Monday, 13 March 2017 00:00

የትራምፕ የጉዞ ገደብ ቢሻሻልም ተቃውሞ ገጥሞታል

Written by 
Rate this item
(1 Vote)

አሜሪካ በአመቱ የምትቀበላቸው ስደተኞች ቁጥር ከ110 ሺህ ወደ 50 ሺህ ዝቅ ተደርጓል

        የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ፤ የሙስሊም አገራት ዜጎችን ተጠቂ ያደረገ ነው በሚል አለማቀፍ ተቃውሞ በገጠመውና ከአንድ ወር በፊት ባወጡት የጉዞ ገደብ ላይ የተወሰነ ማሻሻያ በማድረግ ባለፈው ሰኞ ይፋ ያደረጉት አዲሱ የጉዞ ገደብ ትዕዛዝ፣ ከአገራትና ከተመድ ተቃውሞ እንደገጠመው እየተዘገበ ነው፡፡
የሱዳን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር፣ ሱዳናውያን በአሜሪካ በተካሄዱ የሽብር ወንጀሎች ላይ ተሳትፈው እንደማያውቁ በማስታወስ፣ በመጪው ሳምንት ተግባራዊ ይደረጋል ተብሎ በሚጠበቀውና ለሶስት ወራት ይቆያል በተባለው በዚህ የጉዞ ገደብ ትዕዛዝ ከልብ ማዘኑን መግለጹን ቢቢሲ ዘግቧል፡፡
የአሜሪካ መንግስት ሱዳንን ሽብርተኝነትን ይደግፋሉ በሚል ከዘረዘራቸው አገራት ተርታ ማሰለፉን ያስታወሰው ሚኒስቴሩ፤ ሱዳንን ከዝርዝሩ እንዲያወጣ በድጋሚ መጠየቁንም ዘገባው ገልጧል።
አዲሱ የሶማሊያ ፕሬዚዳንት ሞሃመድ አብዱላሂ ሞሃመድ ፎርማጆ በበኩላቸው፣ አሜሪካ የጉዞ ገደቡን እንድታነሳ የጠየቁ ሲሆን፣ የጉዞ ገደቡ በቀጥታ ተጠቂ ከሚያደርጋቸው በርካታ ቁጥር ያላቸው ስደተኞች መካከል፣ በኬንያው ዳባብ የስደተኞች መጠለያ ውስጥ ሆነው ወደ አሜሪካ የሚገቡበትን ቀን በጉጉት በመጠባበቅ ላይ የሚገኙ 15 ሺህ ያህል ሶማሊያውያን ስደተኞች ቀዳሚነቱን እንደሚይዙ ዘ ጋርዲያን ዘግቧል፡፡
በአሜሪካ የሚገኙ 150 ሺህ ያህል ሶማሊያውያን ስደተኞች ለአገሪቱ ኢኮኖሚ በአንድም ሆነ በሌላ መንገድ ጉልህ አወንታዊ ሚና እየተጫወቱ ይገኛሉ ያሉት ፎርማጆ፤ አገራቸው አልሻባብን የመሳሰሉ አሸባሪ ቡድኖችን በመዋጋት ረገድ የጀመረቺውን ጥረት አጠናክራ እንደምትቀጥል በመግለጽ፣ የጉዞ ገደቡ ይህን እውነታ ከግምት ውስጥ ያላስገባ ነው ሲሉ ተችተውታል፡፡
የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የስደተኞች ከፍተኛ ኮሚሽነር ፊሊፖ ግራንዲ፣ ስደተኞች በአገራቸው የገጠሟቸውን መከራና ስቃዮች ለማምለጥ አገራቸውን ጥለው ለመውጣት የተገደዱ ዜጎች እንጂ ወንጀለኞች አይደሉም፣ የትራምፕ ትዕዛዝ ተገቢ አይደለም ብለዋል፡፡
የሃዋይ ግዛት አስተዳደር የትራምፕ የጉዞ ገደብ እንዳይተገበር የሚጠይቅ ክስ ባለፈው ማክሰኞ መመስረቱንና የእስልምና እምነት ተከታዮች የሆኑ ሁለት የአሜሪካ ኮንግረስ አባላትም የጉዞ ገደቡ ሙስሊሞችን ታላሚ ያደረገ አግላይ እርምጃ መሆኑን በመግለጽ፣ ትዕዛዙ ተግባራዊ እንዳይደረግ ተግተው እንደሚታገሉ ማስታወቃቸውን ዘ ኢንዲፔንደንት ዘግቧል፡፡
ትራምፕ ከዚህ ቀደም ባወጡትና ተግባራዊ እንዳይደረግ በፍርድ ቤት ውሳኔ በታገደው የጉዞ ገደብ ትዕዛዝ ውስጥ ዜጎቻቸው ወደ አሜሪካ እንዳይገቡ የተከለከሉት አገራት ኢራን፣ ሶማሊያ፣ ሱዳን፣ የመን፣ ሶርያ፣ ሊቢያ እና ኢራቅ እንደነበሩ ያስታወሰው ዘ ጋርዲያን፣ ትራምፕ በአዲሱ ትዕዛዝ ኢራቅን ከዝርዝሩ ማውጣታቸውን ዘግቧል፡፡
በአዲሱ ትዕዛዝ ለውጥ ከተደረገባቸው ጉዳዮች መካከል፣ የስድስቱ አገራት ዜጎች የሆኑ ቋሚ ነዋሪዎች፣ ቪዛ ያላቸው፣ ከዚህ ቀደም በስደተኝነት የተመዘገቡ ወይም ጥገኝነት የተሰጣቸው እንዲሁም ሁለተኛ ዜግነት ያላቸው ሰዎች የጉዞ ገደቡ ሳይመለከታቸው ወደ አሜሪካ መግባት እንዲችሉ መፍቀዱ ይጠቀሳል፡፡
የአሜሪካ መንግስት በአዲሱ የፈረንጆች አመት 2017 ብቻ 110 ሺህ ያህል ስደተኞችን ለመቀበል አቅዶ የነበረ ቢሆንም፣ አዲሱ የትራምፕ የጉዞ ገደብ ግን በአመቱ ወደ አሜሪካ የሚገቡ የተለያዩ አገራት ስደተኞች ቁጥር ከ50 ሺህ መብለጥ እንደሌለበት የሚያግድ እንደሆነ ቢቢሲ ዘግቧል፡፡

Read 3231 times