Saturday, 20 May 2017 11:29

የኤጲስ ቆጶስ ተሿሚው ዶ/ር አባ ኃይለ ማርያም መለሰ የቀረበባቸውን አቤቱታ አስተባበሉ

Written by 
Rate this item
(10 votes)

“እምነትና ውኃ እንጂ ቅብዐ ቅዱስም ሜሮንም አልነበረም፤ ሰውዬውም አልቀባኝም”
ቅዱስ ሲኖዶሱ ከሹመታቸው በፊት ጉዳዩ እንዲጣራ አዝዟል
የኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን በመጪው ሐምሌ፣ 16 ኤጲስ ቆጶሳትን ትሾማለች

   የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ፣ በመጪው ሐምሌ ወር ኤጲስ ቆጶስነት የሚሾሙ 16 መነኰሳትንና ቆሞሳትን የመረጠ ሲሆን፤ ከተሿሚዎቹ አንዱ የሆኑት ዶ/ር አባ ኃይለማርያም መለሰ፤ በቤተ መቅደስ ውስጥ ከሃይማኖቱ ውጭ ከኾኑ ሌሎች የእምነት መሪዎች ጋራ “ቅብዓ ቅዱስ ተቀባብተዋል” በሚል የቀረበባቸውን አቤቱታ ድርጊቱን አልፈጸምኩም ሲሉ አስተባበሉ፡፡
የኦርቶዶክስ አብያተ ክርስቲያናትን ጨምሮ፣ የዓለም አብያተ ክርስቲያናት ኅብረት አባላት የኾኑ የወንጌላውያን አብያተ እምነት መሪዎች በተገኙበት፣ ባለፈው የካቲት 22 ቀን፣ በአዲስ አበባ ደብረ ምጥማቅ ሰዓሊተ ምሕረት ቅድስት ማርያም ካቴድራል የተካሔደው መርሐ ግብር፣ በሚያሳስቡ የጋራ ዓለም አቀፋዊ ጉዳዮች ላይ ለመመካከር የተዘጋጀ የጸሎት ሥነ ሥርዓት እንጂ፣ የቡራኬና ቀኖናዊ እንዳልነበረ፣ ዶ/ር አባ ኃይለ ማርያም፣ ለቤተ ክርስቲያኒቱ የሳተላይት ቴሌቭዥን ጣቢያ (ኢኦተቤ-ቴቪ) በሰጡት ማስተባበያ ተናግረዋል፡፡
የመርሐ ግብሩ ጭብጥ፥ “ውኃ ለኹሉም ፍትሐዊ በኾነ መንገድ” በሚል በወርኃ ጾሙ፣ ንጹሕ ውኃ በተለይ ከሰሃራ በታች ላለው ክፍለ አህጉር በፍትሐዊ መንገድ እንዲዳረስና ውኃ ወለድ በሽታዎች እንዲወገዱ ለማሰብ እንደተዘጋጀና ፓትርያርኩና ሊቃነ ጳጳሳቱም መገኘታቸውን የጠቀሱት ዶ/ር አባ ኃይለ ማርያም፣ ሥነ ሥርዓቱን የመሩትም፣ መርሐ ግብሩን እንዲያስተባብሩ ከቤተ ክርስቲያኒቱ በመወከላቸውና በኅብረቱ ተከታታይ መርሐ ግብር ቤተ ክርስቲያኒቱ ተረኛ በመኾኗ እንደነበር አስረድተዋል፡፡
“ቤተ ክርስቲያኒቱን ወክዬ፣ ውኃ በእጅጉ አስፈላጊ የእግዚአብሔር ስጦታ ስለመኾኑ በመጽሐፍ ቅዱስ የሰፈረውንና በሀገራችን ክርስቲያናዊ ትውፊት በጠበልና በእምነት የሚሰጠውን ፈውስ ተናግሬአለሁ፤” ያሉት ዶ/ር አባ ኃይለ ማርያም፤ “የጸሎት ሥነ ሥርዓቱን የምትመራው የኅብረቱ አባል ቤተ ክርስቲያን፣ በመነካካትና በተግባር የምትፈጽማቸው ምልክታዊ መገለጫዎች (symbolic action) አሉ፤ እኔም ተበጥብጦ ከቀረበው ውኃና እምነት በጣቴ ጠቅሼ በተሳታፊዎቹ ግንባር ላይ በትእምርተ መስቀል ምልክት አድርጌያለሁ፤ ይህም፣ ቤተ ክርስቲያኒቱን በእምነትና በሥርዓት የሚመስሏት ሌሎች እኅት አብያተ ክርስቲያናትም፣ በመሰል መርሐ ግብሮች ላይ የሚያደርጉትና የተለመደ ነው፤” ብለዋል፡፡
ለሥነ ሥርዓቱ የቀረበው፣ “ቅብዓ ቅዱስ እና ሜሮን ነው፤ በቤተ ክርስቲያኒቱ ሥርዓት ደግሞ በእምነት ከተለዩና ከተወገዙ ሰዎች ጋራ ይህ አይደረግም፤ መርሐ ግብሩም በቤተ መቅደስ ውስጥ መከናወን አልነበረበትም፤” በሚል ዶ/ር አባ ኃይለ ማርያም እንደቀቡና እንደተቀቡ የሚያሳዩ ምስሎችና ትችቶች በማኅበራዊ ድረ ገጽ በስፋት መሰራጨታቸውን በተመለከተ የተጠየቁት ዶ/ር አባ ኃይለ ማርያም፣ “ሰውዬው ጣቱን አስጠጋ እንጅ በፍጹም አልቀባኝም” ሲሉ ተቀብተዋል መባሉን አስተባብለዋል፡፡
“ቅብዓ ቅዱስም ቅብዓ ሜሮንም አልነበረም፤ እነርሱም አይቀበሉም፤ አይፈልጉም፤” ያሉት ዶ/ር አባ ኃይለ ማርያም፣ በምስሉ ላይ የሚታየው ሰው ጣቱን ወደ ግንባራቸው ሲያስጠጋ፣ በቤተ ክርስቲያኒቱ ሥርዓት የተሾመ ካህን ሌላ ሰው ሊነካውና ሊባርከው እንደማይችል በሹክሹክታ እንደነገሩትና ጣቱን እንደመለሰ ገልጸዋል፡፡  
ሥነ ሥርዓቱ ከተካሔደ ወራት ማስቆጠሩን ያስታወሱት ዶ/ር አባ ኃይለ ማርያም፣ ምስሉን በማኅበራዊ ድረ ገጽ ያሰራጩት ሰዎች፣ ለቤተ ክርስቲያን የሚቆረቆሩ ከኾነ፣ በወቅቱ እንዲብራራላቸው ሊጠይቋቸው ይችሉ እንደነበር ጠቅሰው፤ ቅዱስ ሲኖዶሱ ተሿሚ ኤጲስ ቆጶሳትን እስከሚመርጥበት ሳምንት በማዘግየትና ከሢመተ ጵጵስናው ጋራ በማገናኘት በድረ ገጽ ማስፋፋታቸው፥ “ግላዊ ጥቅምና ተልእኮ እንዳላቸው ያሳያል፤ እኔን ሳይሆን የቤተ ክርስቲያንን ክብር ነው የነኩት፤“ ሲሉ ቅሬታቸውን አሰምተዋል፤ ለሹመቱም የተመረጡት፣ በቅርበትና በሓላፊነት ላይ ስላሉ ሳይሆን በፈቃደ እግዚአብሔር እንደኾነ ተናግረዋል፡፡
የኤጲስ ቆጶስ ተሿሚው ዶ/ር አባ ኃይለ ማርያም ይህን ይበሉ እንጂ፣ የጸሎት ሥነ ሥርዓቱን መርሐ ግብር ሙሉ በሙሉ የሚያሳይ ቪዲዮ፣ ለሊቃነ ጳጳሳት እና ለሊቃውንት ቀርቦ እንዲጣራ፣ ቅዱስ ሲኖዶሱ ከትላንት በስቲያ አዝዟል፡፡ ዶ/ር አባ ኃይለ ማርያም በኤጲስ ቆጶስነት ቢሾሙም ተመልሰው የሚያገልግሉት ምእመኑን በመኾኑ፣ ለቅዱስ ሲኖዶሱና ለቤተ ክርስቲያኒቱ ክብር እንዲሁም የሕዝቡን ኅሊና ነጻ ለማድረግ ሲባል፣ የተነሣው ጥያቄ ከበዓለ ሢመቱ በፊት ምላሽ ማግኘት እንዳለበት፣ ጉዳዩ ያሳሰባቸው ሊቃነ ጳጳሳት ተናግረዋል፡፡ ሌሎች ተችዎች በበኩላቸው፡- ‹‹አጣርቶ መምረጥ ወይስ መርጦ ማጣራት?›› ሲሉ በዶ/ር አባ ኃይለ ማርያም ምርጫ ታይቷል ያሉትን የቅደም ተከተል ግድፈት ተችተዋል፡፡
በቤተ ክርስቲያኒቱ የአራቱ ጉባኤያት መምህርነት ከሚታወቁት ሌላው ዕጩ፣ ሊቀ ሊቃውንት አባ ዕዝራ ሐዲስ ጋራ ጎንደርን በመወከል ተወዳድረው፣ ሁለቱም የቅዱስ ሲኖዶስ አባላትን እኩል 18 ድምፅ በማግኘታቸው በተጣለው ዕጣ ለኤጲስ ቆጶስነት ተመርጠዋል የተባሉት አባ ኃይለ ማርያም፣ በነገረ መለኰት የዶክትሬት ዲግሪ እንዳላቸውና የጠቅላይ ቤተ ክህነት ምክትል ሥራ አስኪያጅ እንደኾኑ ተገልጿል፡፡
ግንቦት 2 ቀን የጀመረውን የርክበ ካህናት ምልአተ ጉባኤውን በትላንትናው ዕለት ያጠናቀቀው ቅዱስ ሲኖዶሱ፣ ክፍት በኾኑ መንበረ ጵጵስናዎች የሚሾሙ 16 ኤጲስ ቆጶሳትን ከትላንት በስቲያ ኃሙስ የመረጠ ሲኾን፤ ሢመተ ጵጵስናው፣ በመጪው ሐምሌ 9 ቀን እንደሚፈጸም ተጠቁሟል፡፡ ተሿሚዎቹ፣ ከ31 ተጠቋሚ መነኰሳትና ቆሞሳት መካከል፣ በክህነትና በምንኵስና ሕይወት፥ በትምህርት ዝግጅትና በአገልግሎት ልምድ በአስመራጭ ኮሚቴ ተለይተው ለቅዱስ ሲኖዶሱ እንደቀረቡና በምሥጢራዊ ድምፅ አሰጣጥ እንደተመረጡ ታውቋል፡፡
ከሢመተ ጵጵስናው በፊት ተሿሚዎቹ ኤጲስ ቆጶሳት፣ የቤተ ክርስቲያን አመራርና አስተዳደር እንዲሁም ቤተ ክርስቲያኒቱን እየፈተኗት በሚገኙ ዐበይት ወቅታዊ ጉዳዮችና እንደ አባትነታቸው የሚጠበቅባቸውን በተመለከተ፣ የአንድ ወር ሥልጠና እንደሚሰጣቸው፣ የቅዱስ ሲኖዶሱ ምንጮች አስታውቀዋል፡፡



Read 6116 times