Monday, 20 March 2017 00:00

የደቡብ ሱዳን ሙርሌዎች ለ3ኛ ጊዜ ጥቃት አድርሰው 28 ሰዎች ገድለዋል

Written by  አለማየሁ አንበሴ
Rate this item
(8 votes)

 ዓመት ሳይሞላ ታፍነው ተወስደው ያልተመለሱ ህጻናት ቁጥር ከ100 በላይ ሆኗል
       በጋምቤላ ክልል አንድ ዓመት ባልሞላ ጊዜ ውስጥ የደቡብ ሱዳን የሙርሌ ታጣቂዎች ሰሞኑን ለ3ኛ ጊዜ ባደረሱት ጥቃት 28 ሰዎች ገድለው፣ 43 ህፃናትን አፍነው መውሰዳቸው ታውቋል፡፡ መንግሥት ሐሙስ ዕለት 6 ህፃናትን ማስመለሱን አስታውቋል፡፡ መጋቢት 3 እና 4 2009 ዓ.ም መነሻቸውን ደቡብ ሱዳን ያደረጉ ከ1 ሺህ በላይ የሚሆኑ የታጠቁ የሙርሌ ጎሳ አባላት ድንበር ጥሰው ወደ ጋምቤላ
ጉጅ እና ጆር አካባቢዎች ዘልቀው በመግባት ጥቃቱን መፈፃማቸውን የጋምቤላ ክልላዊ መንግስት የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ ቻል ቻን ለሮይተርስ በሰጡት ቃል አረጋግጠዋል፡፡
የደቡብ ሱዳን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ ማዊን ማኮል አሪክ በበኩላቸው፤ በጋምቤላ ስለተፈጠረው ችግር መንግስታቸው መረጃ እንዳለው ጠቁመው፣“የኢትዮጵያ መንግስት ወታደሮች ለበቀል እርምጃ የደቡብ ሱዳንን ድንበር አቋርጠው ወደ ግዛታችን አለመግባታቸውን አረጋግጠናል” ብለዋል፡፡ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ቃል አቀባይ መንግስታቸው ሊወስደው ስላሰበው እርምጃ ያሉት ነገር የለም፡፡ እኚሁ የሙርሌ ታጣቂዎች ከሶስት ወራት በፊት ባደረሱት ተመሳሳይ ጥቃት 17 ሰዎችን መግደላቸው ተገልፆ የነበረ ሲሆን በወቅቱ መንግስት ወንጀል ፈፃሚዎቹን ተከታትሎ እርምጃ እንደሚወስድና ችግሩን በዘላቂነት ለመፍታት ከደቡብ ሱዳን መንግስት ጋር እየተነጋገረ መሆኑን አስታውቆ ነበር፡፡ ባለፈው አመት ሚያዚያ ወር ላይም የ3 ቀናት ብሄራዊ ሃዘን አዋጅ ያስከተለ ጥቃት በጋምቤላ ‹‹ጂካዎ›› እና ‹‹ላሬ›› ወረዳዎች ተፈፅሞ ከ200 በላይ ሰዎች ተገድለው፣ 160 ህፃናት ታፍነው መወሰዳቸው የሚታወቅ ሲሆን እስካሁንም ከተወሰዱት ህፃናት መካከል 60 ያህሉን ማስመለስ አልተቻለም። ሰሞኑን ከተወሰዱ ህፃናት ጋር ተደማምሮም ቁጥራቸው ከአንድ መቶ በላይ ሆኗል፡፡ በአንድ አመት ጊዜ ውስጥ የተገደሉት ከ 250 በላይ ናቸው፡፡የኢትዮጵያ መንግስት በበኩሉ፤አጥፊዎችን ተከታትሎ እርምጃ እንደሚወስድና ችግሩን በዘላቂነት ለመቅረፍ የአካባቢውን የህዝብ ለህዝብ ግንኙነት የሚያጠናክሩ መሰረተ ልማቶችን በሁለቱ አገሮች መካከል እየገነባ መሆኑን አስታውቋል፡፡

Read 3040 times