እኩልነትን እንዲያሰፍንና ጥበቃ እንዲያደርግ የጠየቁ ሲሆን፣ ለሴቷ ተገቢው ክብር እንዲሰጣትም ድምጻቸውን አሰምተዋል፡፡
ከመቼውም ጊዜ በተለየ በበርካታ የአለማችን አገራት ከተሞች ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው ሴቶች ለመብቶቻቸው መከበር አደባባይ በስፋት በመውጣት ድምጻቸውን ያሰሙበት ነው በተባለው በዘንድሮው የአለም የሴቶች ቀን፤ በሜክሲኮ፣ በፖላንድ፣ በኬንያ፣ በጀርመን፣ በዩክሬን፣ በየመንና በሌሎች የአለማችን አገራት የተለያዩ ሰልፎች፣ አድማዎችና ተቃውሞዎች ተከናውነዋል፡፡

Read 1760 times