Saturday, 08 July 2017 12:56

አሜሪካ ለሰ/ ኮርያ የሚሳኤል ሙከራ የከፋ ምላሽ እንደምትሰጥ አስጠነቀቀች

Written by 
Rate this item
(1 Vote)

  አሜሪካ ሰሜን ኮርያ በሳምንቱ መጀመሪያ ለፈጸመቺው የረጅም ርቀት ተወንጫፊ ሚሳኤል ሙከራ በሳምንታት ወይም በወራት ጊዜ ውስጥ የከፋ ምላሽ እንደምትሰጥ ፕሬዚዳንት ትራምፕ ማስጠንቀቃቸውን ቢቢሲ ዘግቧል፡፡
ባለፈው ማክሰኞ ረጅም ርቀት ተወንጫፊ ሚሳኤል ሙከራ ያደረገቺው ሰሜን ኮርያ እጅግ አደገኛ አካሄድ እየተከተለች ነው፤ ለዚህ ድርጊቷ ጠንከር ያለ ምላሽ ያስፈልጋታል ብለዋል ትራምፕ ከትናንት በስቲያ ዋርሶ ውስጥ በሰጡት መግለጫ፡፡ አለማቀፉ ማህበረሰብ ሰሜን ኮርያ ከዚህ አጥፊ ድርጊቷ እንድትታቀብ ማድረግ ሲሉም ጥሪያቸውን አቅርበዋል፡፡
የሰሜን ኮርያ ሚሳኤል ረጅም ርቀት በመጓዝ የአሜሪካዋን የአላስካ ግዛት የመምታት አቅም እንዳለው የጠቆመው ዘገባው፣ በተመድ የአሜሪካ አምባሳደር ኒኪ ሃሊ በበኩላቸው የሚሳኤል ሙከራውን ተከትሎ ለተባበሩት መንግስታት የጸጥታው ምክር ቤት በሰጡት መግለጫ አሜሪካ በሰሜን ኮርያ ላይ መጠነኛ ወታደራዊ እርምጃ ልትወስድ እንደምትችል ማስታወቃቸውን አስታውሷል፡፡ ሰሜን ኮርያ የጸጥታው ምክር ቤት የተጣለባትን ማዕቀብ በሚጥስ መልኩ የሚሳኤል ሙከራውን ማድረጓን ተከትሎ፣ የጸጥታው ምክር ቤት ባለፈው ረቡዕ አስቸኳይ ስብሰባ ያደረገ ሲሆን ድርጊቱን በጽኑ አውግዞታል፡፡ ደቡብ ኮርያን እና ፈረንሳይን ጨምሮ የተለያዩ አገራት መንግስታት ድርጊቱን ማውገዛቸውን የጠቆመው ዘገባው፣ በተመድ የፈረንሳይ አምባሳደር በሰሜን ኮርያ ላይ ተጨማሪ ማዕቀብ እንዲጣል ጠይቀዋል፡፡
ሩስያና ቻይና በበኩላቸው ድርጊቱን ቢኮንኑም፣ እነ አሜሪካ የያዙትን ወታደራዊ እርምጃ የመውሰድ አማራጭ ለሌላ የከፋ ቀውስ የሚዳርግ አደገኛ አካሄድ በሚል እንደማይደግፉት አስታውቀዋል፡፡

Read 2301 times