Sunday, 28 May 2017 00:00

ዲሚያን ማርሊ ‹‹ዋን ላቭ›› ኮንሰርት በግዮን ሆቴል ያቀርባል

Written by 
Rate this item
(1 Vote)

  አባቱ ቦብ ማርሊ ሲሞት 2 ዓመቱ የነበረው የመጨረሻው ልጅ ዲሚያን ጁኒየር ጎንግ ማርሊ፤ ማክሰኞ ግንቦት 29 ቀን 2009 ዓ.ም በግዮን ሆቴል ኮንሰርት እንደሚያቀርብ አዘጋጆቹ አስታወቁ፡፡
አዘጋጆቹ ባለፈው ረቡዕ በራማዳ አዲስ ሆቴል በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ፣ ዲሚያን 20 የሬጌ ሙዚቃ አባላትን ይዞ እንደሚመጣ ጠቅሰው፣ እዚህ ካሉት አርቲስት ዘለቀ ገሠሠና አርቲስት ጆኒ ራጋ ጋር ብላክ ኖት ሂፕ ሃፕን በማካተት፣ “ዋን ላቭ” የተሰኘ የዓመቱን ትልቅ ኮንሰርት እንደሚያቀርብ ገልጸዋል፡፡
በበርካታ የዓለም አገራት (ፓሪስ፣ ለንደን፣ ኬንያ፣ ደቡብ አፍሪካ፣ ሲሼልስ …) እየዞረ ኮንሰርት በማቅረብ ላይ የሚገኘው ዲሚያን፤ በ1976 (እ.ኤ.አ) ‹‹ሚስ ዎርልድ›› ከነበረችው አሜሪካዊት ሲንዲ ብረክስፓር የተወለደ ብቸኛው የቦብ ማርሊ ልጅ እንደሆነ ተገልጿል፡፡
በአገራችን ኮንሰርት ማካሄድ የተለመደው ቅዳሜና እሁድ ነው ያሉት አዘጋጆቹ፤ የዚህኛው ኮንሰርት ማክሰኞ መሆን ያልተለመደ ስለሆነ ቢራ ፋብሪካዎች ስፖንሰር ለማድረግ ፈቃደኞች አልሆኑም ብለዋል፡፡ የኮንሰርቱ መግቢያ ዋጋ 400 ብር፣ ቪአይፒ 600 ብር ሲሆን ቀድመው ለሚገዙ ውሱን ቲኬቶች በ350 ብር እንደሚሸጡ ተነግሯል፡፡
ዲሚያን፣ በሚመጣው ረቡዕ በኬንያ ኮንሰርት አቅርቦ በዚያው ወደ ሲሼልና ደቡብ አፍሪካ እንደሚሄድ ጠቅሰው፣ አዲስ አበባ የሚገባው ሰኞ ማታ እንደሆነ፣ በማግስቱ ማክሰኞ ኮንሰርቱን አቅርቦ፣ ‹‹አገሬ ናት›› የሚላትን ኢትዮጵያን እንደሚያይ፣ ረቡዕ ወደ ላሊበላ እንደሚጓዝ፣ ከተቻለም ታላቁን የሕዳሴ ግድብ ለማየት እንደሚሞክር፣ ከዚያ መልስ ወደ ገርጂ መሄጃ ኢምፔሪያል አደባባይ የሚገኘውን የአባቱን የቦብ ማርሊን ሀውልት እንደሚጎበኝና ዓርብ በ20 የአውሮፓ አገሮች ኮንሰርት ለማቅረብ ወደ ለንደን እንደሚጓዝ ገልጸዋል፡፡   

Read 2268 times