Saturday, 18 March 2017 15:17

ለኢትዮጵያ ቱሪዝም የሚተጋው የካረቢያን ሰው

Written by 
Rate this item
(1 Vote)

   • ለፍቅሩ ሲል ብቻ ኢትዮጵያን በመላው ዓለም ያስተዋውቃል
                       • ለቱሪስቶች ብቁ፤ ዓለም አቀፍ ደረጃን የጠበቀ አገልግሎት መስጠት አለብን
                       • ‹‹The Grate Run Of Ethiopia›› በቱሪዝም ማስታወቂያ ላይ የተሰራ ግድፈት?!
                       • የሬጌ ሙዚቃ ለኢትዮጵያ የቱሪዝም ኢንዱስትሪ ዋና የፕሮሞሽን መሳርያ ነው
                      • ሆቴሎች የሚያሰማሯቸው ሰራተኞች በከፍተኛ ደረጃ የሰለጠኑ ሊሆኑ ይገባል

      ራስ ሊቫይ ይባላል፡፡ በመዝገብ ስሙ  ማርክ ጆን ባፕቲስት ቬነስ ተብሎ የሚጠራ ሲሆን ፤ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ኃይማኖት የተጠመቀበት የክርስትና ስሙ ደግሞ አምደስላሴ ነው፡፡ በካረቢያን በምትገኝና ማርቲኔክ በተባለች ደሴት የተወለደው ራስ ሊቫይ፤ ከወጣትነቱ ጀምሮ የስደት ህይወቱን ያሳለፈው በአውሮፓ  ነበር፡፡ በፈረንሳይና በእንግሊዝ   በሚገኙ ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት ተምሯል፡፡ በቢዝነስና ማርኬቲንግ ፣ በኢንተርናሽናል ቱሪዝምና ሆቴል አስተዳደር እንዲሁም በእንግሊዝኛና ፈረንሳይኛ ቋንቋዎች ተርጓሚነት ከፍተኛ ትምህርቶችን በመከታተል ተመርቋል፡፡
በእንግሊዟ የለንደን ከተማ ያለፉትን 30 ዓመታት የኖረው ራስ ሊቫይ፤ ወደ ኢትዮጵያም  ሲመላለስ  ከ20 ዓመታት በላይ አስቆጥሯል፡፡  በፓን አፍሪካኒዝምና በራስ ተፈርያኒዝም ዓለም አቀፍ እንቅስቃሴዎች ንቁ ተሳትፎ እንደሚያደርግ ይናገራል፡፡ የኢትዮጵያ፤ የአፍሪካ፤ የካረቢያን አገራትና በመላው ዓለም ያሉ ጥቁር ህዝቦች ታሪክን በጥልቀት ሲያጠና የኖረው ራስ ሊቫይ፤ በኢትዮጵያ ላይ ያተኮሩ የተለያዩ ጽሁፎችን ዓለም አቀፍ ተነባቢነት ባላቸው መፅሄቶች፣ ጋዜጦችና የተለያዩ የሕትመት ውጤቶች ላይ ያወጣል፡፡ በዓለም አቀፍ የቱሪዝምና የሆቴል አስተዳደር ባለሙያነቱ ደግሞ ለኢትዮጵያ የቱሪዝም ኢንዱስትሪ እገዛና ድጋፍ እንደሚያደርግ ይገልጻል፡፡ በክልሎችና የከተማ መስተዳድሮች ከሚንቀሳቀሱ የቱሪዝም ቢሮዎች ጋር የበጎ ፍቃድ አማካሪ ሆኖ በማገልገል ዕውቅናና ምስጋና ተቀዳጅቷል፡፡  ዋንኛ መተዳደሪያው የንግድ ስራ ሲሆን የኢትዮጵያን ባሕላዊ አልባሳት፤ ጌጣጌጦችና ሌሎች ቁሳቁሶች ወደ ለንደን በመውሰድ ይሸጣል፡፡ በተጨማሪም የመፅሐፍትና የተለያዩ የህትመት ውጤቶች አከፋፋይም እንደሆነ ይናገራል፡፡ የእሱ ህልም ግን በሚወዳት ኢትዮጵያ የሥራ ፈቃድ አግኝቶ፣ለአገሪቱ በአቅሙ አስተዋጽኦ ማበርከት ነው፡፡ ይሄ ሁሉ ፍቅርና መቆርቆር ከየት የመጣ? ከፍቅር በፊት ዕውቀት ይቀድማልና ኢትዮጵያን እንዴት በጥልቀት ሊያውቃት ቻለ? የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ ግሩም ሰይፉ ከራስ ሊቫይ ጋር ባደረገው ጥልቅ ቃለ-ምልልስ ለእነዚህ ጥያቄዎች መልስ አግኝቷል፡፡ በኢትዮጵያ ቱሪዝም ዙሪያም በስፋት አውግተዋል፡፡ የኢትዮጵያ የቱሪዝም ኢንዱስትሪን ለማዘመንና ስኬታማ ለማድረግ የሚበጁ ዕውቀቶችንና አቅጣጫዎችን ከቃለምልልሱ ማግኘት ይቻላል፡፡ እነሆ ፡-

           እስቲ መጀመሪያ ስለ ትውልድ አገርህ ማርቲኔክ ትንሽ አስተዋውቀን…?
ማርቲኔክ በካረቢያን ባህር ምስራቃዊ ክፍል የምትገኝ ደሴት ናት፡፡ በ16ኛው መቶ ክፍለ ዘመን  የፈረንሳይ ቅኝ ግዛት ነበረች፡፡ በተለያዩ ጊዜያት ስፔንና እንግሊዝም በቅኝ ገዢነት  ተፈራርቀውባታል። ፈረንሳይኛ ዋናው የስራ ቋንቋ ቢሆንም  እንግሊዘኛና ስፓኒሽ ቋንቋዎች በስፋት የሚነገሩባት አገር ናት። ማርቲኔክ፤ ከመላው አውሮፓ፣ ከአሜሪካ፣ ከደቡብ አሜሪካ የሚመጡ  ቱሪስቶች ይጎበኟታል፡፡ በካረቢያን ሌሎች አገራትና ደሴቶች የሚገኙ ህዝቦችም እንደ ሁለተኛ አገራቸው ይመለከቷታል፡፡ በተለይ ከትሪንዳድ፤ በርባዶስ፤ ጃማይካ፤ ሴንት ሉሽያ፤ ከጓደሉፕ፤ ግሬኔዳ እና ሴንት ማርቲን የሚፈልሱ ህዝቦች መጠጊያ የሆነች ውብ ምድር ነች፡፡
ማርቲኔክን የአበባዎች ደሴት  ብሎ መጥራትም ይቻላል፡፡ በተለይ ሞቃታማ የአየር ንብረት የሚስማማቸው የአበባ ዝርያዎች በደሴቷ ላይ በብዛት ስለሚበቅሉ ልዩ የተፈጥሮ ውበት አጎናፅፈዋታል። የማርቲኔክ ህዝብ በየደጁ አበባ በማብቀል ባህሉም ይታወቃል፡፡ በመላው ማርቲኔክ ስትዘዋወር በየቦታው፣ በየመንገዱ፣ በየአደባባዩ፣ በየመናፈሻውና በየመኖርያ ቤቶች ግቢ በተለያየ ቀለማት የደመቁ የአበባ ተክሎችን ስትመለከት በአድናቆት ነው የምትፈዘው፡፡  በአትክልትና ፍራፍሬ አምራችነትና አከፋፋይነት የምትታወቅም ሲሆን በተለይ ለዓለም ገበያ ከምታቀርብባቸው የፍራፍሬ አይነቶች ሙዝና አናናስ ይጠቀሳሉ፡፡ በሌላ በኩል የተጣራ ነዳጅ ለዓለም ገበያ የምታቀርብ ሲሆን ‹‹ራም›› የተባለ ባህላዊ የአልኮል መጠጥ አምራችም ነች፡፡
አገርህን አሳምረህ ስላስተዋወቅከን አመሰግናለሁ። አሁን ወደ ኢትዮጵያ እንምጣ፡፡ እስቲ በኢትዮጵያ ላይ ስለምታቀርባቸው የፅሁፍ ስራዎች ልጠይቅህ---
 ኢትዮጵያን የሚመለከቱ ፅሁፎችን በለንደን ከተማና በድረገፅ በዓለም ዙርያ በሚሰራጩ የተለያዩ ሚዲያዎች ላይ አቅርቤአለሁ፡፡ በ2004 እ.ኤ.አ የቦሌ ዓለም አቀፍ ተርሚናል መገንባቱን አስመልክቶ ያዘጋጀሁት ፅሁፍ የመጀመርያው ነበር፡፡ በእንግሊዝና በካረቢያን አገራት  ከፍተኛ ተነባቢነት ባለው የጃማይካ ጋዜጣ ‹‹ዘ ግሊነር›› ላይ ለህትመት በቅቷል፡፡ ከዚያም ‹‹ኢስት አፍሪካን›› በተባለና በእንግሊዝ በሚታተም መፅሄት ላይ በተከታታይ ፅሁፎችን ማቅረብ ቀጠልኩ፡፡ በ2007 እ.ኤ.አ ላይ ኢትዮጵያ የሚሊኒዬም በዓሏን ስታከብር በዓለም አቀፍ ደረጃ በሚታወቀው ‹‹ራስታአይትስ›› ድረ-ገፅ ልዩ መጣጥፍም አቅርቤያለሁ፡፡ በተመሳሳይ ወቅት ለንደን ውስጥ በአማርኛና በእንግሊዘኛ ቋንቋዎች በታተመና የኢትዮጵያ ማህበረሰብ ባዘጋጀው መፅሄት ላይ ሚሊኒዬሙን ምክንያት በማድረግ በ3 የተለያዩ አጀንዳዎች ፅሁፎችን በማዘጋጀት አስነብቤም ነበር፡፡ ከየአፍሪካ ህብረት 50ኛ ዓመት የወርቅ ኢዮቤልዩ በዓል ጋር በተገናኘ ያዘጋጀሁት ጽሁፍም ተጠቃሽ ነው፡፡
ለኢትዮጵያ የቱሪዝም ዘርፍ ስላደረግሃቸው እገዛዎችና ድጋፎች በዝርዝር ልትነግረኝ ትችላለህ?…
በለንደን በሚገኝ ዩንቨርሲቲ ኢንተርናሽናል ቱሪዝምና ሆቴል አስተዳደር በምማርበት ወቅት በኢትዮጵያ ቱሪዝም ላይ የጥናት ፅሁፍ የምሰራበት እድል መፈጠሩ ዋንኛው መነሻ ነው፡፡ ከዚያ በኋላ ላለፉት 20 ዓመታት በኢትዮጵያ የቱሪዝም እንቅስቃሴዎች የተለያዩ አስተዋፅኦዎች ለማበርከት ሞክሬአለሁ፡፡ የቱሪዝም ዘርፍ ላይ ልዩ ትኩረት ማድረግ የጀመርኩት በ2007  የኢትዮጵያ ሚሊኒዬም ክብረ በዓል ጋር በተያያዘ ነበር።  በ2009፤ በ2012 እና በ2013 በተለያዩ የኢትዮጵያ ክልሎች በመዘዋወር ካደረግኋቸው ጉብኝቶች ጎን ለጎን ያከናወንኳቸው ተግባራትም ነበሩ፡፡ በ2009 በደቡብ ክልል የተለያዩ ከተሞችን ጎብኝቼአለሁ፡፡ በክልሉ የሚገኙ የተፈጥሮ ሃብቶች፣ ባህላዊ እሴቶች፣ አኗኗርና አመጋገብን የተመለከተ ልዩ ፅሁፍ ያዘጋጀሁበት ጉብኝት ነበር። ከተሞቹ ከደቡብ ካረቢያን አገራት ጋር በብዙ ሁኔታዎች መመሳሰላቸውን ያሳየሁበት ይህ ፅሁፍ፤ የደቡብ ክልልን የቱሪዝም መዳረሻዎች በማስተዋወቅ ረገድ ስኬታማ ነበር፡፡ ከክልሉ የቱሪዝም ቢሮም የምስጋና ወረቀት አግኝቼበታለሁ፡፡
ከሃዋሳ ከተማ የቱሪዝም ቢሮ ጋር በፈጠርኩት ግንኙነት በተለያዩ የቱሪዝም ማስተዋወቂያ ህትመቶች ዝግጅት ላይ የአርትኦት፣የትርጉምና የማማከር ስራዎችን በማከናወን ተሳትፌያለሁ፡፡ ከዚያም በአዲስ አበባ ለባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር ተመሳሳይ እገዛዎችን አድርጌያለሁ፡፡ በትግራይ ከመቀሌ ከተማ የቱሪዝም ቢሮ ጋር የክልሉን የቱሪዝም መስህቦች ለማስተዋወቅ በዲቪዲ በተዘጋጀ ፊልም ላይ በትርጉምና በአርትኦት ስራዎች ተሳትፌአለሁ፡፡ በአንድ ወቅት በአርባ ምንጭ በተካሄደ የቱሪዝም ሴሚናር ላይ ያለኝን እውቀትና ልምድ ያካፈልኩበት አጋጣሚም ነበር፡፡ በ2013 በታላቁ የህዳሴ ግድብና በኢትዮጵያ የመሰረተ ልማትና የኢኮኖሚ እድገቶች ላይ የሚያተኩር ብሮሸር አዘጋጅቼ በመላው አውሮፓ፤ በአሜሪካና በሰሜን አሜሪካ በማሰራጨትም ተሳክቶልኛል። ይህን ብሮሸር ሙሉ ወጭውን በመሸፈን  ነው ያዘጋጀሁት፡፡ አሁን 3ኛው ህትመት የሚያስፈልግበት ደረጃ ላይ ነው፡፡ በተመሳሳይ ወቅት በእንግሊዝ በሚገኙ የራስ ተፈርያን ማህበረሰብ በሚዘጋጅ ‹‹ተንደር›› በተባለ  መፅሄት ላይ ስለ ኢትዮጵያ ቱሪዝም የተለያዩ መረጃዎች ያሉበት፤ ለቱሪስቶች ምክር የሚሰጥ  ፅሁፍም አሳትሜ ነበር፡፡
ለኢትዮጵያ ቱሪዝምን ያስተዋውቃል ተብሎ ስለተሰራው ስህተት የበዛበት ቡክሌት እናውራ።  ግን መጀመሪያ ስለ ቡክሌቱ ለአንባቢዎች ጥቂት ነገር መግለፅ የሚያስፈልግ ይመስለኛል፡፡ በባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር ከ2 ዓመት በፊት የተዘጋጀው ቡክሌቱ 34 ገፆች ያሉት ሲሆን በመላው ዓለም ተሰራጭቷል፡፡ የፊትና የጀርባ ሽፋኖቹን በተራሮች ያስጌጠ ነው፡፡ በመጀመርያው ገፅ ላይ ‹‹የቱሪዝም ገነት›› በሚል ርእስ መረጃዎች አስቀምጧል። በሌሎች ገፆች ደግሞ በኢትዮጵያ ከፍተኛ ጎብኚ ያላቸው የቱሪዝም መዳረሻዎች በተከታታይ ከፎቶና ከአጫጭር መግለጫዎች ጋር ታትሞበታል፡፡ የጎንደር ፋሲለደስ ቤተ መንግስት፤ በላሊበላ የሚገኘው የቅዱስ ጊዮርጊስ ውቅር ቤተ ክርስትያን፤ የአክሱም ሐውልት፣ በአፋር ክልል የሚገኘው የእሳተ-ጎመራ ልዩ የተፈጥሮ መስህብ - ኤርታሌ፤ የሀረር ግንብ፤ የሰሜን ተራራዎች ፓርክና ጥያ የድንጋይ ትክል በአጫጭር መግለጫዎች ከታጀቡ ፎቶዎች ጋር ቀርበዋል፡፡ ከዚያም ዝቅተኛዎቹ የአዋሽና ኦሞ ሸለቆዎች፤ የኮንሶ መልክዓምድር፤ ልዩ ልዩ ፌስቲቫሎች፡- (አሸንዳ፣ መስቀል፣ ኢሬቻ፣ ገና እና ጥምቀት፤….) በቡክሌቱ እንዲተዋወቁ ተደርጓል፡፡
በጣም የሚገርምው ይህን ቡክሌት የተቀበልከው ወደ ኢትዮጵያ ከመምጣትህ በፊት በለንደን ከተማ የተለያዩ አገራት የቱሪዝም ኢንዱስትሪያቸውን በሚያስተዋውቁበት ዝግጅት ላይ ሲሰራጭ ነው። ወደ ኢትዮጵያ ስትመጣ በቡክሌቱ ይዘት ላይ ብዙ ስህተቶች መኖራቸውን ካሳየኸኝ በኋላ ነው ይህን ቃለ-ምልልስ ለመስራት የወሰንኩት፡፡ እስቲ በቡክሌቱ ላይ የታዘብከውን ስህተቶች አጫውተኝ ------
ስለ ኢትዮጵያ ብዙ የማውቅና በየጊዜው ተመላልሼ የምመጣ ቢሆንም፤ እንደ ማንኛውም የውጭ አገር ዜጋ መረጃዎች እፈልጋለሁ፡፡ ስለዚህም የጠቀስከውን የቱሪዝም ቡክሌት ለንደን ከተማ ላይ እያገላበጥኩ የተመለከትኩት በቁጭት ነበር፡፡ የቡክሌቱን ይዘት አብረን እንደተመለከትነው፣በየገፁ በተፃፉት የእንግሊዘኛ ቃላት በርካታ የስፔሊንግ ስህተቶች አሉባቸው። የእንግሊዘኛ ሰዋሰውን ብንፈትሸውማ -- ተወው፡፡ በየገፁ የተቀመጡት ፈዛዛ ፎቶዎችና ማራኪ ያልሆኑ የምስል ዲዛይኖችም ህትመቱ በቂ ትኩረት ተሰጥቶት አለመሰራቱን ያመለክታሉ፡፡  ምንም አይነት ፅሁፍም ሆነ ፎቶ ሳይኖረው ባዶውን የተተወ ገፅ መገኘቱም የሚያስደነግጥ ነው፡፡
ሌላው አስደንጋጭ ስህተት ደግሞ የመጨረሻው የሽፋኑ የውስጥ ገፅ ላይ የተመለከትከው ነው፡፡ የታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ዓመታዊ የ10 ኪሜ የጎዳና ላይ ሩጫ ውድድር ምስሎች በቀረቡበት በዚህ የሽፋን ገፅ፤ በትልቁ ጎልቶ የሰፈረው ፅሁፍ ‹‹The Grate Run Of Ethiopia›› ይላል፡፡ ‹‹The Great Ethiopian Run›› ለማለት ነው። ለቱሪዝም ኢንዱስትሪው  የላቀ አስተዋፅኦ እያበረከተ ስለሚገኘው  ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ላይ እንዲህ የጎላ ግድፈት መፈጠር አልነበረበትም፡፡ ስለ ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ እኮ በእንግሊዝ ብዙዎች ያውቃሉ፡፡ በተሳሳተ መንገድ ማስተዋወቁ ልክ አይደለም፡፡ በየዓመቱ ከ750 በላይ የውጭ አገር ዜጎች የሚያሳትፈው የጎዳና ላይ ሩጫው፤ በስህተት መተዋወቁ ለትዝብት እንደሚዳርግ መታሰብ ነበረበት፡፡ በርግጥ በጥራት የተሰሩ ሌሎች ቡክሌቶች፤ የተለያዩ ፓምፍሌቶችና በራሪ ወረቀቶች በመላው ዓለም መሰራጨታቸውን አውቃለሁ፡፡ ግን በዚህ ቡክሌት ላይ ያሉት ስህተቶች የኢትዮጵያን ቱሪዝም  በማስተዋወቅ ረገድ ብዙ መስተካከል ያለባቸው ሁኔታዎች እንዳሉ ያስገነዝቡናል፡፡
ወደ አዲስ አበባ ከወር በፊት እንደመጣሁ ብዙ የግል ስራዎች ቢኖሩብኝም፤ ለኢትዮጵያ ሁሌም ቅድሚያ ስለምሰጥ በቡክሌቱ ላይ ያሉ ግድፈቶችን በተመለከተ ከማውቃቸው የቱሪዝም ሰዎች ጋር ለመነጋገር ሞክሬአለሁ፡፡ ከሳምንት በፊት ከአንተ ጋር ተገናኝተን የቡክሌቱን ግድፈቶች ስንታዘብ ቆይተን በበጎ ፈቃደኝነት ‹‹ይህን ቡክሌት ሙሉ ለሙሉ የአርትኦት ስራውን ልስራው፤ ቢያንስ በአማካሪነት ላግዛችሁ›› በሚል በቀጥታ ከቱሪዝም ሃላፊዎች ጋር በድረገፅ በኩል ባገኘሁት የኢሜል አድራሻዎች ግንኙነት ለመፍጠር ሞክሬ ነበር፡፡
በአጠቃላይ እኔ ይህን ስህተት በግልፅ የምተቸው የአገሪቱን ገፅታ ለማሳጣት፤ አርትኦት በመስራት ልጠቀም ብዬ አይደለም፡፡ ሁልጊዜም ማየት  የምፈልገው የኢትዮጵያን መልካም ገፅታ ነው፡፡ እናም ቁጭቴ፣ አገሪቱ ደረጃውን በጠበቀና በአግባቡ በሚሰሩ ህትመቶች ለሌላው ዓለም መተዋወቅ ይኖርባታል የሚል ነው። እንግሊዘኛ ዓለም አቀፍ  ቋንቋ እንደሆነ ይታወቃል፡፡ ስለዚህም በዚህ ቋንቋ ተፅፈው ለቱሪዝም ማስተዋወቂያ ይሆናሉ በሚል የሚሰሩ ማናቸውም ህትመቶች ዓለም አቀፍ ደረጃቸውን የሚያሟሉ፤ ምንም አይነት ስህተት የሌለባቸው፤ በትኩረት የተዘጋጁ መሆን አለባቸው፡፡ በሌላ በኩል የኢትዮጵያን ቱሪዝም በእንግሊዝኛ ብቻ ሳይሆን በሌሎች ቋንቋዎችም ለማስተዋወቅ ጥረት ማድረግ ያስፈልጋል፡፡ የቱሪዝም መስኩ ከአማርኛና እንግሊዘኛ ባሻገር ተጨማሪ ሌሎች ቋንቋዎች ያስፈልጉታል፡፡ በተለይ ፈረንሳይኛ ወሳኝ ሲሆን በአፍሪካ ብዙ አገራት ፈረንሳይኛ ቋንቋ እንደሚናገሩ ይታወቃል፡፡ ስለሆነም ለማስተዋወቅ የሚዘጋጁ ህትመቶች ፈረንሳይኛ ቢጨመርባቸው ጠቃሚ ነው፡፡ ከተቻለ ደግሞ አረብኛና ስፓኒሽ ቋንቋዎች እንዲሁም ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ቻይናውያን ቱሪስቶች እንደ መብዛታቸው የእነሱን መንደሪን ቋንቋ የሚያውቁ ባለሙያዎች መፈጠር አለባቸው። ቋንቋዎችን በብዛት ማወቅ ለቱሪስቶች መስጠት የሚቻለውን አገልግሎት ማጠናከር ብቻ ሳይሆን ዓለም አቀፍ መግባባትን መፍጠር ነው፡፡
ከ2 ዓመት በፊት ኢትዮጵያ በአውሮፓ የቱሪዝምና የንግድ ምክር ቤት ‹‹የዓለማችን ምርጥ የቱሪዝም መዳረሻ›› በሚል ተመርጣ ነበር፡፡ ጁሚያ ትራቭል የተባለ ተቋም  ደግሞ በኢትዮጵያ ቱሪዝም ላይ በማተኮር በሰራው የ2017 ሆስፒታሊቲ ሪፖርት መሰረት፤ በ2016 ላይ ኢትዮጵያ ከ800ሺ በላይ ቱሪስቶች በማስተናገድ 5.6 ቢሊዮን ዶላር ወይንም ከ128 ቢሊዮን ብር በላይ ገቢ አግኝታለች ብሏል፡፡ በሌላ በኩል ዓለም አቀፉ የጉዞና ቱሪዝም ምክር ቤት በኢትዮጵያ የቱሪዝም ኢንዱስትሪ ለ979ሺ ሰዎች የስራ እድል መፍጠሩን በሪፖርቱ አመልክቷል፡፡ የኢትዮጵያ መንግስት እስከ 2020  በቱሪዝም መስክ ከፍተኛ እንቅስቃሴ ለማድረግ ‹‹LAND OF ORIGINS›› የሚል መርህ በማንገብ ተነስቷል፡፡ በየዓመቱ የሚመጡ ቱሪስቶችን በሦስት እጥፍ ለማሳደግ  እቅድ ከመያዙም በላይ ከአፍሪካ 5 ዋንኛ የቱሪስት መዳረሻ የሆኑ አገራት ተርታ ለመሰለፍም እየተሰራ ነው። በአፍሪካ ቱሪስት በብዛት የሚጎበኛቸውና ከፍተኛ ገቢ በማስመዝገብ ሞሮኮና ደቡብ አፍሪካ ግንባር ቀደም ናቸው፡፡  በየዓመቱ እያንዳንዳቸው ከ10 ሚሊዮን በላይ ቱሪስቶች ያስተናግዳሉ፡፡ ግብፅ ደግሞ በየዓመቱ ከ9.9 ሚሊዮን በላይ ቱሪስቶችን በማስተናገድ ትከተላለች፡፡ ሶስቱ አገራት ከፍተኛ የቱሪስት ፍሰት ሊኖራቸው የቻሉት በተጠናከሩ መሰረተ-ልማቶቻቸው እንዲሁም ለቱሪስቶች በሚያቀርቧቸው አገልግሎቶች  እንደሆነ ይገለፃል፡፡ ኢትዮጵያ በዓለም የኢኮኖሚክ ፎረም በተሰራ ጥናት  በምቹ የቱሪዝም መዳረሻነት ገና ብዙ ይቀራታል ተብሏል።  በቱሪዝም መሰረተ ልማቶች በተለይ በመንገድና ሆቴሎች ዙርያ የተሻለ ደረጃ ላይ ብትገኝም ለቱሪስቶች በሚሰጡ አገልግሎቶች ብዙ መሻሻሎች ያስፈልጋሉ፡፡ በአስተማማኝ ፀጥታና ደህንነት፣ በጤና እና ንፅህና፣ በተማረና በሰለጠነ የሰው ሃይል፤ በኢንፎርሜሽንና ኮሚኒኬሽን ቴክኖሎጂ አቅርቦት ዝቅተኛ ደረጃ ላይ ናት፡፡ በቱሪዝም ኢንዱስትሪው በተያዘው እቅድ መሰረት ስኬታማ ለመሆን ምን መደረግ አለበት? ቅድሚያ ትኩረት ሊሰጣቸው የሚገባቸው የትኞቹ ናቸው….?
የመጀመርያው ትኩረት መሆን ያለበት በቱሪዝም መስክ ያለውን የሰው ሃይል በዘመናዊ መልክ ማደራጀት ነው፡፡ ለዚህም ስኬት በስልጠናዎች ላይ መስራት ከፍተኛ ለውጥ ያስገኛል፡፡ በተለይ ወጣቱን ትውልድ የሚያሳትፉ የሰው ሃይል ምልመላዎች፤ የአቅም ግንባታ ስልጠናዎች መኖራቸው ተገቢ ነው።  ለቱሪስቶች ብቁ፤ ዓለም አቀፍ ደረጃን የጠበቀና በእውቀት ላይ የተመሰረተ አገልገሎት የሚሰጥበት መዋቅርም መዘርጋት ይኖርበታል፡፡ ከኢትዮጵያ ውጭ በተለያዩ የዓለም ክፍሎች የሚሰራጩ የቱሪዝም ማስተዋወቂያዎች በአቀራረብ፤ በመረጃቸው ትክክለኛነት፤ በዲዛይን ውበት ደረጃቸውን ጠብቀው መዘጋጀት አለባቸው፡፡ በአጠቃላይ በኢትዮጵያ ዓለም አቀፍ ደረጃ ያለው የቱሪዝም እንቅስቃሴ ያስፈልጋል። የቱሪዝም እድገት በፈጣን ሁኔታ እንዲቀጥል የሰው ሃይሉ በከፍተኛ ስልጠና እና አደረጃጀት መሻሻል እንዲሁም የማስተዋወቅ ስራዎች ጥራት ወሳኝ መሆናቸው መታወቅ አለበት፡፡ የቱሪዝም ኢንዱስትሪው ወጣቱን ትውልድ የሚያሳትፍ፤ የየክልሉን ማህበረሰብ በባለድርሻ አካልነት የሚያስተባብርና የሚጠቅም፣ ዓለም አቀፍ ደረጃውን በጠበቀ እውቀት የተጠናከረ መሆን ይኖርበታል፡፡
ኢትዮጵያ በቱሪዝም መስክ ግዙፍ አቅም እንዳላትና ብዙም እንዳልሰራችበት በተለያዩ ጊዜያት  የሚወጡ የዓለም አቀፍ ተቋማት ሪፖርተሮች የሚያረጋግጡት ነው፡፡ የቱሪዝም ኢንዱስትሪው የኢኮኖሚ እድገቱን ለማቀላጠፍና በድህነት ቅነሳ የተያዙ አቅጣጫዎችን በመደገፍ ረገድ ወሳኝ መሆኑ መታወቅ አለበት። ማንኛውም የቱሪዝም እንቅስቃሴ ዓለም አቀፍ ግንኙነቶችና ትውውቆችን በማዳበር፤ የኢኮኖሚ እድገት በማቀላጠፍና በማነቃቃት፤ ለማህበረሰቡ ዘላቂ የኢኮኖሚና የባህል እድገት እድሎችን በመፍጠር፤ እና የስራ እድሎችን በማብዛት ከፍተኛ አስተዋፅኦ ይኖረዋል፡፡ ኢንቨስትመንትን የሚያጠናክር፤ የውጭ ምንዛሬን የሚያሳድግ፤ መልካም ገፅታን የሚገነባ መሆኑን መገንዘብም ተገቢ ነው፡፡
በሌላ በኩል የቱሪዝም ኢንዱስትሪውን የሚያበለፅጉ አዳዲስ ሃሳቦችና እቅዶች፤ የአሰራር አቅጣጫዎችን ማበረታታት ያስፈልጋል፡፡ ለምሳሌ ያህል በሙዚቃ ኢትዮጵያን በተሻለ ደረጃ ማስተዋወቅ ይቻላል፡፡ በሬጌ ሙዚቃ እና ራስ ተፈርያኖች በሚሰሯቸው ሙዚቃዎች፣  በሚሳተፉባቸው ትልልቅ መድረኮች ኢትዮጵያን፣አፄ ኃይለስላሴን፤ አዲስ አበባን፤ ሻሸመኔን፤ አድዋን… ደጋግመው ይጠቅሳሉ። የኢትዮጵያ የባንዲራ ቀለማት የፋሽኖቻቸው፤ የመድረኮቻቸው ማድመቂያ ናቸው። ይህ ለቱሪዝሙ መስክ  ትልቅ አቅም የሚፈጥር ነው። ሬጌ  ሙዚቃን፤ የራስተፈርያኖች ባህልና ዓለም አቀፍ እንቅስቃሴን በማስተሳሰር ከኢትዮጵያ ቱሪዝም ጎን በበጎ አስተዋፅኦ እንዲቆሙ ማነሳሳት ይቻላል፡፡ በተለይ የሬጌ ሙዚቃ ለኢትዮጵያ የቱሪዝም ኢንዱስትሪ ዋና የፕሮሞሽን መሳርያ ነው ብዬ ነው የማምነው፡፡ ብዙ የሬጌ ሙዚቀኞች በተለያዩ የዓለም ክፍሎች ስለ ኢትዮጵያ ይሰብካሉ…የተስፋዋ ምድር እያሉ ያሞግሷታል፡፡ ጓዛቸውን ጠቅልልው መጥተው ሊኖሩባት፤ ሊሰሩባት ይፈልጋሉ፡፡ ይህን በቅርበት ስለማውቅ ሁሌም የማስበው ቢያንስ በኢትዮጵያ በየዓመቱ አንድ ዓለም አቀፍ የሬጌ ሙዚቃ ፌስቲቫል ቢኖር ብዬ ነው፡፡
ኢትዮጵያ በዓለም አቀፍ ደረጃ በገነነችበት የአትሌቲክስ ስፖርትም ቱሪዝሙን ማስተዋወቅ እንደሚቻልም መገንዘብ ጥሩ ነው፡፡ አሁን ለምሳሌ በክረምት ወር 16ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና በእንግሊዝ ለንደን ይካሄዳል፡፡ ይህን ሻምፒዮና ምክንያት በማድረግ ቱሪዝሙን ለማስተዋወቅ፤ በለንደን ከሚገኘው ኤምባሲ፤ ከዲያስፖራው ማህበረሰብና ከአትሌቲክሱ ባለድርሻ አካላት ጋር በቅንጅት በመስራት ስኬታማ መሆን አያዳግትም። በአጠቃላይ የኢትዮጵያ ቱሪዝምን ወደ ላቀ ደረጃ ለማሸጋገር በሚከተሉት ጉዳዮች ላይ ማተኮር ያዋጣል።  የባለሙያዎች ስልጠናዎች፤ የምክክርና የውይይት መድረኮች፤ ዎርክሾፕ፤ ሴሚናርና ሲምፖዚየም በየጊዜው መዘጋጀት አለባቸው፡፡ ዓለም አቀፍ ደረጃን የጠበቀና ዘላቂነት ያለው አሰራር  መኖር አለበት፡፡ በሰላምና መልካም አስተዳደር ዙርያ  የግንዛቤ መፍጠርያ መድረኮችና ልዩ ልዩ ዘመቻዎች በማድረግ ቱሪስቶች አገሪቱን ያለ አንዳች የፀጥታና የደህንነት ስጋት መጎብኘት እንደሚችሉ ማነሳሳት ያስፈልጋል፡፡ በአፍሪካ አህጉር የቱሪዝም ንግድ መረብ የሚዘረጋበትን መዋቅር ኢትዮጵያ በፈር ቀዳጅነት በማስተዋወቅ መስራት ትችላለች፡፡ ከሌሎች አገራት ጋር ጠቃሚ ተመክሮዎችን እንዲሁም ልምዶችን በመለዋወጥ መንቀሳቀስም ይቻላል።
የቱሪዝም ኢንዱስትሪውን ከሚፈታተኑ ጉዳዮች መካከል የአገልግሎት ሰጭ ተቋማት ብቃትና የተሟላ ጥራት ነው፡፡ ማንኛውም ቱሪስት ወደሚጎበኘው አገር ከገባ በኋላ በመጀመርያዎቹ 3 ሰዓታት በሚኖረው ቆይታ ላይ ትኩረት ያደረገ መስተንግዶ ወሳኝ መሆኑን ስትነግረኝ ነበር፡፡ እስቲ ስለሱ አብራራልኝ…
ማንኛውም ቱሪስት የሚጎበኘው አገር ሲደርስ መጀመርያ ላይ እግሩ የሚረግጠው አየር ማረፊያውን  ነው፡፡ ስለዚህም የሚኖረው አቀባበል በቱሪስቱ የእንግድነት መንፈስ ላይ ወሳኝ ተዕእኖ ይኖረዋል፡፡ ይህ አሰራር በካረቢያን አገራት በሚገኝ ልምድ ማጠናከር ይቻላል፡፡ በማርቲኔክ የሚደረገውን በምሳሌነት ልጠቅስልህ እችላለሁ፡፡ ቱሪስቶች በአየር ማረፊያዎችና መርከቦች በሚቆሙባቸው ወደቦች ሲደርሱ በመንግስት የቱሪዝም ተቋም የተደራጁ  የሙዚቃና የባህል ቡድኖች በልዩ ድባብ አቀባበል ያደርጉላቸዋል፡፡ ይህ በኢትዮጵያም ትኩረት ተሰጥቶት መለመድ ያለበት አሰራር ነው፡፡ ወጣቶችን ስልጠና ሰጥቶና አደራጅቶ አገርን ገና ከጅምሩ በሚያስተዋውቁበት ባህላዊ አቀባበል ላይ መትጋት  በቱሪስቱ ላይ የመጀመርያውን በጎ ስሜት የሚፈጥርበት ዕድል አለ፡፡ ቱሪስቱ ከአየር ማረፊያ ከወጣ በኋላ ደግሞ ወደ ሚያርፍበት ሆቴል የሚንቀሳቀስበት የትራንስፖርት አገልግሎትም ቀጣዩ ወሳኝ ነገር ነው፡፡ የትራንስፖርት አገልግሎቶች በተመጣጠነ ዋጋ፤ ምቹ በሆኑ ሁኔታዎች መሰጠት አለባቸው፡፡ የመጨረሻው ወሳኝ አቀባበል የሆቴል አገልግሎት ነው፡፡ የሆቴሎች አገልግሎት ከቱሪዝም ኢንዱስትሪው ጋር የላቀ ትስስር ስለሚኖራቸው በዚህ ላይ ትኩረት መስጠቱ አስፈላጊ ነው፡፡
 ሆቴሎች የኮከብ ደረጃቸውን መጠበቃቸው ብቻ ሳይሆን አገልግሎት ሰጭ ሰራተኞቻቸው በከፍተኛ ደረጃ የሰለጠኑና ደረጃውን የጠበቀ መስተንግዶ ለመስጠት የሚችሉ መሆን አለባቸው፡፡ በተለይ ኢትዮጵያ ውስጥ ከሆቴል አስተናጋጆችና ሌሎች ሰራተኞች ጋር በተያያዘ የማስተውለው የቋንቋ ችግር ነው፡፡ በሆቴል ለቱሪስቶች መስተንግዶ የሚሰጡ ባለሙያዎች ቢያንስ እንግሊዘኛ በተጨማሪም ፈረንሳይኛ ቋንቋ መናገር የሚችሉ መሆን አለባቸው፡፡ በዘመቻ መልክ በዚህ የቋንቋ ክህሎት ላይ በመስራት ለውጥ ማምጣት ይቻላል፡፡ በተጨማሪም በየሆቴሎቹ የእንግዳ መስጫ ክፍል፤ የማረፊያ አዳራሾች---- የአገሪቱን የቱሪዝም መዳረሻዎች በተመለከተ መረጃ የሚሰጡ የተለያዩ ህትመቶች ተሟልተው መገኘት ይኖርባቸዋል፡፡ በጉዞና በአስጎብኝነት ስለሚሰሩ ተቋማት ግልፅ የሆኑ መረጃዎች ያስፈልጋሉ፡፡ በአጠቃላይ በአየር ማረፊያ፤ በትራንስፖርት ከዚያም በሆቴል አገልግሎቶች ማንኛውም ቱሪስት በሚያደርጋቸው የመጀመርያዎቹ 3 ሰዓታት ቆይታ በትኩረት መስራት የቱሪስቶችን ፍሰት  ለማሳደግ ወሳኝ ነው፡፡
በሌላ በኩል ከተለያዩ አገራት የሚመጡ ቱሪስቶችን በአግባቡ ማስተናገድ የሚቻለው ስለ ባህላቸው በቂ ዕውቀትና ግንዛቤ ሲኖር ነው፡፡ የተለያዩ አገራት መገለጫ የሚሆኑ ባህላዊ እሴቶች በጥናት ገምግሞና ለአገልግሎት አሰጣጥ መዘጋጀቱ ለቱሪስቶች የላቀ እርካታ የሚፈጥር መሆኑን ማወቅ ያስፈልጋል። ስለዚህም የቱሪዝም ባለድርሻ አካላት፣ የመንግስት ሰራተኞች፣ አስጎብኚ ድርጅቶች፣ የጉዞ ወኪሎች፣ የሆቴል ማናጀሮች፣ አስተናጋጆች በየአገራቱ ባህላዊ እሴቶች ዙሪያ በቂ ግንዛቤ ሊኖራቸው በሚያስችል ፖሊሲ መንቀሳቀስ ያስፈልጋል። ባህላዊ እሴቶችን ጠንቅቆ ከማወቅ  ባሻገር የቱሪዝም ዲፕሎማሲን ማጠናከርም ወሳኝ ነው፡፡ ከተለያዩ አገራት የቱሪዝም ውጤታማ ተመክሮዎችን ለመቅሰም የሚያስችሉ የተቀናጁ የግንኙነት  መረቦች መዘርጋት ያስፈልጋል። በተለይ በዳያስፖራው ተጠቅሞ መንቀሳቀስ ውጤታማ ያደርጋል፡፡ ትውልደ ኢትዮጵያውያን፣ የታሪክ ጉዳዮች ግንኙነት ያላቸው፣ የጥቁር ህዝብ ምሁራኖችና ታጋዮች፣ የፓን አፍሪካ አቀንቃኞች… የቱሪዝሙ ባለድርሻ አካል መሆን አለባቸው፡፡
በመጨረሻው  ምን የምትለው አለህ?
በእኔ በኩል ከኢትዮጵያ የቱሪዝም እንቅስቃሴ ጋር በተያያዘ በየክልሎች በመዘዋወር ባከናወንኳቸው ተግባራት ከተለያዩ የቱሪዝም ሃላፊዎች ጋር መልካም ግንኙነት ስለፈጠረልኝ፤  ወደፊትም ይህን መልካም ግንኙነት በሚያጠናክሩ የተለያዩ ስራዎች ላይ በመሳተፍና ድጋፍ በመስጠት ለመቀጠል እፈልጋለሁ። ለቀጣይ ትውልድ ተምሳሌት በሚሆኑ የተለያዩ የቱሪዝም እንቅስቃሴዎች ላይ የበኩሌን አስተዋፅኦ ማድረግ እንደምችል ሙሉ እምነት አለኝ፡፡ በተለያዩ የቱሪዝም ማስተዋወቂያ የህትመት ውጤቶች፣ በትርጉምና በአርትኦት ሥራዎች ለመሳተፍ፤ በቱሪዝሙ መስክ የሰው ሃይል በማደራጀትና የአቅም ግንባታ ዙርያ ስልጠናዎችን በመስጠት ማገልገል ነው ምኞቴ፡፡
ለምወዳት ኢትዮጵያ በምሰራው ሁሉም ነገር የላቀ ኩራት ይሰማኛል፡፡ በቀጣይ ግን ያለኝን እውቀት፤ ሙያ፤ የዳበረ ልምድ በመጠቀም በሚመለከተው የመንግስት አካል የስራ ፈቃድ ተሰጥቶኝ ወይም ተቀጥሬ የምሰራበት ሁኔታ እንዲፈጠር እፈልጋለሁ። በኢትዮጵያ ውስጥ ልሰራበት የሚያስችለኝ የስራ ፈቃድ ‹‹ዎርክ ፐርሚት›› እንዲሰጠኝ ማመልከቴ አይቀርም፡፡ በጎ ምላሽ እንደማገኝበትም ተስፋ አደርጋለሁ፡፡ በሆቴልና የቱሪዝም አስተዳደር በርካታ ስራዎችን ማከናወን እችላለሁ። የተለያዩ የአቅም ግንባታ ስልጠናዎች በማዘጋጀት ማስተማር እችላለሁ። ልዩ ልዩ የማርኬቲንግ፤ የማስተዋወቅ፤ የፕሮጀክት እንቅስቃሴዎች ማካሄድም ይቻላል፡፡ ህጋዊ የስራ ፈቃድ የማገኝ ከሆነ ከመንግስትና ከግል የቱሪዝም ተቋማት ጋር በአጋርነት ከመስራት ባሻገር የራሴን ድርጅት በመክፈት ልሰራም አቅሙ አለኝ። በቱሪስት አስጎብኝነት፤ በጉዞ ወኪልነት፤ በተለያዩ የፕሮሞሽንና የማስታወቂያ ህትመት በፈረንሳይኛና እንግሊዘኛ ቋንቋ አስተርጓሚነት ተርጓሚነትና አስተማሪነት፤ በቱሪዝም ረገድ ዓለም አቀፋዊ የግንኙነት መረቦች በመዘርጋት፤ ወዘተ…  ብዙ መስራት ይቻላል፡፡

Read 2397 times