Print this page
Sunday, 07 May 2017 00:00

የእብዱ ማስታወሻ (የአጭር አጭር ልብወለድ

Written by  ድርሰት፡- ኒኮላይ ጎጎል ትርጉም፡- ሰለሞን አበበ ቸኮል
Rate this item
(1 Vote)

   ዲሴምበር 5
ሌሊቱን ሙሉ ጋዜጦችን ሳነብ አደርሁ፡፡ በስፔይን ውስጥ የሚገርሙ ነገሮች እየሆኑ ነው። የንጉሡ ዐልጋ ላይ ማንም እንዳልተቀመጠበት አነበብኹ፡፡
ክቡራኑ ማንን የዐልጋው ወራሽ እንደሚያደርጉ ጨንቋቸዋል፡፡ ከዚህም የተነሳ ብዙ ሁከትና ብጥብጥ ተነስቷል፡፡
መቸም ይህ ለኔ፣ በጣሙን የሚያስገርም ነገር ነው የሆነብኝ!
አንዳንዶች ደሞ የኾነች “ዶና” ዙፋኑን ትውረስ ብለዋል፡፡ እንዴት ነው ሴት ዙፋን ላይ የምትወጣው? በጭራሽ! እሷ አትችልም፤ያማ እማይኾን ነገር ነው፡፡ መውረስ ያለበት ንጉሥ ነው፡፡
--- ግን ደሞ አንድም ንጉሥ አልተገኘም እያሉ ነው፡፡ እንዴት ሆኖ ነው ንጉሥ የሚጠፋው? ንጉሥማ ይኖራል፤መኖር አለበት፡፡ ንጉሥ የለም ማለት እኮ መንግሥት የለም ማለት ነው፡፡ ንጉሥማ ይኖራል፤ አንድ የኾነ ቦታ ተሸሽጎ ይኾናል እንጂ መኖርስ ይኖራል፡፡ ይኾነኝ ተብሎ የሆነ ቦታ ተደብቆ እንዲቆይ ተደርጎ ይሆናል፡፡ በቤተሰብ ጉዳይ ተሰውሮ ወይም በአንዱ ውጭ ሀገር ለምሳሌ፣ በፈረንሳይ አንድ አደጋ ገጥሞት ሊሆን ይችላል፡፡ ወይም ደግሞ በሌሎች ምክንያቶች፡፡
ዲሴምበር 8
ዛሬ ወደ ቢሮ ሄጄ ለመግባት ብነሳም የተለያዩ ሰበቦችና ሀሳቦች ያዙኝ፡፡ ይሄ የስፔይን ነገር ከኔ ጭንቅላት በላይ ነው የሆነው፤ ሊገባኝ አልቻለም፡፡
እንዴት ብላ ነው ሴት ዙፋኑን የምትወርሰው፡፡ ዳሩ እነሱም ቢሆኑ አይፈቅዱላትም፡፡ ቀድሞ ነገር እንግሊዝም ዝም አትልም እንጂ፡፡ ከዚህም በላይ የጠቅላላውን አውሮፓ ሥርአት የሚነካ ነው - የነሞሳውን ንጉስ፣ የኛ ዘር፡፡
በበኩሌ እነዚህ ነገሮች እኔን እንደ አንድ ነገር ነው ያንዘረዘረኝ፡፡ በጣም ስለናጠኝ ሙሉውን ቀን ሌላ ነገር ማሰብም እንደተሳነኝ አልዋሽም፡፡
እራት ላይ፣ ማቭራ፣ “ቀልብህ እዚህ አይደለም” ብላኝ ነበር፡፡ እርግጥ ተገቢ ስለነበረ ሁለት ሳህኖችን አንስቼ ወለሉ ላይ አንከሻክሼአቸዋለሁ፡፡ ወዲያው ነው እንክሽክሻቸው የወጣ! ከዚያ ወጣሁና ከጉብታዋ ስር ወደሚያደርሰው መንገድ ቁልቁል ተንሸራሸርሁ። ምንም አላገኘሁም፡፡ ከዚያ በኋላ አልጋዬ ላይ ለረጅም ጊዜ በጀርባዬ ተንጋልዬ፣ያንኑ የስፓኛውን ጥያቄ እንዲችው ሳወጣ ሳወርድ ቆየሁ፡፡
እንግዲህ አስቀድሜ የማደርገው ነገር፣ እኔ ማን እንደነበርኩ ለራሷ ለማቭራ መንገር ነው፡፡ ያኔ ከፊቷ የቆመው የስፔይኑ ንጉሥ መኾኑን ስታውቅ፣ እጆቿን እያፍተለተለች፣ በፍርሃት ልትሞት ትደርሳለች፡፡ ይቺ ደደቢት ሴት፣ በስፔይኑ ንጉሥ ላይ በጭራሽ ዐይኖቿን ጥላ አታውቅም፡፡ ግን በጥቂት መልካም ቃላትች አረጋጋኋት፡፡.. አዲሱ መንግሥት ጥሩ መንግሥት ስለኾነ፣ ለርሷ ክፉ እንደማይኾን፤ እኔም ብኾን አንዳንዴ ጫማዎቼን ስላምታታች የማልቆጣት መኾኔን ነገርኳት፡፡
እሺ፣ከሌላው ከተራው መንጋስ ምን ይጠበቃል?- ከነዚህ ጋ እንዴት አድርጎ ነው በሕይወት ውስጥ ስላሉ ትላልቅ ነገሮች ማውራት የሚቻለው?
ማቭራ፤ የስፔይን ንጉሥ ሲባል የሚታያት ዳግማዊው ፊሊጵ ብቻ ነው፡፡ ሁሉም አንድ ስለሚመስላት ፈርታ ነበር፡፡ በእኔና በፊሊጵ መካከል ግን ምንም የሚያመሳስለን ነገር እንደሌለ፤ ደሞ በእኔ ዘንድ የካፑቺኖ ወንድማማች የሚባል ማኅበር እንደሌለ ኹሉ አስረዳኋት፡፡
ዛሬ ቢሮ አልገባሁም፤ ገደል ይግቡ!

Read 2754 times