Monday, 12 June 2017 06:54

አይሲስ በሞሱል 231፣ አልሻባብ በፑንትላንድ 70 ሰዎችን ገድለዋል

Written by 
Rate this item
(0 votes)

 በኢራቅ የአይሲስ ታጣቂዎች ባለፈው ሳምንት ብቻ ከምዕራባዊ ሞሱል ለማምለጥ የሞከሩ ከ231 በላይ ሰዎችን መግደሉ የተነገረ ሲሆን፣ አልሻባብ በበኩሉ፤ ከትናንት በስቲያ በፑንትላንድ በሚገኝ የጦር ሰፈር ላይ በፈጸመው ጥቃት 70 ያህል ሰዎችን መግደሉ ተዘግቧል፡፡
ታጣቂዎቹ ባለፈው አንድ ሳምንት ብቻ ከአይሲስ ይዞታ በማምለጥ በኢራቅ ወታደሮች ቁጥጥር ስር ወደሚገኙ አካባቢዎች ለማምለጥ ሞክረዋል የተባሉትን ከ231 በላይ ኢራቃውያንን መግደሉን የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ከትናንት በስቲያ አስታውቋል፡፡
ዛንጂሊ በተባለቺው የምዕራባዊ ሞሱል አካባቢ ሰሞኑን በተከፈተ የአየር ጥቃት እስከ 80 ያህል ኢራቃውያን መገደላቸውን የሚጠቁም መረጃ ማግኘቱን የገለጸው ተመድ፤ ጉዳዩን እያጣራ እንደሚገኝም አስታውቋል፡፡ በአሮጌዋ የሞሱል ከተማ ከ200 ሺህ በላይ ኢራቃውያን የስቃይ ኑሮ እየገፉ እንደሚገኙም ተመድ አመልክቷል፡፡
አሶሼትድ ፕሬስ በበኩሉ፤ በከፍተኛ ሁኔታ የታጠቁ የአልሻባብ ወታደሮች ከትናንት በስቲያ በፑንትላንድ በሚገኝ የጦር ሰፈር ላይ በፈጸሙት ጥቃት ከ70 በላይ ሰዎችን መግደላቸውንና በርካቶችን ማቁሰላቸውን የዘገበ ሲሆን በአፍሪካ ቀንድ አካባቢ በቅርብ አመታት ታሪክ የተፈጸመው የከፋ ጥቃት ነው በተባለው በዚህ የአልሻባብ ጥቃት ሴቶችንና ህጻናትን ጨምሮ አንገታቸው ተቀልቶ የተገደሉ በርካታ ሰዎች እንዳሉ ተገልጧል፡፡  
አጃንስ ፍራንስ ፕሬስ በዘገባው፤ ቦኮሃራም በናይጀሪያዋ ሜዱጉሪ ከተማ ከትናንት በስቲያ በፈጸመው የተኩስና የአጥፍቶ መጥፋት ጥቃት 11 ያህል ሰዎች መገደላቸውን ጠቁሟል፡፡

Read 1815 times