Sunday, 28 May 2017 00:00

የአውሮፓ ሊጎች የኃይል ሚዛን ከታላላቆቹ ክለቦች ሊወጣ አልቻለም

Written by 
Rate this item
(2 votes)

 በ2016/17 የውድድር ዘመን የአውሮፓ 5 ታላላቅ ሊጎች  ሲገባደዱ  ቼልሲ በእንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ    ፤ ጁቬንትስ በጣሊያን ሴሪ ኤ ፤ ባየር ሙኒክ በጀርመን ቦንደስ ሊጋ፤ ሪያል ማድሪድ በስፔን ላሊጋ እንዲሁም ሞናኮ በፈረንሳይ ሊግ 1 ሻምፒዮንነታቸውን አረጋግጠዋል፡፡ ከ5ቱ ታላላቅ ሊጎች ባሻገር በሳምንቱ አጋማሽ ላይ  በዩሮፓ ሊግ ማንችስተር ዩናይትድ ከአያክስ ተፋልመዋል፡፡ ማንችስተር ዩናይትድ 2ለ0 በማሸነፍ ለመጀመርያ ጊዜ የዩሮፓ ሊግ ዋንጫን ያሸነፈ ሲሆን እንዲሁም በሊጉ አምስተኛ ደረጃ ይዞ በማጠናቀቁ በቀጣይ የውድድር ዘመን የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ ተሳትፎውን አሳክቷል፡፡ በሌላ በኩል ከሳምንት በኋላ በ62ኛው የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ የዋንጫ ጨዋታ  የስፔኑ ላሊጋ ሻምፒዮን  ሪያል ማድሪድ ከጣሊያኑ ሴሪ ኤ አሸናፊ ጁቬንትስ  ይፋጠጣሉ፡፡
በቅርቡ ይፋ ባደረገው  ሪፖርት The CIES Football Observatory የተባለ የእግር ኳስ ጥናት አድራጊ ተቋም በ5ቱ የአውሮፓ ታላላቅ ሊጎች እንደተለመደው የኃይል ሚዛኑ ከታላላቅና ውጤታማ ክለቦች ሊወጣ አልቻለም፡፡ በተለይ የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ ከ1993 እኤአ ወዲህ በአዲስ አሰራር መካሄድ ከጀመረበት ጊዜ አንስቶ በየሊጎቹ የገቢ ሁኔታዎች በከፍተኛ ደረጃ ያደጉ ቢሆንም፤ በትልልቅ እና ትንንሽ ክለቦች መካከል ያለው የሃይል ሚዛን ሊጠብብ ግን አልቻለም፡፡  
በሲአይኢኤስ ሪፖርት መሰረት  ከ1993 እኤአ ወዲህ በነበሩት  25 የውድድር ዘመናት በአምስቱ ታላላቅ ሊጎች  ሻምፒዮን የሆኑ ክለቦች በዝርዝር ሲጠቀሱ የጥቂት ክለቦች የበላይነት ቀጥሏል፡፡ በእንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ 6 ፤ በጣሊያን ሴሪ ኤ 5፤ በስፔን ላሊጋ 5፤ በጀርመን 6 እንዲሁም በፈረንሳ ሊግ 1 10 የተለያዩ ክለቦች የሻምፒዮናነት ክብሩን ባለፉት 25 የውድድር ዘመናት ማሳካታቸውን ለማረጋገጥ ተችሏል፡፡
በእንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ በሻምፒዮናነት የጨረሰው  ቼልሲ ሲሆን፤  ባለፉት 25 የውድድር ዘመናት በአጠቃላይ የሻምፒዮናነት ክብሩን ለማግኘት የበቁት 6 ክለቦች ናቸው፡፡ ማንችስተር ዩናትድ 13 ጊዜ፤ ቼልሲ 5 ጊዜ፤ አርሰናል 3 ጊዜ፤ ማችስተር ሲቲ 2 ጊዜ እንዲሁም ሌስተር ሲቲ እና ብላክበርን ሮቨርስ እኩል አንድ ጊዜ የሊጉን የሻምፒዮናነት ክብር ተጎናፅፈዋል፡፡
በጣሊያን ሴሪ  ኤ ለስድስተኛ ተከታታይ የውድድር ዘመን የስኩዴቶውን ክብር ለመቀዳጀት ከጫፍ ላይ የደረሰው ጁቬንትስ ሲሆን፤ ባለፉት 25 የውድድር ዘመናት የስኩዴቶውን ክብር  ለመጎናፀፍ የበቁት አምስት ክለቦች ናቸው፡፡ ለ11 ጊዜያት የስኩዴቶውን ክብር በመቀዳጀት ከፍተኛውን ስኬት ያስመዘገበው ጁቬንትስ ሲሆን ከ2012 ጀምሮ እስከ 2017 ለስድስት ተከታታይ ጊዜያት ሻምፒዮን መሆኑ ክብረወሰን ሆኖ የሚመዘገብ ነው፡፡  ለ6 ጊዜያት የሴሪኤውን የስኩዴቶ ክብር በመጎናፀፍ ኤሲ ሚላን ሲከተል፤ ኢንተርሚላን ለአምስት ጊዜ ፤ ላዚዮ እና ሮማ እኩል አንድ ጊዜ የስኩዴቶውን ክብር ተጎናፅፈዋል፡፡
በስፔን ላሊጋ ከ2012 በኋላ ለመጀመርያ ጊዜ ሻምፒዮን ለመሆን የበቃው ሪያል ማድሪድ ሲሆን 25 የውድድር ዘመናት 5 ክለቦች የሻምፒዮናነት ክብሩን አግኝተዋል፡፡ ባርሴሎና  በድምሩ ለ12 ጊዜያት የስፔን ሻምፒዮን በመሆን ቀዳሚ ሲሆን  ሪያል ማድሪድ ለ7 8 ጊዜያት ሻምፒዮን በመሆን በሁለተኛ ደረጃ ተቀምጧል፡፡ አትሌቲኮ ማሪድ እና ቫሌንሽያ እያንዳንዳቸው እኩል ሁለቴ እንዲሁም ዲፖርቲቮ አንዴ ዋንጫውን አንስተዋል፡፡
በጀርመን ቡንደስ ሊጋ የዘንድሮ ሻምፒዮን ለመሆን የበቃው ባየር ሙኒክ ሲሆን፤ ባለፉት 25 የውድድር ዘመናት 6 የተለያዩ ክለቦች የሻምፒዮናነት ክብሩን አግኝተዋል፡፡ 16 የቡንደስሊጋ የሻፒዮንነት ክብሮችን በመሰብሰብ ግንባር ቀደም የሆነው ባየር ሙኒክ ሲሆን፤ ቦርስያ ዶርትመንድ  3 ጊዜ፤ ዌርደር ብሬመን ሁለት ጊዜ እንዲሁም ካይዘስላውተርን ፤ ስቱትጋርት እና ዎልፍስበርግ እኩል አንድ ጊዜ ሻምፒዮን ለመሆን ችለዋል፡፡
በፈረንሳይ ሊግ 1  ሻምፒዮን ለመሆን የበቃው ሞናኮ ሲሆን ባለፉት 25 የውድድር ዘመናት 10 የተለየዩ ክለቦች ሻምፒዮኖች ሆነዋል፡፡  ኦሎምፒክ ሊዮን ለ7 ጊዜያት፤ ፒኤስጂ ለ4 ጊዜያት፤ ሞናኮ ለ3 ጊዜ፤ ናንትስ እና ቦርዶ እያንዳንዳቸው እኩል 2 እንዲሁም ኦክዜር፤ ሌንስ፤ ማሴይ፤ ሊል እና ሞንትፕሌየር እኩ 1 ሻምፒዮን ሊሆኑ ችለዋል፡፡
በሌላ በኩል በ2016/ 17 የውድድር ዘመን The CIES Football Observatory በሰራው ሪፖርት በተጨዋቾች ስብስብ የዋጋ ግምት ደረጃ ውዱ ክለብ የነበረው የእንግሊዙ ማንችስተር ዩናይትድ በ626 ሚሊዮን ፓውንድ ነው፡፡ የስፔኑ ሪያል ማድሪድ በ553 እና ማንችስተር ሲቲ በ533 ሚሊዮን ፓውንድ ሁለተኛ እና ሶስተኛ ደረጃ ላይ ናቸው፡፡ ባርሴሎና በ423፤ ቼልሲ በ419፤ ፒኤስጂ በ397፤ ጁቬንትስ በ345፤ አርሰናል 332፤ ባየር ሙኒክ በ312 እንዲሁም ሊቨርፑል በ310 ሚሊዮን ፓውንድ የተጨዋቾች ስብስብ የዋጋ ተመናቸው እስከ 10ኛ ያለውን ደረጃ ይወስዳሉ፡፡
በውድድር ዘመኑ በ5ቱ የአውሮፓ ታላላቅ ሊጎች  የእግር ኳስ ገበያው እስከ 25 ቢሊዮን ዩሮ የተንቀሳቀስበት ሲሆን በየሊጎቹ ተሳታፊ የሆኑ ክለቦች ድምር ገቢ ከ15 ቢሊዮን ዩሮ በላይ እንደሚሆን ተገምቷል፡፡ በእንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ  718 ፤ በጀርመን ቡንደስ ሊጋ 316፤ በስፔን ላሊጋ 264፤ በጣሊያን ሴሪኤ 133 እንዲሁም በፈረንሳይ ሊግ 35 ሚሊዮን ዩሮ ተንቀሳቃሽ ትርፍ ይጠበቃል፡፡
የአምስቱ ሊጎች የተጨዋቾች ደሞዝ ወጭ  ከ7.4 ቢሊዮን ዩሮ በላይ የነበረ ሲሆን በተጨዋቾች የዝውውር ገበያ እስከ 4.2 ቢሊዮን ዩሮ ወጥቷል፡፡  በትራንስፈርማርከት  በዝርዝር በሰፈረው መረጃ መሰረት የእንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ ላይ የተወዳደሩ 20 ክለቦች የነበሩት 521 ተጨዋቾች የዋጋ ተመናቸው 4.91 ቢሊዮን ዩሮ ፤ በስፔን  ላሊጋ የተወዳደሩ 20 ክለቦች  484 ተጨዋቾች የዋጋ ተመናቸው 3.65 ቢሊዮን ዩሮ ፤ በጣሊያን ሴሪ ኤ የተወዳደሩ 20 ክለቦች  529 ተጨዋቾች የዋጋ ተመናቸው 2.88 ቢሊዮን ዩሮ  ፤ በጀርመን ቡንደስ ሊጋ የተወዳደሩ 18 ክለቦች  506 ተጨዋቾች የዋጋ ተመናቸው 2.63 ቢሊዮን ዩሮ እንዲሁም በፈረንሳይ ሊግ 1  የተወዳደሩ 20 ክለቦች  553 ተጨዋቾች የዋጋ ተመናቸው 1.73 ቢሊዮን ዩሮ ነበር፡፡

Read 2019 times