የኢትዮጵያ አየር መንገድ በ2010 ባወጣውና ተግባራዊ እያደረገው ባለው የ2025 ራዕይ፣ በ15 አመታት ውስጥ አሳካቸዋለሁ ብሎ ያስቀመጣቸውን ግቦቹን በአምስት አመታት ጊዜ ውስጥ ለማሳካት መቻሉን አስታውቋል፡፡
የኢትዮጵያ አየር መንገድ ዋና ስራ አስፈጻሚ አቶ ተወልደ ገብረ ማርያም ባለፈው ማክሰኞ በአዲስ አበባ የተጀመረውን የአለማቀፉ የሲቪልአቪየሽን ተቋም 4ኛው አለማቀፍ የአቪየሽን ዘርፍ ስልጠና ሲምፖዚየም ሲከፍቱ ባደረጉት ንግግር፣አየር መንገዱ አግባብነት ያለው ዕቅድ ማውጣቱና ትክክለኛውን የማስፈጸም ስልት መጠቀሙ በ15 አመታት ውስጥ አሳካቸዋለሁ ያላቸውን ግቦች በ5 አመታት ጊዜ ውስጥ ለማሳካት አስችሎታል ብለዋል። አየር መንገዱ ባለፉት ሰባት አመታት እጅግ ፈጣን እድገት ማስመዝገቡን የጠቆሙት አቶ ተወልደ፤ የአፍሪካ ቀዳሚው አየር መንገድ የመሆን ራዕዩን ካስቀመጠው ጊዜ በአስር አመት ያህል ቀደም ብሎ ለማሳካት መቻሉንም ገልጸዋል፡፡