Sunday, 30 April 2017 00:00

የባንክ፣ የኢንሹራንስና የማይክሮ ፋይናንስ ኤክስፖ ይከፈታል

Written by  ናፍቆት ዮሴፍ
Rate this item
(0 votes)

   ከሰኔ 16-18 2009 ዓ.ም ለሦስት ቀናት የሚዘልቅ “ኢትዮ ኢንተርናሽናል ባንኪንግ፣ ኢንሹራንስና ማይክሮ ፋይናንስ ኤክስፖ” በአፍሪካ ህብረት አዳራሽ ሊካሄድ መሆኑ ተገለፀ፡፡ “እያንዳንዷ ሳንቲም ዋጋ አላት” በሚል መሪ ቃል የሚካሄደው ኤክስፖው፤ በባንኪንግ፣ በኢንሹራንስ፣ በማይክሮ ፋይናንስና በሌሎች ተዛማጅ የስራ ዘርፎች የተሰማሩ የግልና የመንግስት ተቋማት እንዲሁም ሌሎች ባለድርሻ አካላት ለደንበኞቻቸውና ለተጠቃሚዎቻቸው የሚያቀርቡትን አዳዲስ ምርትና አገልግሎቶች በአንድ ቦታ የማስተዋወቅ ዕድል ይሰጣቸዋል ተብሏል፡፡
በዚህ ኤክስፖ ላይ መንግስታዊ ተቋማት፣ የመንግስትና የግል ባንኮችና ኢንሹራንሶች፣ የማይክሮ ፋይንስ፣ የፋይናንስና ኢንቨስትመንት ተቋማት፣ አማካሪ ድርጅቶች፣ ከፍተኛ የትምህርት ተቋማትና የህግና የሂሳብ ኦዲት አገልግሎት ሰጪ ድርጅቶች እንዲሁም ሌሎችም ይሳተፋሉ ተብሏል፡፡
በኤክስፖው ላይ የፓናል ውይይት፣ የመዝናኛና ሌሎች ዝግጅቶች የሚቀርቡ ሲሆን ኤክስፖውን ወደ 5 ሺህ ገደማ ታዳሚ ይጎበኘዋል ተብሎ እንደሚጠበቅ፣ የኤክስፖው አዘጋጆች ዴሪክ ኮሚዩኒኬሽን እና ሄድላይት ኤቨንት ጠቁመዋል፡፡

Read 1701 times