Sunday, 14 May 2017 00:00

‹‹ቀዳማዊ ቴዎፍሎስ ፓትሪያርክ›› መፅሐፍ ተመረቀ

Written by  ናፍቆት ዮሴፍ
Rate this item
(0 votes)

 በግፍ በተገደሉት የቀድሞው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ፓትሪያርክ ቀዳማዊ ቴዎፍሎስ የህይወት ታሪክ፣ ላይ የሚያጠነጥነውና በታምራት አበራ ጀምበሬ የተሰናደው ‹‹ቀዳማዊ ቴዎፍሎስ ፓትሪያርክ›› የተሰኘ መፅሀፍ ባለፈው ሚያዚያ 23 ቀን 2009 ዓ.ም የቤተክርስቲያን አባቶች፣ ምሁራንና የተለያዩ እንግዶች በተገኙበት በኢትዮጵያ ሆቴል ተመረቀ፡፡ በምረቃ ስነ-ስርዓቱ ላይ በክብር እንግድነት የተገኙት የቅድስት ስላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ የበላይ ሀላፊ አቡነ ጢሞቴዎስ፤ ቅዱስነታቸው ትምህርትን ለማስፋፋት ያደረጉትን አስተዋፅኦ አብራርተዋል፡፡ በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የቋንቋዎች ተቋም የእንግሊዝኛ መምህር ዶ/ር አሰፋ ዘሩ፤ በመፅሀፉ ላይ ዳሰሳ ያቀረቡ ሲሆን ቄስ ዶ/ር ምክረ ስላሴ ገ/አማኑኤል የአይን ምስክርነትና ፓትርያርኩ ቤተክርስቲያኒቱን ለአለም ለማስተዋወቅ ያበረከቱትን አስተዋፅኦ ገልፀዋል፡፡
በዕለቱ የአጫበርና የቆሜ የአቋቋምና ያሬዳዊ ዜማ በሊቃውንተ ቤተክርስቲያን የቀረበ ሲሆን ‹‹የስላሴ ቀጠሮ›› የተሰኘ ከመፅሀፉ የተወሰደ ታሪክ በአርቲስት ፍቃዱ ተክለማሪያም ለታዳሚው መቅረቡንም የምርቃት ዝግጅት ኮሚቴ አስተባባሪ አቶ መልአከ ተሰማ ተናግረዋል፡፡ ከዚህ በተጨማሪም በአንዱአለም አባተ የሀዘን እንጉርጎሮ የቀረበ ሲሆን የቅኔ መርሀ ግብርና ቅዱስነታቸውን የሚያስታውስ አጭር ፊልም ለእይታ እንደበቃ ተገልጿል፡፡ በምረቃው ላይ ለቅዱስነታቸው አደባባይ ቢፈቀድላቸውም እስካሁን ሃውልታቸው አለመቆሙን አስመልክቶም በአስቸኳይ ሃውልታቸው እንዲቆም የምርቃቱ አስተባባሪ አቶ መልዓከ ተሰማ ጥሪ አቅርበዋል፡፡ “ቀዳማዊ ቴዎፍሎስ ፓትሪያርክ” መፅሀፍ በ410 ገፆች የተቀነበበ ሲሆን ለአገር ውስጥ በ150 ብርና ለውጭ አገር በ20 ዶላር ለገበያ ቀርቧል፡፡

Read 1961 times