Sunday, 04 June 2017 00:00

አየር መንገድ ወደ ሲንጋፖር የቀጥታ በረራ ጀመረ

Written by 
Rate this item
(0 votes)

    የኢትዮጵያ አየር መንገድ ወደ ሲንጋፖር የቀጥታ በረራ አገልግሎት መጀመሩን አስታወቀ። አየር መንገዱ ባለፈው ረቡዕ ማታ ቦሌ ዓለም አቀፍ አየር መንገድ በሚገኘው ቢሮው በሰጠው መግለጫ፤ የቀጥታ በረራው በሳምንት አምስት ቀናትና በጣም ፈጣን በሆነ ሰዓት ከሲንጋፖር ወደ 53 የአፍሪካ አገራትና ከአፍሪካ አገራት ወደ ሲንጋፖር መብር የሚያስችል መሆኑን የአየር መንገድ ዋና ስራ አስፈፃሚ አቶ ተወልደ ገ/ማሪያም ለጋዜጠኞች አስታውቀዋል፡፡ ሲንጋፖር በአሁኑ ሰዓት በጣም ያደገች፣ 5 ሚ. ህዝብ ያላትና የዜጎቿ የነፍስ ወከፍ ገቢ ከፍተኛ ከሆኑ የዓለም አገራት በሶስተኛ ደረጃ ላይ የምትገኝ በመሆኗ የቀጥታ በረራ አገልግሎቱ በኢኮኖሚው እድገትም ሆነ የቱሪስትን ፍሰት ከመጨመር አኳያ ትልቅ ፋይዳ ያለው ነው ብሏል - ዋና ሥራ አስፈጻሚው፡፡   
ሲንጋፖር አየር መንገድ እንደ ኢትዮጵያ አየር መንገድ፤ የስታር አሊያንስ አባል በመሆኑ ሁለቱ አየር መንገዶች በመተባበር ትልቅ ስራ መስራት እንደሚችሉም አቶ ተወልደ ተናግረዋል። ሲንጋፖርን ጨምሮ አብዛኞቹ የእስያ አገሮች ወደ አፍሪካ ቀጥታ በረራ እንደሌላቸው የገለፁት ኃላፊው፤ ከጆሀንስበርግና ከኬፕታውን ወደ ሲንጋፖር የሚበር አንድ አየር መንገድ እንዳለና አፍሪካንና ሲንጋፖርን የሚያገናኝ ይሄኛው ሁለተኛው መስመር እንደሆነ ገልፀዋል፡፡
ሲንጋፖር ኢትዮጵያ ውስጥ ኤምባሲ እንደሌላት ተጠቅሶ፣ የሁለቱ አገራት ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት ምን ይመስላል በሚል ጥያቄ የቀረበላቸው ሥራ አስፈጻሚው፤ ”ሲንጋፖር እዚህ ኤምባሲ የላትም፤ የሲንጋፖር የኢትዮጵያ አምባሳደርም የሚቀመጠው ሲንጋፖር ነው፤ ምንም እንኳን ኤምባሲ እዚህ ባይኖራቸውም ሁለቱ አገሮች ጥሩ ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት አላቸው፤ የቀጥታ በረራው ሁለቱንም አገራት ተጠቃሚ ያደርጋል” ብለዋል፡፡
የኢትዮጵያ አየር መንገድ አለም አቀፍ መዳረሻዎች ከ95 በላይ የደረሱ ሲሆን ባለፈው ሰሞን ወደ ቼንዶ፣ መጋቢት መገባደጃ ላይ ቪክቶሪያ ፎልስ፣ ማዳጋስካር አንታናናሪቮ፣ እንዲሁም ኖርዌይ የቀጥታ በረራ ከፍቷል፡፡
ከሚያዝያ እስከ ግንቦት ባሉት ሁለት ወራት ውስጥ አምስት አዳዲስ የቀጥታ በረራ መስመሮችን መክፈቱንም አቶ ተወልደ ገ/ማርያም ገልፀዋል፡፡


Read 1144 times