Print this page
Sunday, 02 July 2017 00:00

ጋቶች ወደ ራሽያ ለኢትዮጵያ አዲስ ምዕራፍ

Written by 
Rate this item
(0 votes)

      የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን እንዲሁም የኢትዮጵያ ቡና ክለብ ተጨዋችና አምበል ሆኖ ያገለገለው ጋቶች ፓኖም የራሽያውን ታዋቂ ክለብ አንዚ ማካችካላ ተቀላቀለ፡፡ የ23 ዓመቱ ጋቶች ይህን በኢትዮጵያ እግር ኳስ አዲስ ምዕራፍ የሚከፍት ዝውውር ያሳካው ከኢትዮጵያ ቡና ጋር የነበረው የቅጥር ውል ካበቃ በኋላ ነው፡፡  ባለፈው ሰሞን ለሙከራ ወደ ራሽያ ተጉዞ የነበረው ተጨዋቹ በሙከራ ጨዋታ ላይ ጎል ካገባ በኋላ የክለቡን ሃላፊዎች እና አሰልጣኞች ስለማረካቸው፤ የዝውውሩን ሂደት ስኬታማ አድርጎታል በማለት የተጨዋቹ ወኪል  ሆኖ የሰራው ትውልደ ጀርመናዊው ዴቪድ በሻህ በሰጠው መግለጫ አስታውቋል፡፡ ጋቶች በራሽያ ፕሪሚያራ ሊግ ተፎካካሪ ከሆኑ ክለቦች ዋንኛ ተጠቃሽ  የሆነውን አንዚ ማካችካላ በመቀላቀል መጫወት የሚጀምረው ከ2017 -18 እኤአ የውድድር ዘመን ጀምሮ ሲሆን የውል ስምምነቱ ለ3 ዓመታት የሚቆይ   ነው፡፡  
በተከላካይ አማካይ እና በመሃል አማካይ መስመሮች የሚጫወተው ጋቶች  ከአውሮፓ ታላላቅ ሊጎች ቀጥሎ በሚመደበው ራሽያ ፕሪሚዬራ ሊግ በመጫወት የመጀመርያው ኢትዮጵያዊ ሲሆን ይህም በኢትዮጵያ እግር ኳስ አዲስ የስኬት ደረጃ ሆኖ ሊጠቀስ ይችላል።    አንዚ ማካችካላ  ለ2017-18 ዘመን ለሚያደርገው ዝግጅት ጋቶች ፓኖምን ጨምሮ    ሌሎች 10 ተጨዋቾችን ያስፈረመ ሲሆን ከታዋቂዎቹ ሲኤስኬ እና ዳይናሞ ሞስኮ ያዛወራቸው ይገኙበታል፡፡ በተጨዋቾ ስብስቡ ከ6 የተለያዩ  አገራት ፕሮፌሽናሎች ጨምሮ 29 ተጨዋቾችን ያስመዘገበው የሩሲያው ክለብ  የዝውውር ገበያ የዋጋ ተመኑ 18.4 ሚሊዮን ዮሮ እንደሆነ ታውቋል፡፡
ከጋቶች ፓኖም የራሽያ ዝውውር በኋላ የተሰሙ አንዳንድ መረጃዎች በአንዚ ማካች ካላ በሳምንት 5ሺ ዩሮ እንደሚከፈለው የገለፁ ሲሆን  በዝውውር ገበያው የዋጋ ተመኑ ከግማሽ ሚሊዮን ዩሮ በላይ ሊሆን እንደሚችል ተገምቷል፡፡ ይህም በኢትዮጵያ እግር ኳስ ውዱ ተጨዋች ሊያደርገው ይችላል፡፡
ከጋቶች ፓኖም ሻገር የሌሎቹ ዋልያዎች የዝውውር ገበያ ግምትና ወቅታዊ ውጤታማነት
ሽመልስ በቀለ በወቅቱ የዝውውር ገበያ የዋጋ ተመኑ 400ሺ ዩሮ ነው፡፡ የግብፅ ክለብ ፔትሮጄት የሚገኘውና በቀኝ እና ግራ አማካይ መስመሮች የሚጫወተው ሽመልስ  ባለፈው 1 ዓመት በግብፅ ሊግ እና ካፕ ላይ በ22 ጨዋታዎች 5 ጎሎችን አስመዝገቧል፡፡
የ28 ዓመቱ ሳላዲን ሰኢድ በወቅቱ የዝውውር ገበያ የዋጋ ተመኑ 300ሺ ዩሮ ነው፡፡ ዘንድሮ በቅዱስ ጊዮርጊስ ማልያ በአፍሪካ ክለቦች ሻምፒዮንስ ሊግ ከቅድማጣርያው አንስቶ በ7 ጨዋታዎች በመሰለፍ 4 ጎሎች አስመዝግቧል፡፡
ኡመድ ኡክሪ በወቅቱ የዝውውር ገበያ የዋጋ ተመኑ 200ሺ ዩሮ ነው፡፡ በ2014 15 የውድድር ዘመን በአልኢትሃድ፤ በ2015 በኤንፒፒአይ እየተጫወተ ከፍተኛ ልምድ ያካበተው ኡመድ ከ2016 በጀምሮ በግብፁ ኤል ኤንታግ ኤልሃረቢ እየተጫወተ ሲሆን በግብፅ ሊግ እና ካፕ ላይ በ29 ጨዋታዎች 11 ጎሎችን አስመዝገቧል፡፡
ጌታነህ ከበደ አሁን በሚጫወትበት የደደቢት እግር ኳስ ክለብ በወቅቱ የዝውውር ገበያ የዋጋ ተመኑ 150ሺ ዩሮ ነው፡፡ ከዓመት በደቡብ አፍሪካ ሁለት ክለቦች ቢድቬስት ዊትስ እና በፕሪቶርያ ሲጫወት በ56 ጨዋታዎች በመሰለፍ 13 ጎሎች ያስመዘገበው ጌታነህ ዘንድሮ በኢትዮጵያ ፕሪሚዬር ሊግ ኮከብ ግብ አግቢነት ጨርሷል፡፡

Read 2084 times
Administrator

Latest from Administrator