Error
  • JUser: :_load: Unable to load user with ID: 62
Wednesday, 04 April 2012 10:03

ከአዲስ አበባ -ጅቡቲ እስከ ሻኩራ ገዳም

Written by 
Rate this item
(1 Vote)

“ለምግብ የምሰጠው ምንም ዋጋ አልነበረም፤ ከተገኘ እሰየው ከሌለ ግድ አልነበረኝም፤ ያ ነገር ለምዶብኝ ነው መሰለኝ አሁን እራሱ ሆድ መሙላቱ ብዙም ቦታ የምሰጠው አይደለም”

“ጃሉድ” ከቁራን የተገኘ ቃል ነው፡፡ “በሁሉም ነገር ውስጥ መገኘት››የሚል ትርጓሜ አለው፡፡ የጃሉድ እናት ጎጇቸውን ያደምቅላቸው ዘንድ የወለዱትን የመጀመሪያ ልጅ ለማየት እንኳን አልታደሉም፡፡እንደተወለደ ሕይወቱ አለፈ፡፡ተስፋ አልቆረጡም፤ በድጋሚ ሞከሩ፤ ሁለተኛውም ተመሳሳይ ሆነ፡፡ሦስተኛ ጥረት አደረጉ፤ የመጣው ጽንስ የመወለጃ ጊዜውም ደረሰና ምጡ መጣ፡፡ በፍጥነት እንዲደርስ የተጠራው አምቡላንሱ ድምፁን እያሰማ፣ ነፍሰጡሯን እናት ከቃሊቲ አሳፍሮ በሰላም ለማገላገል መክነፍ ጀመረ፡፡ጎተራ አካበቢ ሲደርስም ምጡ ተፋፋመ፡፡ ሕፃኑ ግን ሆስፒታል መድረስ አልቻለም፡፡  አምቡላንሱ ውስጥ ተወለደ፡፡ እናም ሆስፒታሉ ቀርቶ ጉዞ ወደ ኋላ ሆነ፤ ያን ቀን (የዛሬ 37 ዓመት) የተወለደውና በቅርቡ “ያቺን ነገር” የተሰኘ በሬጌ ስልት የተቀነቀነ አዲስ አልበም የለቀቀው ጃሉድ የተሰኘ ድምፃዊ ነው፡፡

ስደት ከትምህርት ቤት ወድ ጅቡቲ

‹‹ጃሉድ›› ትምህርቱን የጀመረው በሚሲዮን ትምህርት ቤት ነበር፡፡በኋላ ላይ ግን አባቱ በመታመማቸው ምክንያት መቀጠል አልቻለም፡፡ ሌላ ትምህርት ቤት ተቀየረለት፡፡ እዛም አልሆነም፡፡ ትምሕርቱን አቋርጦ ራሱን ለመቻል ከኑሮ ጋር ትንቅንቅ ጀመረ፡፡ የልጅ ምኞት ረጅም ነውና፣ ገና በወጣትነቱ ማለዳ አዲስ አበባ ቁጭ ብሎ ሆሊውድን ተመኘ፡፡ የተመኘውን በአቋራጭ ለማግኘት በባቡር ተሳፍሮ ድሬደዋ ገባ፡፡ ቀጠለና ወደ ጅቡቲ አመራ፡፡ የጃሉድ የስደት ጉዞ እንደ ተጻፈው ቀላል እንዳልነበር ይናገራል፡፡ በጅቡቲ ፖሊሶች ተንጠልጥሎ፣ ወደ ኢትዮጵያ ድንበር መመለስ ለእርሱ ብርቁ አልነበረም፡፡ ፖሊሶቹ ሲይዙት ወደ ኢትዮጵያ ይመልሱታል፡፡ እንደ ገና ተመልሶ ይሄዳል፤ አሰቃቂ በርሃዎችን በእግሩ ተመላልሶባቸዋል፤ ምኞቱ ግን ከጅቡቲ ሆሊውድ ገብቶ ዝነኛ አርቲስት መሆን ነበር፡፡ ምኞቱ ግን የሚሞከር አልሆነለትም፡፡ የጃሉድ ሆሊውድ ጅቡቲ ውስጥ የሚገኘው “ምንሊክ” የተሰኘው የኢትዮጵያ ሬስቶራንት ሆነ፡፡ ጅቡቲ ውስጥ የሚገኙ ሬስቶራንቶችን እያቀያየረ መሥራት የጃሉድ ዕጣ ፈንታ ሆነ፤ “ጅቡቲ ውስጥ የማልዘፍነው ዓይነት ዘፈን አልነበረም፤ ከኢትዮጵያ ብሔር ብሔረሰብ አንድም ዘፈን አይቀረኝም፤  ሁሉንም ዘፈን እዘፍን ነበር›› ይላል ጃሉድ፤ የጅቡቲ ቆይታውን ሲያስታውስ፡፡

ኑሮ በጅቡቲ ያልተመቸው ጃሉድ፤ እዛ ሆኖ ስለ ኢትዮጵያ ሙዚቃ ማሰቡን አላቋረጠም፡፡ ሁሌም የኢትዮጵያ ሙዚቃ እና ሙዚቀኞች የት ደረሱ? ሲል ይጠያይቃል!! የተገኘውን መረጃም ይሰበስባል፡፡ ወጣቶቹ ተሳክቶላቸው አልበም ሲያወጡ ተወዳጅም ሲሆንላቸው ሲሰማ፣ “እነሱ ከተሳካላቸው እኔስ ለምን ሄጄ አልሠራም” በማለት ሆሊውድን ተመኝቶ ኢትዮጵያን የለቀቀው ጃሉድ፤ ከአምስት ዓመታት የጅቡቲ ቆይታ በኋላ ተመልሶ አገሩ ገባ፡፡

ፍላጎት እና ምኞት ብቻቸውን ስኬት አይሆኑም እና አዲስ አበባ ጃሉድ እንዳሰባት ሆና አልተቀበለችውም፡፡ 10 የመከራ ዓመታትን አስቆጠረችው፡፡ ጃሉድ ስለእነዚህ የመከራ ዓመታት ሲተርክ በተመጠኑ ቃላት ነው፡፡ “ያለፉት ጊዜያት አሁን ለእኔ የጥንካሬ ምንጮች ናቸው፤ ለምሳሌ እየሄድኩ ቢደክመኝ እና የምተኛበት አጥቼ ግንድ ደገፍ ብዬ ብተኛ ምንም አይመስለኝም፡፡ ጃሉድ ረሃብ ምን እንደሚመስል በተግባር አይቶታል፤ ግን ደግሞ ዓላማው ዘፈን ሠርቶ ውጤታማ ማድረግ ነውና በየቀኑ ከሙዚቃ ጋር ይውላል ይኖራል፡፡ “የሚገርምሽ ነገር ለምግብ የምሰጠው ምንም ዋጋ አልነበረም፤ ከተገኘ እሰየው ከሌለ ግድ አልነበረኝም፤ ያ ነገር ለምዶብኝ ነው መሰለኝ አሁን እራሱ ሆድ መሙላቱ ብዙም ቦታ የምሰጠው አይደለም” ይላል፡፡

የጃሉድ የመከራ ዓመታት ማጣት እና መራብ ብቻ አልነበሩም ለአምስት ተከታታይ ዓመታት ታምሞ ነበር፡፡ “አንዳንድ ጊዜ በጣም ጤነኛ እሆናለሁ፤ አንዳንዴ ደግሞ በተከታታይ ለሦስት ወር እታመማለሁ፤ በወቅቱ ምን እንደሚያመኝ አላውቀውም ነበር፤ አሁን ግን ሳስበው አለመረጋጋት እና ጭንቀት የፈጠሩብኝ ስሜቶች ሳይሆን አይቀርም” ይላል ጃሉድ፡፡ የጃሉድ ትረካ ይቀጥላል፤ ግን ስሜቱ እና የድምፁ መጠን አይቀየርም፤ በጀመረው መንገድ እየተረከ ይቀጥላል፡፡

ወደ ሻኩራ ገዳም

ከአንድ ዓመት በፊት የጃሉድን የ17 ዓመታት የውጣ ውረድ ታሪክ መስመር የሚያሲዝ አንድ ዕድል ተፈጠረ፡፡ የአልበሙን ሚክሲንግ እና ማስተሪንግ የሠራለት ሰላም በላቸው (ፒስ) የተባለ ጓደኛው ወደ ሻኩራ ገዳም ይዞት ገባ፡፡ ገዳሙም በፍቅር ተቀበለው፡፡

‹‹ሻኩራ ገዳም” እውነተኛው ገዳም አይደለም፤ የሙዚቃ ባለሞያዎቹ ተሰብስበው የሰጡት ስያሜ ነው፡፡ በተለምዶ 22 እየተባለ በሚጠራው አካባቢ፣ የሙዚቃ አቀናባሪው ካሙዙ ካሳ የሚገኝበት ስቱዲዮ ነው፡፡

በዚህ ስቱዲዮ ውስጥ ካሙዙን ጨምሮ አራት ባለሞያዎች እዛው ይሠራሉ፣ እዛው ይበላሉ፣ እዛው ቤት ይተኛሉ እናም ለቤቱ “ሻኩራ ገዳም” የሚል ስያሜ ሰጡት፡፡ ጃሉድ በዚህ ቤት አምስተኛ ሰው ሆኖ ገባ፤ አልበሙንም መሥራት ጀመረ፡፡

“በአንድ ዓመት ቆይታዬ ለመቀረጽ ከካሙዝ ጋር ቀጠሮ የያዝኩባቸው ቀናት በጣት የሚቆጠሩ ናቸው፤ አንዳንዶቹ ዘፈኖች በቀጥታ ስቱድዮ  ውስጥ ለመቀረጽ ስገባ የመጡልኝ ዜማና ግጥሞች ናቸው፡፡ በሙዚቃ ውስጥ ያሳለፍኩት ረጅም ዓመታት እና እግዚአብሔር የሰጠኝን የዜማ ፀጋ ያለ ማቋረጥ ከውስጤ እንዲወጣ  ማድረጉ ነው፡፡

ከፈለግሁ አሁን ቁጭ ብዬ አዲስ ዜማ ልፈጥር እችላለሁ፡፡›› ጃሉድ በከፍተኛ በራስ የመተማመን ስሜት ውስጥ ሆኖ ነበር የሚተርከው፤ “ልዝፈንልሽ?” ድንገት ጠየቀ ጃሉድ የዚህ ሁሉ ዓመታት ልፋቱ ለውጤት ሲበቃ በማየቱ ተደስቷል፤ “እንኳን አንዱን ጀመርኩት እንጂ ከዚህ በኋላ ሌላውን መሥራት አያቅተኝም›› ሲልም በቀጣዩ ስለሚሠራው ሥራ ያስባል፡፡

ያቺን ነገር

“ያቺን ነገር” የተሰኘው የጃሉድ አዲስ አልበም፣ 16 ዘፈኖችን ይዟል፡፡ ከግማሽ በላይ የሚሆነው የዚህ ዘፈን ክፍል፣ በሬጌ ስልት የተቀነቀኑ ሲሆን የሁሉም ዘፈኖች ግጥም እና ዜማ የተሠሩት በእራሱ በጃሉድ ነው፡፡

ጃሉድ አልበሙን ሠርቶ ካጠናቀቀ በኋላ ለገበያ የሚያቀርብበት መንገድ ሌላ አሳሳቢ ፈተና ሆኖበት ነበር፡፡ ከ “ናሆም ሪከርድስ” ጋር ተነጋግሮም ረጅም ቀጠሮዎችን መጠበቅ ነበረበት፤ እንዲያም ሆኖ በቀጠሮው ሰዓት ሊደርስለት አልቻለም፡፡ታደለ ሮባ ሙዚቃ ለመሥራት ወደ ሻኩራ ገዳም ከሚሄዱ ደንበኞች አንዱ ነው፡፡ የጃሉድን ዘፈኖች እንደሰማም ፕሮዲዩስ ለማድረግ ተስማማ የሙዚቃ አልበሙን ለማጠናቀቅ የራሱ አስተዋጽኦ በማበርከት፣ አልበሙን አሳትሞ የማከፋፈል ኃላፊነቱን ወስዶ እንዳለውም አደረገ፡፡

ያቺን ነገር የት ደረሰ?

አልበሙ ከወጣ አንድ ወር ሆኖታል፡፡ ጃሉድ፤ ታደለ ሮባ የሰጠውን መረጃ ተሞርኩዞ ሲናገርም፤ “ታደለ እንደነገረኝ የመጀመሪያ ዙር ሕትመት ተጠናቆ፣ ሁለተኛውን ዙር ለማሰራጨት ማተሚያ ቤት ገብቷል፤ ሰዎች እየሰሙት ሰምተውትም አስተያየት እየሰጡ መሆኑን አውቃለሁ፡፡ በዚህም ተደስቻለሁ፤ ዐሥራ ምናምን ዓመታት የለፋሁት ለዚህ አይደል በመጨረሻ ምኞቴ እውን ሲሆን በማየቴ በጣም ተደስቻለሁ” በማለት ደስታውንም ይገልፃል፡፡

ጃሉድ ከዚህ በኋላ

“የመድረክ ሥራ እንዳቀርብ ጥያቄዎች እየቀረቡልኝ ነው፡፡ እኔ ግን “እንዴት ሆኜ፤ በምን መልኩ ነው መድረክ ላይ ወጥቼ ሥራዎቼን የማቀርበው” የሚለውን በጣም እያሰብኩበት ነው!! መድረኩስ ምን መምሰል አለበት? የሚለውን እየተማከርኩበት ነው ከዛ በኋላ የመድረክ ሥራዎችን የምሠራ ይመስለኛል” በማለት በቀጣይ ማከናወን ስለሚገባው ነገሮች ይናገራል፡፡

ጃሉድ እና ሬጌ

የጃሉድ አማርኛ እንደ ሬጌ የሙዚቃ ስልት አቀንቃኞች የተወላገደ ይመስላል፡፡ እሱ እንደሚለው፤ ይህ የአዘፋፈን ስልት ከዜማው እና ከግጥሙ ጋር አብሮ የተሰጠው እንደሆነ ይናገራል፡፡

‹‹ድሮ ስዘፍን ልክ አሁን እንደማወራው ነበር፤ በኋላ ግጥም ሳልጽፍ ዜማ ሳልደርስ ዝም ብዬ ከውስጤ ማውጣት ስጀምር፤ አማርኛው አሁን የዘፈንኩበትን ስልት መያዝ ጀመረ፡፡ ሳጣጥመው በጣም ወደድኩት፤ በቃ በዛው ቀጠልኩበት” ይላል ጃሉድ፡፡

እንዳለውም ጃሉድ ለየት ያለ ሥራ ይዞ ቀርቧል፡፡ የካሴት አዟሪዎች መረጃም የሚያሳየው ይህንን ነው፡፡ ሰዎች ሲዲውን እየገዙለት ነው፡፡

 

 

Read 2928 times Last modified on Friday, 06 April 2012 11:37