Saturday, 10 June 2017 14:28

በቦሌ ዘመናዊ የአውሮፕላን ማቆሚያ ቴክኖሎጂ ተገጠመ

Written by 
Rate this item
(0 votes)

  በቦሌ አለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ፤ ከ778 ሺህ ዩሮ በላይ በሆነ ወጪ ለመጀመሪያ ጊዜ ዘመናዊ የአውሮፕላን ማቆሚያ ቴክኖሎጂ ተገጥሞ፣ አገልግሎት መስጠት መጀመሩ ተገለጸ፡፡
የኢትዮጵያ ኤርፖርቶች ድርጅት ለአዲስ አድማስ በላከው መረጃ፤ ከዚህ ቀደም አውሮፕላኖችን በቦታቸው ለማቆም አገልግሎቱ በሰው ኃይል ይሰጥ እንደነበረ ጠቅሶ፤ ይህ አሰራር ከአየር መንገዱ ዘመናዊ አሰራር ጋር የማይሄድ በመሆኑ በዲጂታል ቴክኖሎጂ መቀየር አስፈልጓል ብሏል፡፡
አንድ አውሮፕላን በማኮብኮቢያ ሜዳ ላይ ካረፈ በኋላ እስከ ማቆሚያው ወይም የመንገደኞች መሸጋገሪያ ድልድይ ድረስ ከፓይለቱ ጋር በመነጋገር አውሮፕላኑን የማቆም ስራ ይሰራ እንደነበር ጠቁሞ፤” ይህ አይነቱ አሰራር በፓይለቱና በመረጃ ሰጪው መካከል አለመግባባት ይፈጥር ነበር፤ ቴክኖሎጂው ይህን ችግር ሙሉ በሙሉ ይቀርፋል” ሲል አብራርቷል፡፡  
ቴክኖሎጂውን ሴፍ ጌት የተባለ የስዊድን ኩባንያ ያቀረበ ሲሆን በቦሌ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ከሚገኙ 52 የአውሮፕላን ማቆሚያዎች መካከል ለጊዜው 14ቱ ላይ መሳሪያው ተተክሎ አገልግሎት መስጠት እንደጀመረ ተጠቁሟል።
ቴክኖሎጂው የአውሮፕላን ማረፊያውን አገልግሎት በማዘመን፣ አለማቀፍ ደረጃውን የጠበቀ አገልግሎት ለመስጠት ያስችላል ተብሏል።  

Read 1515 times