Sunday, 28 May 2017 00:00

ማንችስተር - የአውሮፓ 13ኛው የሽብር ጥቃት ሰለባ

Written by 
Rate this item
(5 votes)

   የአውሮፓ የቅርብ አመታት የሽብር መዝገብ፣ ከፓሪስ እስከ ማንችስተር

      አሁንም አውሮፓ ተሸበረች…
ባለፈው ሰኞ ምሽት በእንግሊዟ ማንችስተር ከተማ ሙዚቃን ሊያጣጥሙና መንፈሳቸውን ዘና ሊያደርጉ ከየአቅጣጫው የተሰባሰቡ የሙዚቃ አፍቃሪያን፣ በአንድ አዳራሽ ውስጥ ታድመው ነበር፡፡ በርካታ ወጣቶችና ህጻናት የታደሙበት የአሜሪካዊቷ አሪያና ግራንዴ የሙዚቃ ኮንሰርት ሞቅ ደመቅ ብሎ ወደ መገባደጃው ተቃርቧል፡፡
የሆነች ቅጽበት ላይ ግን…
አዳራሹን ያናወጠና ከሙዚቃው ድምጽ በላይ ጎልቶ ያስተጋባ፣ ያልተጠበቀ ፍንዳታ ድምጽ ተሰማ፡፡ ለሙዚቃ የታደሙት ተመልካቾች በድንገተኛው ፍንዳታ ተደናግጠው ነፍሳቸውን ለማዳን በየአቅጣጫው ተራወጡ፡፡ ጭንቅ ሆነ፡፡ ሁሉም ራሱን ለማዳን የቻለውን ሁሉ ማድረግ ያዘ፡፡
ከአይሲስ ጋር ግንኙነት እንዳለው በተነገረለት አጥፍቶ ጠፊ የተፈጸመውና የሽብር ቡድኑም ሃላፊነቱን እንደሚወስድ በይፋ ባስታወቀበት የማንችስተሩ የሽብር ጥቃት፤ 22 ያህል ሰዎችን ሲገድል፣ ሌሎች 59 ሰዎችን አቆሰለ፡፡ እንግሊዝ ብቻ ሳትሆን መላ አውሮፓ በድንጋጤ ክው አለች፡፡
የማንችስተሩ የሽብር ጥቃት እ.ኤ.አ ከ2015 ወዲህ በምዕራብ አውሮፓ አገራት የተፈጸመ 13ኛው ጥቃት ሲሆን፣ በእነዚሁ ጥቃቶች ከ300 በላይ ሰዎች ለህልፈተ ህይወት እንደተዳረጉ ሮይተርስ ዘግቧል፡፡ ለአብዛኛዎቹ የሽብር ጥቃቶች ሃላፊነቱን የወሰደውም አሸባሪው ቡድን አይሲስ መሆኑን ጠቁሟል፡፡
ሽብር ከወትሮ በተለየ አምና እና ዘንድሮ አውሮፓን ደጋግሞ ሰለባው አድርጓታል፡፡ አህጉሪቱ ሽብርንና ሽብርተኞችን ለመዋጋት የቻለቺውን ያህል ታጥቃ ብትነሳም፣ ችላ መመከት እንዳቃታት ዘገባዎች ይጠቁማሉ፡፡ የሽብር ጥቃቶች ከፈረንሳይ እስከ ቤልጂየም፣ ከእንግሊዝ እስከ  ጀርመን በየአቅጣጫው መፈጸማቸውንና የከፋ ጥፋት ማድረሳቸውን ቀጥለዋል፡፡
አምና እና ዘንድሮ ብቻ በአህጉሪቱ ከተፈጸሙት ዋና ዋና የሽብር ጥቃቶች መካከልም የሚከተሉት ይጠቀሳሉ፡፡
ባለፈው ሚያዝያ ወር በፈረንሳይ መዲና ፓሪስ የተፈጸመው የሽብር ጥቃት አንድን ፖሊስ ለሞት የዳረገ ሲሆን፣ አሸባሪው ቡድን አይሲስ ለሽብር ጥቃቱ ሃላፊነቱን ወስዷል፡፡
በሚያዝያ መጀመሪያ በስቶክሆልም የተፈጸመው የሽብር ጥቃትም አምስት ሰዎችን ለሞት፣ ከ15 በላይ የሚሆኑትን ደግሞ ለመቁሰል አደጋ ዳርጓል፡፡ ትልቅ መኪና ይዞ ጥቃቱን የፈጸመው ራክማት አኪሎቭ የተባለ ኡዝቤክስታናዊ ሲሆን፣ ግለሰቡ የአይሲስ አባል እንደነበረም ተናግሯል፡፡
በመጋቢት ወር መጨረሻ አካባቢ ካሊድ ማሱድ የተባለ ግለሰብ፣ በታዋቂው የለንደኑ ዌስትሚኒስቴር ድልድይ አቅራቢያ በከፈተው የተኩስ ጥቃት አራት ሰዎችን ገድሎ፣ ሌሎች ከ40 በላይ የሚሆኑትንም አቁስሏል፡፡ በስተመጨረሻም ሊያመልጥ ሲሞክር ከፖሊስ በተተኮሰበት ጥይት ተገድሏል፡፡ አይሲስም እንደ ልማዱ ሽብሩን የፈጸምኩት እኔ ነኝ ሲል በኩራት አውጇል፡፡
ያለፈው አመት 2016 ሃምሌ ወር ለጀርመን የተደራራቢ የሽብር ጥቃትና የሃዘን ወር ነበር፡፡ በዚያው ወር በበርሊን ሆስፒታል ውስጥና በኡዝበርግ ባቡር ላይ የተፈጸሙትን የሽብር ጥቃቶች ጨምሮ በአንድ ሳምንት ብቻ አምስት የሽብር ጥቃቶች ተፈጽመዋል፡፡
በመጋቢት ወር 2016 መጨረሻም በቤልጂየም መዲና ብራስልስ እጅግ አሰቃቂ የሽብር ጥቃቶች ተፈጽመዋል፡፡ በብራስልስ አውሮፕላን ማረፊያ እና በባቡር ጣቢያ አካባቢ የተፈጸሙት ሁለት የሽብር ጥቃቶች በድምሩ 32 ሰዎችን ለህልፈተ ህይወት ሲዳርጉ ከ300 በላይ የሚሆኑትንም ለመቁሰል አደጋ ዳርገዋል፡፡
በፈረንጆች አመት 2015 የመጀመሪያ ሳምንት በቻርሊ ሄቢዶ መጽሄት ዝግጅት ክፍል ቢሮ ላይ በተፈጸመ የሽብር ጥቃት 17 ዜጎቿን ያጣቺው ፈረንሳይ፣ ከወራት በኋላም 130 ሰዎችን ለሞት የዳረገ ሌላ የሽብር ጥቃት አስተናግዳለች፡፡

Read 3640 times